Site icon ETHIO12.COM

የኢትዮጵያ ህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም አስተዳደራዊ በደሎች መፈትሄ እንዲያገኙ በማድረግ ሂደት ችግሮች እየገጠሙት መሆኑን ገለጸ

አንዳንድ አስፈፃሚ አካላት በዜጎች ላይ የሚያደርሱትን አስተዳደራዊ በደል ለማስተካከል የሚቀመጡ መፍትሔዎችን ተግባራዊ በማድረግ በኩል ችግሮች እየገጠሙት መሆኑን የኢትዮጵያ ህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ገለጸ፡፡የኢትዮጵያ ህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም የ10 ዓመት መሪ የልማት ዕቅድ ዙሪያ ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትና ሌሎች ባለድርሻ አካለት ጋር በአዳማ እየመከረ ነው።የተቋሙ ዋና ዕንባ ጠባቂ ዶክተር እንዳለ ሃይሌ በውይይቱ ወቅት እንዳሉት ከሁለት አዋጆች የሚመነጭ ከአዋጅ ቁጥር 1142/2011 እና የመረጃ ነፃነት አዋጅ ቁጥር 590/2000 የተሰጠው ስልጣን አለ።

በዚህም መሰረት አስፈፃሚ አካላት በዜጎች ላይ የሚያደርሱትን አስተዳደራዊ በደሎች በመመርመርና የመፍትሔ ሃሳብ በማቅረብ ተፈፃሚ እንዲሆን ማድርግ ይጠበቅበታል።ይሁን እንጂ ተቋሙ የሚሰጣቸው የመፍትሄ ሃሳቦች በብዛት ተፈፃሚ አለመሆናቸውን አብራርተዋል።በዚህም በ2012 ዓ.ም በአስፈፃሚ አካላት የደረሱ አስተዳደራዊ በደሎችን በመመርመር ያስቀመጣቸው የመፍትሄ ሃሳቦች ተፈፃሚ እንዲሆኑ በማድረግ በኩል ስኬቱ 48 በመቶ ብቻ መሆኑን አንስተዋል።ይሄው የማስፈጸም ምጣኔ ባለፉት ስድስት ወራት ወደ 51 በመቶ ከፍ ቢልም ከሚቀርበው ችግር አንፃር አሁንም በቂ እንዳልሆነ አብራርተዋል።

በአስር ዓመቱ መሪ ዕቅድ መሰረት ኢተዮጵያ በአፍሪካ ሞዴል የዕንባ ጠባቂ ተቋም የመፍጠር አላማ ሰንቃለች።ለእቅዱን ስኬታማ ለማድረግ ብዙ ስራዎች ይጠበቃሉ ያሉት ዶክተር እንዳለ ተቋሙን ከማንኛውም ፖለቲካና የመንግሥት አስፈፃሚ አካላት ተፅእኖ ነፃና ገለልተኛ ለማድረግ ሰፊ ጥረት ይጠይቃል ብለዋል።በዚህም የተቋሙ የለውጥ ስራ ነፃና ገለልተኛ እንዲሆን በሚያስችል መንገድ የተደራጀ መሆኑን ገልጸዋል፡፡የኢትዮጵያ ህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ለታችኛው የህበረተሰብ ክፍል ድምጽ የመሆን ሃላፊነትን በመውሰድ የተጠያቂነትን መርህ በመከተል አስፈፃሚ አካላት በግልጽነት መስራታቸውን ይከታተላል፡፡ ኢዜአ

Exit mobile version