Site icon ETHIO12.COM

የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ወቅታዊ ጉዳዮችን በተመለከተ አስቸኳይ ሀገራዊ ጥሪ አቀረበ

በኢትዮጵያ በሚገኙ የተለያዩ የፖለቲካ እና የሀሳብ መሪዎች እንዲሁም የማህበረሰብ ክፍሎች መካከል እጅግ መሠረታዊ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የሃሳብ ልዩነቶች እና አለመግባባቶች ያሉ መሆናቸው በግልፅ ይታወቃል ያለው ኮሚሽኑ፤ይህንንኑም ታሳቢ በማድረግ አለመግባባቶች በሰለጠነ መንገድ በምክክር የሚፈቱበትን አውድ ለመፍጠር የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን መቋቋሙን አንስቷል፡፡

እነዚህን ልዩነቶችና አለመግባባቶች በንግግርና በምክክር መፍታት ሲገባ በተለያዩ አካባቢዎች እና በተለያዩ ወገኖች እየተወሰዱ ያሉ የኃይል እርምጃዎች የሀገራችን ኢትዮጵያን ደህንነትና ህልውና እየተፈታተኑ መጥተዋል ብሏል፡፡

ኮሚሽኑ የተቋቋመበትን ተግባርና ኃላፊነት ለመወጣት  በሐረሪ፣ በድሬዳዋ ከተማ መስተዳድር፣ በሲዳማ፣ በደቡብ ምዕራብ፣ በጋምቤላና ቤኒሻንጉል የተሳታፊዎች ልየታ እየተከናወነ መሆኑን ኮሚሽኑ አስታውቋ፡፡

በሌሎች ክልሎችም ተመሳሳይ ተግባራት ለማከናወንና አጀንዳዎች ለመሰብሰብ በተዘጋጀሁበት በዚህ ወቅት በተለያዩ የሃገሪቱ ክፍሎች እየታዩ ያሉ ደም አፋሳሽ ግጭቶች ስራዬን አዳጋች እያደረጉት ይገኛሉ ሲል ኮሚሽኑ ገልጧል፡፡
የኮሚሽኑ ምክር ቤት ትናንት ባደረገው ልዩ ስብሰባ በመላው ሀገሪቱ የሚታዩ ግጭቶች በአስቸኳይ ያላንዳች ቅድመ ሁኔታ ቆመው የሚመለከታቸው አካላት በሙሉ አሉን የሚሏቸውን ልዩነቶች ወይም ጥያቄዎች በጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጠው በምክክር እንዲፈቱ አስቸኳይ ሀገራዊ ጥሪ አቅረቧል።

ለዚህ ተግባራዊነትም የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ባለድርሻ አካላትን በማቀራረብ፣ የልዩነት አጀንዳዎችን ሰብስቦ ለማወያየትና ለማመካከር አመቺ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ዝግጁ መሆኑን አረጋግጧል።


Exit mobile version