Site icon ETHIO12.COM

ግብጽ ኢትዮጵያን ለማተራመስ አቅሟን ሁሉ ተጠቅማ እየሰራች መሆኑንን ዓለም አቀፍ ጥናት አረጋገጠ

ኢትዮጵያ እንዳትረጋጋ ግብጽ የመጨረሻ አማራጭ አድርጋ እየሰራች መሆኑን አንድ ዓለም አቀፍ ጥናት አመለከተ። ግብጽ ከህዳሴው ግድብ ፕሮጀክት ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያ ውስጥ የብሔርና የሃይማኖት ልዩነቶችን በመጠቀም ሰላምና መረጋጋት እንዳይኖር የመጨረሻ አማራጭ በማድረግ ተግታ እየሰራች መሆኑን ጂዮፖሊቲካል ፊውቸር የተባለ ዓለም አቀፍ ድርጅት ባወጣው ጥናት አመልክቷል።

ለበርካታ ሺህ ዘመናት የአባይ ወንዝ ውሃን ያለምንም ከልካይ ብቻዋን ስትጠቀም የኖረችው ግብጽ ኢትዮጵያ የምታስገነባው ታላቁ የህዳሴ ግድብ የውሃ ድርሻዬን ይቀንስብኛል በማለት ብዙ መልኮች ያሉት አለምአቀፍ ዘመቻዎችን ከከፈተች በርካታ ዘመናት እንደሆናት ያተተው ጥናቱ ሁሉንም ጥረቷን ባለማቋረጥ ኢትዮጵያን የምታዳክምበትና በድርድሩ አሸናፊ ሆና የምትወጣበትን መንገድ ቀይሳለችም ብሏል።

ድርጅቱ በፈረንጆቹ 2021 ላይ ይከሰታሉ ሲል ግምት ከሰጣቸው ወሳኝ ሁነቶች መካከል ኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ ብሄሮች መካከል ሊነሱ የሚችሉ ግጭቶች አቀጣጣይ ሆና የምትሳተፈው ግብጽ ስለመሆኗ አስረጂዎቹን አስቀምጧል። ሰማንያ አምስት በመቶው ከኢትዮጵያ በሚሄደው የአባይ ወንዝ ላይ ግብጽ የውሃውን ባለቤትነት በሚመለከት ከኢትዮጵያ ጋር ውዝግብ ውስጥ መግባት ከጀመረች መቶ አመታት ስለማለፋቸው የሚያትተው ጥናቱ ውዝግቡ ኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብን ከጀመረች በኋላ ይበልጥ እየተካረረና መፍትሄውም እየራቀ መጥቷል ብሏል።ጥናቱ የግድቡን ግንባታ እያፋጠነች ከሱዳንና ከግብጽ ጋር የምትደራደረው ኢትዮጵያ ግድቡን ወደ ማጠናቀቅ እየተቃረበች መሆኑን ገልጿል።

ይሄንን የኢትዮጵያን ተግባር በዝምታ ማየት ያልቻለችው ግብጽ ቀጥተኛ ወታደራዊ እርምጃ በግድቡም ሆነ በኢትዮጵያ ላይ ትወስዳለች ብሎ መገመት ከባድ እንደሆነ የገለጸው ጥናቱ፤ ምናልባት ግብጽ ወታደራዊ እርምጃ እወስዳለሁ ብትል ከኢትዮጵያ የሚሰጣት አጸፋዊ ምላሽ ከባድ ሊሆን እንደሚችልና የግብጽ መንግስት ኢኮኖሚያዊና ውስጣዊ ቁመናም ይሄንን አይነት ነገር ሊቋቋም እንደማይችል አመልክቷል።

ግብጽ ስትራቴጂያዊ ጠቀሜታን መሰረት በማድረግ ሃያላኑን ሩሲያንና አሜሪካን ለማማለል ያደረገቻቸው ሙከራዎች አሜሪካ ከሱዳን ጋር በመስማማቷ ሩሲያ ደግሞ ከአልጄሪያ ጋር ተወዳጅታ ሊቢያ ውስጥ በመግባቷ አልተሳኩም ብሏል።አሜሪካም ሆነ ሩሲያ አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ከግብጽ የሚፈልጉት ነገር ባለመኖሩ ግብጽ የምታነሳው የአባይ ውሃ ጉዳይ በኢትዮጵያ ፣በሱዳንና በግብጽ የሶስትዮሽ ድርድርና ስምምነት ብቻ እንዲቋጭ በማድረግ ገለልተኝነታቸውን ማሳየት እንደሚፈልጉ ነው ጥናቱ የገለጸው ።

ጫና ማሳደር ይችሉ የነበሩት የባህረ ሰላጤው ሃገራትም ከእስራኤል ጋር ስምምነት ላይ በመድረሳቸው ከግብጽ ጋር ያላቸውን ግንኙነት አቀዝቅዘውታልም ብሏል።አሁን ላይ ግድቡን በሚመለከት ከግብጽ ጋር አብራ የቆመች የምትመስለው ሱዳንም የራሷ የሆኑ ውስጣዊና ውጫዊ ጫናዎች ያሉባትና ከድርድሩ ማግኘት የምትፈልገው ውጤት እንዳለ ያተተው ጥናቱ፤ በአፍሪካ ቀንድ ኢትዮጵያን ተጎራብተው አካባቢያቸውን ሰላም ማድረግ ላይ ያተኮሩት ኤርትራ፣ ጅቡቲና ሶማሊያም ከጎረቤታቸው ኢትዮጵያ በተሻለ ግብጽን የሚረዱበት አሳማኝ ምክንያት እንደሌለ ይፋ አድርጓል።

እስካሁን ግብጽ በግልጽ የሚታይ እርምጃ ባትወስድም ኢትዮጵያ በውስጥም ሆነ በውጭ ያጋጠሟትን ፈተናዎች በማክበዱ በኩል በርትታ እየሰራች ስለመሆኑ በትግራይ ክልል የተፈጠረውን ሁኔታ ተከትሎ ኢትዮጵያ ከሱዳን ጋር የገባችበትን የድንበር ውዝግብ እንዲሁም ማነነትን መሰረት ያደረጉ ግጭቶችን ለማሳያነት አንስቷል።የተከሰቱት የብሄር ግጭቶች ከኢትዮጵያ መንግስት ቁጥጥር ውጭ አለመሆናቸውን እንዲሁም ቀጥተኛ ወታደራዊ እርምጃ እንደማያስኬድ የተረዳችው ግብጽ፤ በውስጣዊና ውጫዊ ግጭቶች መብዛት የተነሳ ከሚዳከመው የኢትዮጵያ የመደራደር አቅም የራሷን ፍላጎት ለማሳካት አሁንም በርትታ እየሰራች እንደሆነ ገልጿል።

ጥር 30/2013(ኢዜአ)

Exit mobile version