ETHIO12.COM

ሰው ሰራሽ ቦይ በመገንባት ቀይ ባህርን መቀላቀል የኢትዮጵያ ሌላ አማራጭ?

አርተፊሻል ቦይ በመገንባት ቀይ ባህርን ወደ ኢትዮጵያ በማምጣት ኢትዮጵያ የባህር በር ሊኖራት ይችላል፤ ይህ በአለም ላይ በኢትዮጵያ የአፋር ምድር ረባዳነት የተነሳ ተፈጥሮ የሰጠው እድል ነው!

በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል አርተፊሻል ቦይ በመስራት ኢትዮጵያ የወደብ ባለቤት መሆን ትችላለች፡፡ እንደዚህ አይነት አጋጣሚ ሊፈጠር የቻለው፤ የኢትዮጵያ የአፋር ቦታ ከባህር ወለል በታች እስከ 110 ሜትር ዝቅ የሚል በመሆኑ ምክንያት ነው፡፡

እንደዚህ አይነት ከባህር ወይም ከውቅያኖስ በዚህ አጭር እርቀት ያነሰ የወለል ዝቅታ (surface elevation) በዚህ ቦታ እንጂ በአለም ላይ የለም፡፡ በዚህ ጥሩ ተፈጥሮ የተነሳ ከቀይ ባህር ጋር ለማገናኘት ቦይ በመስራት ከመገናኘት ባሻገር የጣናን ሶስት እጥፍ የሚረዝም ሐይቅ በድንበሩ መፍጠር ይቻላል፡፡

የሚገነባው ቦይ 470 ሜትር ስፋት የሚኖረው ሲሆን፤ የአለማችን ትልቁን 124 ሜትር ስፋት ያለውን መርከብ በሁለት አቅጣጫ እንዲያስተናግድ በማሰብ እና መርከቡ የሚኖረው 34 ሜ የውሃ ውስጥ ጥልቀት ታሳቢ በማድረግ ነው፡፡ በዚህ መሰረት ቦዩ በአጠቃላይ 470 ሜትር ስፋት እና በትንሹ 50 ሜትር ጥልቀት ሊኖረው ይችላል፡፡

78 ኪሜ እርዝመት እና 470 ሜትር ስፋት ያለው አርተፊሻል ቦይ በሚሰራበት ወቅት፤ የቀይ ባህርን ውሃ ወደ ኢትዮጵያ ለመቀልበስ፤ ከ78 ኪሜ የኤርትራ መሬት ውስጥ 40 ኪሜ ላይ ብቻ የተወሰነ የማይጋነን ጥልቀት ያለው ቁፋሮ (excavation) የሚሰራ ይሆናል፡፡

ይህንን አርተፊሻል ቦይ በመስራት ኢትዮጵያ ከቀይ ባህር ጋር መገናኘት ትችላለች፡፡ ሌላ ወደብ አልባ ሐገር በሚኖረው ተራራማና ከፍ ያለ የመሬት ተፈጥሮ የተነሳ ይህንን እድል ሊያገኝ አይችልም፡፡ ኢትዮጵያ ሌላ የወደብ አማራጭ ከኤርትራ ቢኖራትም ባይኖራትም፤ ይህንን ቦይ መገንባቱ የባህር በር ከማገኘትና ከኢኮኖሚ ጠቀሜታ ባሻገር ለአከባቢው ተፈጥሮ የሚጠቅም ነው ብዬ አስባለው፡፡

የመሬቱን አቀማመጥ (Orginal Ground Level x,y,z OGL data) በሰርቨየር በማንበብ እና የቦይ ግንባታ design manual በመጠቀም በዝርዝር ዲዛይን በማድረግ የግንባታ ወጪውን ተምኖ መገንባት ይቻላል፡፡ እኔ ቦይ አዋጪ በሆነ መንገድ ሊሰራ እንደሚችል እና preliminary design ነው ያቀረብኩት፡፡

ኤርትራ ኢትዮጵያ ላይ ከባህር ዳርቻ አንጻር በበደለችው በደል ላለፉት 30 አመታት ወጣቶቿን ሳዋ ወታደራዊ ማሰልጠኛ እያስገባች፤ ከነገ ዛሬ በኢትዮጵያ ተወረርኩ እያለች በስቅቅ እየኖረች እንደሆነ ይታወቃል፤ ኢትዮጵያም የአሰብ ወደብ የሚገኝበት የአፋር ግዛቷን ለማስመለስ ጥሩ ቀን እየጠበቀች ትገኛለች፡፡

ስለዚህ ያለውን የሁለቱ ሐገሮች ውጥረት በተወሰነ ደረጃ የአርተፊሻል ቦይ ግንባታው ይቀንሳል ብዬ አምናለሁ፡፡ የፕሮጀክት ግንባታ ወጪውም፤ ኢትዮጵያ ለጅቡቲ የምትከፍለውን አመታዊ የወደብ ኪራይ ግማሽ ወይም ሙሉ ቢያክል ነው፡፡ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ እንደ ጥሩ ወዳጅ እና ጎረቤት ሐገሮች ባህሩን በነጻነት ቢጠቀሙ ያተርፋሉ ባይ ነኝ!

በ Andinet Zeleke Bekele.

Exit mobile version