Site icon ETHIO12.COM

የዓለም ባንክ ፕሬዚዳንት አዲስ አበባ እየመከሩ ነው፤ የአገር በቀለ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በጀት ይለቀቃል ተብሎ ይጠበቃል

አሜሪካ በኢትዮጵያ ላይ ጥላው የነበረውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ክስ በይፋ ማንሳቷን ማስታወቋን የሁለቱ አገሮች ግንኙነት መሻሻሉና ወደ አንድ ከፍተኛ ሊባል የሚችል ደረጃ ማደጉን እንደሚያመላክት ፎሪን ፖሊሲ ዘግቦ ነበር። “… ይህ ውሳኔ የአሜሪካና የዓለም አቀፍ ኢኮኖሚያዊ ዕርዳታ ወደ ኢትዮጵያ መላክን ለማስቀጠል መንገድ የሚከፍት ነው” ሲል ፎሪን ፖሊሲ የዜናውን እምብርት አመላክቶም ነበር። እንግዲህ ይህን ተከትሎ ነው ዓለም ባንክ ብድርና ድጋፍ መስጠት መጅመር ብቻ ሳይሆን ፕሬዚዳንቱን አዲስ አበባ የላከው።

730 ሚሊዮን ዶላር ከጅቡቲ ወደ መሃል አገር ለሚያመራው መንገድ ማሻሻያ ገንዘብ መለቀቁ ይፋ በሆነ ማግስት የዓለም ባንክ ፕሬዝዳንት አጃይ ባንጋን አዲስ አበባ ገብተዋል። ፕሬዚዳንቱን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በጽህፈት ቤታቸው አነጋግረዋቸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዝርዝር ባይናገሩም በድጋፍና አነስተኛ በሚባል ብድር የአገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያውን የሚደግፍ የገንዘብ አቅርቦት ስምምነት እንደሚኖር ማመላከታቸውን ከጽህፈት ቤታቸው የወጣ መረጃ ያመላክታል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የዓለም ባንክን ፕሬዚዳንት በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው ሲያስጎበኙዋቸው

አሜሪካን የትህነግ ደጋፊና አዝማች ሆና ኢትዮጵያ ላይ ጠርቅማው የነበረውን በር መክፈቷን ተከትሎ የዓለም ባንክ የ400 ሚልዮን ዶላር የሰው ሃብት ላይ የሚውል ድጋፍ ማድረጉና ሃምሳ ሚሊዮን ዶላር የአነስተኛ ወለድ ብድር መፍቀዱ የሚታወስ ነው። ይህ ከመሆኑ ቀደም ብሎ ለኢትዮጵያ አገር-በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ስኬታማነት ለጋሽ ድርጅቶችና የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ጥሪ በቀረበበት ስብሰባ ላይ ለኢትዮጵያ ጥያቄ ምላሽ ከሰጡት መካከል በዓለም ባንክ የኢትዮያ ዳይሬክተር ካሮልይን ”ዓለምዓቀፉ ማህበረሰብ ኢትዮጵያ ኢኮኖሚዋን ለማሻሻይ የምታደርገውን ጥረት ያደንቃል።መንግስት በዘርፉ ያሉ ተግዳሮቶችን ለይቶ ችግሩን ለማቃለል በራሱ ከሚሰራቸው ስራዎች ባለፈ የሌሎችን ድጋፍ መጠየቁም ሊደነቅ ይገባል።ይህ የተጀመረው የኢኮኖሚ ማሻሻያ ውጤታማ እንዲሆን በፋይናንስም ሆነ በቴክኒክ ለመደገፍ ዝግጁ ነን” ማለታቸው ይታወሳል።

የድጋፍ በሩ መከፈቱን ተከትሎ ” ድጋፍ መደረግ የለበትም፣ ማዕቀብ ሊጣል ይገባል” በሚል በአሜሪካ ድምጻቸውን ያሰሙ፣ የተባበሩት መንግስታትን የወተወቱና ደብዳቤ አዘጋጅተው የላኩ ቢኖሩም፣ ለዓለም አቀፍ የልማት አጋሮችና የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አባላት በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን (ECA) አዳራሽ ገለጻ በተደረገበትና ድጋፋቸው እንዲያደርጉ በተጠየቀበት ወቅት ልክ እንደ ዓለም ባንክ ወኪል ስብሰባ ላይ  የታደሙት በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን ዋና ጸሃፊ ዶክተር ቬራ ሶንጌ “ኢትዮጵያ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ስደተኞች ተቀብለው ከሚያስተናግዱ አገሮች አንዷናት።ይህ ደግሞ ኢኮኖሚዋን ለማሳደግ የምታደርገው ጥረት ላይ ጫና ይፈጥርባታል።ይህን ጫና ለመቀነስ የተባበሩት መንግስታትም ሆነ ሌሎች የልማት አጋሮች በማሻሻያው የተገለጸው የስራ ዕድል ፈጠራ ውጤታማ እንዲሆን ድጋፍ ሊያደርጉ ይገባል” ማለታቸው ይታወሳል።

በጦርነቱ የሁለት ዓመት ቆይታ ኢትዮጵያ ላይ የወረደውን የተቀነባበረ ዘመቻ፣ የሚዲያና የዓለም አቀፍ ተቋማታ አድማና ሴራ፣ ትህነግ በውክልና በመሳሪያና በሳተላይት መረጃ እያታገዘ ሲያካሂድ የነበረውን ጦርነት በድል የተወታችው ኢትዮጵያ ሁሉን አልፋ ዛሬ የተዘገባትን በር ሁሉ አስገድዳ ለማስከፈቷ የህዝቧ ህብረትና “አትንኩኝ” ባይነት ቅድሚያውን እንደሚይዝ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ደጋግመው ማስታወቃቸው አይዘነጋም።

መከላከያዋ ታርዶባት፣ ቡና ሸጣ የገዛችው መሳሪያ ተዘርፎባት ከባዶ በመነሳት ዛሬ ላይ ፈርጣማ ክንድ ያጎለበትችው ኢትዮጵያ፣ ኮቪድ ካስከተለው ጣጣ ጋር በውስጥ ከሚቀነባበርባት ሴራ ጋር ተዳምሮ ሳይጥላት በአሸናፊነት መውጣቷን ባይገልጹም እንግዳው የዓለም ባንክ ፕሬዚዳንት ” በሀገር ውስጥ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ብዙ ፈተናዎች ቢያጋጥሙም ኢትዮጵያ ለቁልፍ የልማት ግቦች የሰጠችውን ትኩረት ይደነቃል” ሲሉ በጅምላ ማወደሳቸው ተሰምቷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይና ካቢኔያቸው፣ እንዲሁም የቅርብ አጋሮቻቸው በጋራ እንደየአግባባቸው በሁለትዮሽ ውይይቱ ላይ በአጠቃላይ የኢትዮጵያን ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ ላይ ማብራሪያ እንደሰጡ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ “የዓለም ባንክ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን የትብብር አድማስ በማስፋት ለኢኮኖሚ እድገታችን በኮንሴሽናል ፋይናንስ፣ በአለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን በኩል ጠንካራ የኢንቨስትመንት ፋይናንስ አቅርቦት እና የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳችንን የሚደግፍ የዘለቀ አስተዋፅዖ ይኖረዋል”ሲሉ በማህበራዊ አውዳቸው ላይ ጽፈዋል።

ለሁለት ቀን ቆይታ አዲስ አበባ የገብት የዓለም ባንክ ፕሬዚዳንት የአፍሪካ ህብረትን ጨምሮ ከተለያዩ አካላት ጋር እንደሚነጋገሩና ኢትዮጵያ ባቀረበችው የገንዘብ ጥያቄ አስመልክቶ ይፋዊ መረጃ እንደሚሰጡ ይጠበቃል።

ይህንን ማስፈንጠሪያ ethio12news ተጭነው በቴሌግራም ገጻችን ይከተሉን

Exit mobile version