Site icon ETHIO12.COM

በቅናት ተነሳስቶ የሴት ጓደኛዉን የገደለዉ ኮንስታብል በ15 አመት ፅኑ አስራት ተቀጣ፡፡

ኮንስታብል ገመቹ ቤኩማ የተባለ የፖሊስ አባል በ1996 ዓ.ም ወጥቶ ስራ ላይ የዋለዉን የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ወንጀል ህግ አንቀፅ 539/ሀ ላይ የተመለከተዉን ድንጋጌ በመተላለፍ በፈፀመዉ ድርጊት ተከሶ በእስራት እንዲቀጣ ተወስኖበታል፡፡

የዐቃቤ ህግ የክስ ዝርዝር እንደሚያስረዳዉ ተከሳሹ የአዲስ አበባ ፖሊስ ተወርዋሪ ሀይል ባልደረባ ሆኖ በመስራት ላይ ሳለ ሰዉን ለመግደል አስቀድሞ በማሰብ የስራ ባላደረባዉ የሆነችዉን ሟች ኮንስታብል ታሪኳ ግዛዉ የሴት ጓደኛዉን ከሌላ ጓደኛዬ ጋር አድራ ስትወጣ አየኋት በሚል ምክንያት ቂም ይዞ ድርጊቱን ፈፅሟል፡፡

ተከሳሹ መጋቢት 19 ቀን 2012 ዓ.ም ከጥዋቱ 11፡40 ሲሆን ለስራ ፈርሞ ያወጣዉን ክላሽን ኮቭ ጠመንጃ ከመሰል 30 ጥይት ጋር ይዞና ምቹ ሁኔታን ተጠቅሞ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 04 ክልል ልዩ ቦታው ሻንቅላ ወንዝ ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ አማኑኤል ቤተክርስትያን ጀርባ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ተወርዋሪ ሀይል ሻለቃ መኖሪያ ግቢ ዉስጥ ሟችን ጠብቆ ይዞት በነበረዉ ጠመንጃ አንድ ጥይት ተኩሶ የግራ ጓኗን የመታት ሲሆን ሆዷ ላይ ጉዳት ደርሶባት ደም በመፍሰሱ ምክንያት ህይወቷ እንዲያልፍ ያደረገ በመሆኑ ተከሳሽ በፈፀመዉ ከባድ የሰዉ መግደል ወንጀል ተከሷል፡፡

ክሱን የመሰረተዉ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ዐቃቤ ህግ የሰውና የሰነድ የማስረጃ ዝርዝሮቹን አጠናቅሮ የክስ ሂደቱ ሲያካሄድ ከቆየ በኋላ ተከሳሹ ወንጀሉን መፈፀሙ በቀረቡት ማስረጃዎች ተረጋግጦ ወንጀለኛ ነህ ተብሏል፡፡

በዚሁ መሰረትም ተከሳሹ የፖሊስ አባል ሆኖ ሳለ ሀላፊነቱን ወደ ጎን በመተዉ ድርጊቱን የፈፀመ መሆኑ በቅጣት ማክበጃነት የቤተሰብ አስተዳዳሪ መሆኑ ደግሞ በቅጣት ማቅለያነት ተይዞለት ኮንስታብል ገመቹ ቤኩማ በ15 አመት ፅኑ አስራት እንዲቀጣ ተወስኖበታል፡፡

Federal attorney general Fb

Exit mobile version