ETHIO12.COM

እንደ ሱዳን የመሆን ምኞትና ጥድፊያ – የነጻ አውጪ ጋጋታ

በሱዳን ኮሽ ባለ ቁጥር ” መንግስት ይናድ” እያሉ አደባባይ ወጥተው ጎማ የሚያነዱ ዛሬ ከስመዋል። ኮሽ ባለ ቁጥር ተተኪ ሳይዘጋጅላቸው መንግስታቸውን የናጡና የነቀነቁ ዛሬ የጸጸት ጊዜ ማግነት አልቻሉም። ተሰደዋል። ወይም የመንደር ለመንደር ሌቦች ሆነዋል። ወይም አካላቸው ከጎደሉት ውስጥ ናቸው። ወይም ሞተዋል። ኮሽ ባለ ቁጥር በስሜት የሚነዱ ሁሉ ውጤቱን ከሱዳን እያዩ ነው። ሱዳን ውስጥ “አገር የሞተ አንደሁ ወዴት ይደረሳል?” የሚለው ዘፈን ተረስቷል።

ያለ ምንም ማጋነን ከሰባት ሚሊዮን የሚልቁ የሱዳን ዜጎች በአየርና በየብስ መኖሪያ መንደራቸውን፣ ቤታቸውን፣ ንብረታቸውን ጥለው እዛም እዚህም ተሰደዋል። ይህ የሆነው ደግሞ በጣምራ አገሪቱን ሲሟሯት የነበሩት ሁለት የጦር ጀነራሎች በስልጣን ጥማት በጀመሩት ጦርነት ሳቢያ የሆነ ነው። ኢመደበኛ ሃይል ገንብቶ ከውጭ ሃይሎች ጋር ተቧድኖ በማዕድን ንግድ ካዝናውን ያደለበው መሃይምና የአገሪቱን ሲቪል መንግስት ከበተነው የጦር መኮንን ጋር ለመበላላት በተጀመረው ጦርነት ያለቁትም ቁጥራቸው ንሯል። ኢትዮጵያ ውስጥ የሚታየው የነጻ አውጪዎችና ግንባሮች ትንቅንቅም ሩጫው ሱዳንን የመሆን ምኞት መስሏል። በርካታ መመሳሰሎች እየታዩ ነው።

የሱዳን ጦር መሪ ጀነራል አብደል ፋታህ አል-ቡርሃን እና የፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ መሪ ጀነራል ሞሐመድ ሐምዳን ዳጋሎ ሱዳንን ተስማምቶ መጋጥ ተስኗቸው መፋለም ከጀመሩ ዛሬ ሰባት ወር አልፏቸዋል። በሰባት ወሩ የርስ በርስ ፍልሚያ እነዚህ ሁለት አልጠግብ ባዮች ባሰለፏቸው ሃይሎች አስር ሺህ የሚጠጉ ንጹሃን እንዳለቁ እየተገለጸ ነው። ከስድስት እስከ አስራ ሁለት ሺህ የሚሆኑ አካላቸው ጎድሏል። 4.1 ሚሊዮን በአገር ውስጥ ተፈናቅለዋል። 2.1 ሚሊዮን የሚሆኑ አገራቸውን ጥለው ነብስ አውጪኝ ስደት ላይ ናቸው። በውጭ ሃይሎች ግፊትና እርዳታ ነዳጅ የሚርከፈከፍበት የሱዳን ቀውስ አገሪቱን ትናንሽ ቦታ ሊቆራርሳት እንደሆነም እየተሰማ ነው።

ሲያስቡት ጨለማ የሚሆነው የሱዳን ጉዳይ ከሞት፣ ስደትና አካለ ጎዶሎነት በተጨማሪ ችጋር፣ በሽታ ጥማት የከፋ አደጋ አንግሶባታል። ሴቶች፣ አረጋዊያና ህጻናት በያሉበት ጠኔ እየጠበሳቸው እንደሆነ መረጃዎች እየወጡ ነው። ጎን ለጎን ደግሞ ወዴት ወስደው እንደሚሸጡት ባይታወቅም የቤት ለቤት ዘረፋው የሚከናውነው ያለማንም ከልካይ ነው። ዘረፋው እንዴት እንደሚከናወን የሚገልጹ ሚዲያዎች እንደሚሉት ከሆነ ሱዳን ሁሉም ነገር ሊመለስ በማይችልበት ደረጃ ፈር ለቋል። በመጋዘኖች ላይ ዝርፊያ ከተፈጸመ በሁዋላ መጋዘኑንን በእሳት ማጋየትና አመድ ማድረግ ወግ ሆኗል።

As of 15 August 2023, between 4,000 and 10,000 people had been killed and 6,000 to 12,000 others injured,[8][9][12][11] while as of 12 September 2023, over 4.1 million were internally displaced and more than 1.1 million others had fled the country as refugees.

ዝርፊያ ከተከናወናባቸው መጋዘኖች መካከል የሽቶ ማከማቻ መጋዘን ይገኛል። ይህ መጋዘን ሲዘረፍ አንድ ጨለማ አላሳይ ያለው ላይተር ለኩሶ በተፈጠረ እሳት ከመቶ ሃይ የሚልቁ ሰዎች ነደዋል። አመድ ሆነው መለየት እንዳልተቻለ የቢቢሲ ዘጋቢ ጽፋለች። በሱዳን

ጦርነቱን ተከትሎ በሱዳን መንግሥት ፈርሷል። የፖሊስ ኃይል የለም። እስር ቤቶች እየተሰበሩ ወንጀለኞች በነጻ ተለቀዋል። በጥቅሉ ህግ በአፍጢሙ ተደፍቷል። ስለ ህግ፣ ፍትህና ርትዕ ማሰብ ብሎ ነገር የለም። ከዚሁ ጋር ተያያዞ የክላሽንኮቭ ጠብ መንጃ ዋጋ በግማሽ መቀነሱ ተሰምቷል። ቢቢሲ እንዳለው ከሆነ በሱዳን ከሚማረኩና ከሚያዙ የሰራዊት አባላት የሚማረከው መሳሪያ የሚሸጠው በጦር መሪዎች ነው። ይህም በመሆኑ አቅርቦቱ ከፍተኛ ሆኖ ዋጋው ቀንሷል። 830 ዶላር ግድም የሚከፍል የካላሽ ባለቤት ይሆናል።

ሱዳን ከሶማሊያ ቀጥላ እየፈረሰች ያለች አገር ስትሆን፣ አሁን ላይ በጎሳ የመከፋፈል አብዮት እየተፋፋመባት እንደሆነ እየተገለጸ ነው። የሱዳን ፈጥኖ ደረሻ ሃይል መሪ ሕምዳን ዳጋሎ መንግስት እንደሚመሰርቱ ካስታወቁ በሁዋላ፣ ቤተመንግስታቸውን የተነጠቁት ጀነራል አብደል ፋታህ አል-ቡርሃን ጨምሮ ሱዳን ለጊዜው ሶስት ቦታ መበለቷ ፣ የንግግርና ድርድር ጉዳይ ተረት እንደሆነ እየተገለጸ ነው።

ሱዳን ከተሞቿን እየበላች ነው። ሱዳን ነዋሪዎቿ እየተበሉ ነው። ቤተሰብን፣ ዘመድን፣ ወዳጅን፣ ጎረቤትን በወጉ መቅበርና ሃዘን መቀመጥ ቅንጦት ሆኗል። የሱዳን አንጋቾች ለማንና ለምን ምክንያት እንደሚዋጉ የሱዳንን ህዝብ ወቅታዊ አቋቋም ያዩ የሚረዱት እውነት ነው። የሱዳን ህዝብ መከራው ልክ አልፎእ ግልብጥ ብሎ ወደሚችልበት ስፍራ እየጎረፈ ነው። መሰደድ ያልቻሉት አቅም ያጡ ብቻ ናቸው። ሱዳን በየትኛውም የተስፋ ሚዛን የማይለካ ውድቀት ውስጥ ተነክራለች። እዛም እዚህም የተደራጁና መሳሪያ በገፍ ያታጠቁ የሚፈነጩባት የድም መሬት ሆናለች።

ሱዳን ማሰብ የተሳናቸው ልጆቿ ልክ እንደ እሳተ ጎሞራ፣ ጎርፍና የመሬት መንቀጥቀጥ አይነት አደጋ ሆነውባታል። በስደት ኖርዌይ የምትኖር ሱዳናዊ ” ሱዳን ፈርሳለች። ተስፋ ቆርጫለሁ። ተዓምር ካልተፈጠረ በቀር የሱዳን ነገር አክትሟል” ስትል አገር አልባ የመሆን ስብራቷን ገልጻለች።

በኢትዮጵያ ለውጡን ተከትሎ የፈነዳው አዲሱ እሳቤ ስልጣን፣ ወንበር፣ ክልልነት፣ ዞንነት፣ የከተማነት ጥያቄ፣ ህገወጥነት፣ ወረራ፣ ዝርፊያ፣ ወዘተ የሚጠቀሱ ሲሆኑ ” እኔ የለውጡ ጌታ ነኝ” በሚል የሚታየው ኩርፊያ ከሁሉም ይልቃል።

ያኮረፉ የሚዲያ ሰዎች፣ የኮረፉ ፖለቲከኞች፣ ያኮረፉ ደጋፊዎች ወዘተ ብሄር እየፈለጉ ነገር ማጦዝና ህዝብን ቁጣ ውስጥ የሚከት መረጃ ማሰራጨት የትግል ስልታቸው ከሆነ ሰነባብቷል። እንደውም አንዱ ከከሸፈው ልምድ የሚቀስምምበት የቢዝነስ አውድ ሆኗል። ደምና የህዝብ ስቃይ ንግድ የሆነላቸው የድርጅት መሪ መስለው በግፋ በለው የጎ ፈንድ ሚ ተዋንያኖች ሆነዋል።

ዜጎች ተደራጅተው፣ በሰከነ መንገድ ጥያቄያቸውን ከማቅረብ ይልቅ በብስጭት እንዲነሱ “ሰበር” እያለ የሚጮኸው የንግድ ሚዲያ፣ አንድ ኪስና ቋት አልበቃ ብሎቸው ሁለትና ከዛም በላይ ሚዲያ ከፍተው የኢትጵያን ፖለቲካ እያቦኩት ነው።

ትህነግ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ በዘር ባቡር ሲከንፍ ኖሮ ዛሬ እንደሚታየው ስምና ታሪክ አልባ ሆነ። ህዝቡን ለድህነት፣ ረሃብ፣ ውርደትና ኪሳራ ዳርጎ በውርደት ሸማ ተጆብኖ የሞት ጣር ላይ ነው።

ኦነግ በተመሳሳይ ሃምሳ ዓመት በተመሳሳይ መንገድ እየዳከረ ነው። የኦሮሞ ጥያቄዎች በሙሉ ተመልሰው ፋይላቸው ተዘግቶ ሳለ አሁን ደረስ የተመለሱ ጥያቄዎች ለማስፈጸም በሚል ብረት አንስቶ ይገላል። እንደ ወለጋ አይነት የጥጋብ መሬት፣ ሃብታም ገበሬ ለማኝ አድርጎ ይፎክራል። ደግሞ ደጋግሞ ስርቻ ከወረወረው ትህነግ የሚኮርጀው ኦነግ መሳሪያውን ወርውሮ በምርጫ የፖለቲካ ስልጣን ለመያዝ ከመታገል ይልቅ ባረጀ እሳቤ ላይ ተቸክሎ የተዋለደ ህዝብ ሊበትን በየጥሻው እየተሹለከለከ ንጽሃንን ይገድላል።

አማራ ክልል የተለያዩ አካላት ከውስጥና ከውጭ መሪ እንደሆኑ የሚናገሩለት ትግል በርካቶችን ግራ አጋብቷል። አማራ ላይ የተፈጸመውን መፈናቀልና ግድያ ለማቆም አልሞ ተጀመረ የተባለው ትግል ስክነት የጎደለው፣ ወጥ ያልሆነ፣ ሌሎችንም የትግሉ አጋዥ የማይደርግ እንደሆነ ቢገልጽም አድናቆት የሚቸሩት አሉ።

እየዋለ ሲያድር አዳዲስ መረጃ የሚቀርብበት የአማራ ክልል እንቅስቃሴ አሁን ላይ “ፋኖ ለህልውና ለፍትህና ለዴሞክራሲ ንቅናቄ (ፋ.ህ.ፍ.ዴ.ን) የሚል አዲስ ስም እንደያዘም እየተገለጸ ነው። የአማራ ህዝባዊ ሃይል ግንባር በሚል ከሚታወቀውና በአገር ውስጥ እስክንድር ነጋ፣ በውጭ ሻለቃ ዳዊት የሚመሩት ይህ ንቅናቄ እያለ የተቋቋመው አዲስ ንቅናቄ በይፋ ማን እንደሚመራው አልተመለከተም። እንደሚባለው ከሆነ እነ አቶ አንዳርጋቸው በዚህ ምድብ ከነመሳይና መኮንን ጋር ተሰልፈዋል።

ስለ ድርጅቶቹ አሳብ መስጠት የጽሁፌ አላማ ባይሆንም የአማራ ክልልን እንቅስቃሴ አስመልክቶ የአመራር ሚና እንደሚጫወት የሚገልጸው የጀርመኑ አቶ ዘመድኩን (ዘመዴ) በጅምላ ሙስሊም ጠል፣ ኦሮሞ ጠል፣ መረጃዎችን በስፋት እያሰራጨ መሆኑን በርካቶች አልወደዱትም። በግል አደገኛ አካሄድ መስሎ ይታየኛል። የአማራ ህዝብ ክርስቲያን፣ ሙስሊም፣ ዋህቢያ፣ ወንጌላዊ ወዘተ ብሎ የሚከፋፈል ባለመሆኑ ይህ አካሄድ ሌላ ቀውስ የመጥመቅ አጀንዳ ሆኖ ይሰማኛል።

በተለይም አሁን የተጀመረውን ውጊያ የአማራና ኦሮሞ አድርጎ የሚያቀርቡ ዘመዴን ጨምረው አደብ ቢገዙ፣ ተከታዮቻቸውም ይህን ቢያስገነዝቧቸው፣ መሪ ነን የሚሉ በይፋ ወጥተው ቢያወግዙ ወይም በዚህ ደረጃ ህዝብን ከህዝብ በሃይማኖት ለማጫረስ የሚሰሩ አካላት የትግሉ ተባባሪ እንዳልሆኑ ማስታወቅ አስፈልጊ ይምስለኛል።

“የግራኝ መሐመድ ወረራ” በሚል ኦሮሞን እንደ ማህበረሰብ ወራሪ አድርጎ መሳል ኢትዮጵያን የማፍረስ አጀንዳ ያላቸው ሽብር ጠማቂዎችና ስፖንሰር አድራጊዎች ሴራ ነውና “ቢቀርብን” ለማለት እወዳለሁ።

አማራና ኦሮሞን የማጋደል. የማጫረስና ወደ ለየለት ጦነት የማስገባት አጀንዳ የማን አጀንዳ እንደነበር የሚታወቅ ሆኖ ሳለ የአማራ ጥያቄ ላይ አስታኮ ይህንኑ አጀንዳ መስበክ በሰላም እየኖረ ላለው “ወገን” የሚባል ህዝብም አይጠቅምምና በአስቸኳይ እርምት ይወሰድበት። በዘር ፖለቲካ እየላመች ያለቸው ኢትዮጵያ የሃይማኖት ግጭት ከተነሳባት እዛና እዚህ ሳይባል በሁሉም መንደር እሳቱ እንደሚነድ ለአፍታም ጥርጥር የለውም። ይህ የአንድም ፍትህ ጠያቂ አማራ አጅንዳ አይደለም።

አማራ “ተነፈግሁ” ፍትህ ጠየቀ እንጂ “ኦሮሞ፣ ሙስሊምና ዋቄፈታ ልዩ ጠላቶቼ ናቸው ” ብሎ በጅምላ ሲከስ አልተሰማም። አማራ በሁሉም የአገሪቱ ክፍል አሁንም ከሁለኡም ጋር እምነትና ዘር ሳይለየው እየኖረ ነው። የተወሰኑ ሴረኞች የዘል ዕልቂት እንዲነሳ በሚፈጽሙት ወነጀል ሳቢያ አማራን ከሁሉም ወገኖቹ የሚያቅቅሩ አካሄዶች ባስቸኳይ ሊቆሙ እንደሚገባ የማሳስበው ሱዳን ላይ እየሆነ ያለው በኢትዮጵያ ሊሆን የማይችልበት አንድም ምድራዊ ምክንያት ስለሌለ ነው።

መንግስትም ቢሆን ቢያንስ በክልል ደረጃ አማራ ክልል ላይ ሁሉም ወገኖች ተቀምጠው በውይይት ችግራቸውን የሚፈቱበት እግባብ እንዲመቻች ቢያደርግ የተሻለ ይሆናል።

አብዱል ከሪም አህመድ / ነጻ አሳብ


Exit mobile version