Site icon ETHIO12.COM

ለትግራይ ከአዲስ አበባ ክተት ተጠራላት፤ የትግራይ ወጣቶች ቢራ መጠጣታቸው ተወገዘ

“የትግራይ ወጣት ሙሉ በሙሉ ብረት አንስተህ ወደ በረሃ መግባት አለብህ፤ በበረሃው ትግል ከተሸነፍን አንገታችንን ቀና አድርገን መሄድ አንችልም ” ሲል በምርጫ ቦርድ ሰላማዊ ትግል እንዲያደርግ ተፈቅዶለት የምስክር ወረቀት የተሰጠው ባይቶና አመራር ዮሴፍ በርሀ ጥሪ አሰማ። በውል የማይታወቀው ጃል መሮ ብቪኦኤ አማካይነት ለሁለተኛ ጊዜ ማስተባበያ ሰጠ። ኦነግ ሸኔ ከደሙ ንጹህ መሆኑንን ገለጸ።

ዮሴፍ አዲስ አበባ ስሙ በውል ከለተጠቀሰ ሆቴል ሆኖ ተቀማጭነቱ አሜሪካ ከሆነ ከትግራይ ሚዲያ ሃውስ ጋር ባደርገው ቃለ ምልልስ የመከለከያ ሰራዊትን ” ወራሪ” ሲል በተደጋጋሚ ጠርቷል። በትግራይ ከተሞች አዛውንቶች እንጂ ወጣቶች ሊታዩ እንደማይገባ አስታውቋል። በርካታ ወጣቶች ወደ አዲስ አበባ መጉረፋቸው ትክክል ባለመሆኑ ወደ በረሃ እንዲሄዱ የክተት ጥሪ አስተላልፏል። አቶ ጌታቸው ረዳ በርካታ ውጣቶች ወደ በረሃ እየጎረፉና ብዛታቸው ማመን እንደሚያስቸግር መጥቀሳቸው ይታወሳል።

” መሪዎቻችን ተገለዋል፣ ታስረዋል. የተቀሩት በረሃ ናቸው” ሲል ያስታወቀው የባይቶና አመራር በትግራይ ወጣቶች ቢራ ሲጠጡ፣ ሰርግ ሲያደርጉ ማየት እንደሚያሳዝን ገልጾ፣ ጭፈራ ቤቶች መከፈታቸውን አውግዟል። አያይዞም ” በትግራይ ትልልቅ ከተሞቻችን በተለይ መቐለ ወጣቱ ከገዳዬቹ ጋር ዘሩን ሊያጠፉት ከመጡ አብሮ መጠጥ ቤት ጎን ለጎን ተቀምጦ ቢራ ሲጠጣ ይታያል” ብሏል።

“ወጣቱ ወደ ከተሞች እየመጣ ነው አንዳንዱም ይሄው እዚህ አዲስ አበባም መጥቷል የተከፈተብን ጦርነት ዘራችንን ለማጥፋት እንደሆነ የገባውም አይመስልም። እናንተ በውጭ የምታደርጉት ትግል ብቻ በቂ አይደለም ። በረሃ የወጡት አንድ ለሃምሳ ውጊያ እየገጠሙ ትግል ላይ ናቸው። ስለዚህ ወጣት ሁሉ ወደ በረሃ ወጥቶ መታገል አለበት”

” እሱ ከትግራይ ሸሽቶ አዲስ አበባ በሚያምር ሆቴል እየተከፈለው ተቀምጦ ወጣቱን ሊማግድ ክተት ሲያውጅ መንግስት የት ነው? ” ሲል ጋዜጠኛ አርአያ ጠይቆ ” አምስትና አራት ልጆቻቸውን፣ ባሎቻቸውን ያጡ የትግራይ እናቶች ላለፉት አርባ ዓመታት እያነቡ ሲኖሩ ዞር ብሎ ያያቸው የለም። አሁንም ስብሃት ጥፍጥፎ የሰራው የባይቶና ፓርቲ አመራር አዲስ አበባ ተንደላቆ እየኖረ ወታቱን ሊማግድ ጥሪ ያቀርባል። ዛሬም እናቶች ልጆቻቸውን እንዲነጠቁ፣ ቀውሱ እንዲሰፋ አስነዋሪ ቃላቶችን እያሰማ ይቀሰቅሳል” ሲል ኢትዮጵያ ባላት ህግ መሰረት የክተት ጥሪው እንዲመረመር በድጋሚ አሳስቧል።

ይህ እስከታተመበት ድረስ አዲስ አበባ ከተማ ተቀምጦ ክተተ ጥሪ ስላስተላለፈው የባይቶና አመራር ፈቃድ የሰጠው ምርጫ ቦርድም ሆነ የመንግስት የጸጥታና የፍትህ አካላት እስካሁን በግልጽ ያሉት ነገር የለም። ይሁን እንጂ ከተለያዩ ቦታዎች ጦርነቱ መፋፋሙን፣ ድርድር አማራጭ መሆኑንና ጎን ለጎን የክተት ጥሪ የሚሰማው ዘመቻ ቁጥር ሁለት መካሄዱን ተከትሎ እንደሆነ የሚናገሩ አሉ። ሰሞኑንን በርካታ ተዋጊዎችና አመራሮቹን ያጣው ትህነግ የመጨረሻ አመራሮቹ መከበባቸው በመሰማቱ ጥሪው ያለቀ ሰዓት እንደሆነም ተጠቁሟል።

Exit mobile version