Site icon ETHIO12.COM

ለጃዋር የሞባይል ሲም ካርዶችን ሊያቀብል ሲል በቁጥጥር ስር ውሏል የተባለው ግለሰብ ዋስትና ተፈቀደለት

በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለጃዋር መሀመድ 4 የሞባይል ሲም ካርድ ሊያቀብል ሲል በቁጥጥር ስር ውሏል የተባለው ግለሰብ ዋስትና ተፈቀደለት፡፡ ተጠርጣሪ ሀምዛ ጀማል አንድ በኦ ኤም ኤን ድርጅት ስም እና 3 በግለሰብ ስም የወጡ ሲም ካርዶችን ለጃዋር መሀመድ ሊያቀብል ሲል በማረሚያ ቤቱ የጥበቃ አባላት በቁጥጥር ስር ውሏል ተብሎ ከአንድ ወር በላይ በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ምርመራ ሲደረግበትና ለአራት ጊዜ ፍርድቤት ሲቀርብ መቆየቱ ይታወሳል፡፡

በምርመራው መርማሪ ፖሊስ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት ምስክር ቃል መቀበሉን ከኢትዮ ቴሌኮም ሲም ካርዱ በማን ሰም ስለመውጣቱ ማስረጃ መሰብሰቡን ገልጾ ነበር፡፡

የምርመራ መዝገቡን ዐቃቤ ህግ እየተመለከተው መሆኑን እና ተጨማሪ ምስክር ለመቀበል ተጨማሪ የምርመራ ቀናትን ጠይቆ የነበረ ሲሆን የተጠርጣሪ ጠበቃ በቂ ጊዜ ተሰጥቷል ተጨማሪ ጊዜ መጠየቁ አግባብ አይደለም ሲል ተቃውሞ ተከራክሮ ነበር፡፡

የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ የጊዜ ቀጠሮ ችሎት መርማሪ ያቀረበው የጊዜ ቀጠሮ ጥያቄ ተጨማሪ ጊዜ  ለመስጠት አሳማኝ ምክንያት አይደለም ሲል አልተቀበለውም፡፡ እስካሁን በምርመራ ቀናት የተከናወኑ ስራዎች በቂ ናቸው ሲል ተጠርጣሪው የ30 ሺህ ብር ዋስ አስይዞ ከማቆያ እንዲፈታ ዋስትና ፈቅዷል፡፡

በታሪክ አዱኛ

Exit mobile version