አፍሪካ ህብረት የውጭ ምንዛሬ አካውንቱን ወደ ሌላ አገር እንደሚያዘዋውር ተጠቅሶ በህብረቱ ስም የወጣው ዜና ሃሰት፣ ሆን ተብሎ የተቀነባበረ መሆኑን መንግስት አስታወቀ። መረጃው ቀድሞውንም ዜናው “ሴራ” ነው በሚል አስተያየት ከሰጡ ወገኖች ጋር የሚስማማ ሆኗል።
ቀሲስ በላይ መኮንን አፍሪካ ህብረት ቅጥር ግቢው ውስጥ በሚገኘው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቅርንጫፍ ነገሩ ሲነቃ ከተሰወሩ ግለሰቦች ጋር ተገኝተው በሃሰተኛ ሰነድ 6.5 ሚሊዮን ዶላር ክፍያ ሲጠይቁ ፖሊስ በቁጥጥር ስር አውሏቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ መሆኑ ይታወሳል።
በዚሁ መነሻ የአፍሪካ ሕብረት የውጭ ምንዛሪ ሒሳቡን ወደ ሌላ ሀገር ሊያዘዋውር ነው በሚል የተሰራጨው መረጃ “የተሳሳተ” ነው ሲል ይፋ ያደረገው የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ነው።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ነቢዩ ተድላ ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ የአፍሪካ ሕብረት በግቢው ውስጥ በሚገኘው የኢትዮጵያ ንግድ በንክ ሒሳቡ ላይ በሀሰተኛ ሰነድ ገንዘብ ለማዘዋወር የተደረገበትን ሙከራ ተከትሎ “ከሕብረቱ ጋር ባደረግነው ቀጥተኛ ውይይት ይህ አይነት እሳቤ በተቋሙ ውስጥ እንደሌለ የተቋሙ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች አረጋግጠዋል” ሲሉ ብለዋል።
ሪፖርተር በእንግሊዝኛ እትሙ ስማቸው፣ ሃላፊነታቸውና ለጉዳዩ ያላቸውን አግባብነት ሳይጠቅስ የአፍሪካ ህብረት እምነት በማጣቱ የውጭ ምንዛሬ አካውንቱን ወደ ሌላ አገር ለማዘዋወር ማሰቡን አስታውቆ ነበር። ሌሎችም መገናኛዎች ይህንኑ ተከትለው ህብረቱ አካውንቱን በስጋት ከኢትዮጵያ ወደ ሌላ አገር ለማዘዋወር እንቅስቃሴ መጀመሩን በቅብብሎሽ አራብተዋል።
ቃል አቀባዩ ስም ሳይጠሩ እንዳመለከቱት ከሆነ የኢትዮጵያ መንግሥት ከሕብረቱ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ባደረገው ውይይት “በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያለው የድርጅቱ ሒሳብ በአስተማማኝ ሁኔታ እየተጠበቀ እንደሆነ” መናገራቸውን አመልክተዋል። ዜናውን የተከታተሉ ሙከራው ከፍተኛ ሴራ እንደነበር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መግለጫ ያሳብቃል ብለዋል።
የጀርመን ድምጽ ” የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስትያን ከፍተኛ የሥራ ኃላፊ የሆኑት ሊቀ ዐዕላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን ከሳምንት በፊት አዲስ አበባ ውስጥ ተቀማጭ በሆነው አሕጉራዊው ድርጅት የአፍሪቃ ሕብረት ዋና ግቢ ውስጥ በሚገኝ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቅርንጫፍ በመቅረብ፣ ‘ከሕብረቱ የክፍያ ሰነድ ጋር ተመሳስለው የተዘጋጁ’ በተባሉ ሀሰተኛ ሰነዶች በመጠቀም ከሕብረቱ የባንክ ሒሳብ ወደ ሌላ ሒሳብ ከስድስት ሚሊዮን ዶላር በላይ ለማዘዋወር ሲሞክሩ መያዛቸውን ተከትሎ፤ በሀገር ውስጥ ተነባቢ የሆነው The Report የእንግሊዝኛው ጋዜጣ፤ በስም ያልተጠቀሱ የአፍሪቃ ሕብረት የገንዘብ ባለሙያዎችን ዋቢ አድርጎ ሕብረቱ የውጭ ምንዛሪ ሒሳቡን ከኢትዮጵያ ሊያዘዋውር መሆኑን እንደገለፁለት ዘግቧል።” ሲል ሪፖርተርን ዋቢ አድርጎ ዜናውን አራብቷል። መልሶም በመግለጫው መሰረት ዜናውን አመጣጥኗል።
የተፈጠረው ክስተት በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ነባራዊ ሁኔታ ላይ ያስከተለው ተጽዕኖ ስለመኖር አለመኖሩ የተጠየቁት ቃል ዐቀባዩ “ሙከራ ነው። ጉዳዩ በሕግ ያለ ነው። ዝርዝር ልንናገር አንችልም” ሲሉ መልስ ሰጥተዋል።
“የተጽነሰውን ሴራ ዛሬ መንግስት አዋለደው” በሚል አስተያየት ያጋሩ ” በተጠቀሱት የማጭበርበሪያ ሰነዶችና ለዘርፋ በተሰራው ድራማ ብር እንደማይወሰድ የሴራው አቀናባሪዎች ያውቃሉ። ይህን ያላወቁት ወይም ወደፊት አቋማቸው የሚጠራው ቀሲስ በላይ ብቻ ናቸው። ዋናው ዓላማው በኢትዮጵያ ላይ ዲፖላሲያዊ ኪሳራ ማድረስ ነው። ይህ በቅንብር የተሰራ ሴራ እንደሆነ ሃልፊው በዲፕሎማሲያዊ ቋንቋ ነግረውናል። ወደፊትም ተመሳሳይ ዘመቻ ይቀጥላል” ብለዋል።
መንግስት ከህብረቱ የሚመለከታቸው ከፍተኛ ሃላፊዎች ጋር ጥብቅ ውይይት ማድረጉን የሚጠቅሱ ወገኖች፣ የህብረቱ ከፍተኛ ሃላፊዎች በህብረቱ ስም የወጣውን መረጃ አስመክቶ ተመሳሳይ ጥፋት እንዳይሰራ በተዋረድ መመሪያ ማስተላለፋቸው አመልክተዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ነቢዩ ተድላ «ጉዳዩ በሕግ ያለ ነው። ዝርዝር ልንናገር አንችልም። የተሞከረው ጥቃት ግን ከሽፏል። ጉዳዩ ወደ ሌላ ደረጃ ሳያልፍ ወይም ጉዳት ሳያስከትል ለመቆጣጠር ተችሏል» ብለዋል።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ባንክ፣ መብራት ሃይል፣ በመሳሰሉ ተቅማት ላይ “ሴራ ወለድ” ዘገባዎች ወይም መረጃዎችን በማጣመም አገሪቱን በሚጎዳ መልኩ ዜና ማድረግ መለመዱን በርካታ አገራቸውን የሚወዱ በስጋት እየገለጹ ነው።
በቅርቡ ከንግድ ባንክ የዘረፉ ገንዘቡን እንዲመልሱ በተደጋጋሚ ተጠየቀው ፈቃደኛ ያልሆኑት ምስላቸው ይፋ ሲሆን ” እንዴት ምስላቸው ይለጠፋል” በሚል አገሪቱ ላይ ሌብነት እንዲነግስ ሲሟገቱ የነበሩ ሚዲያዎችና የማህበራዊ መድረክ ተዋናያችን በማንሳት ትዝብታቸውን የገለጹ በተደጋጋሚ ” መንግስትን መጥላትና አገርን አሳልፎ መስጠት፣ አገር አለኝ የምትላቸውን ተቋማት ማጠልሸት በአንድ ወቅት አሳፋሪ ታሪክ ይሆናል” በሚል ሃዘኔታቸውን መግለጻቸው የሚታወስ ነው።
የአፍሪካ ህብረት ከኢትዮጵያ እንዲነሳ ሁሉንም ዓይነት ድንጋይ የፈነቀሉ፣ አሁንም ያልተኙ መልካቸውን እየቀያየሩ ሴራ እንደሚያመርቱ የሚገልጹ፣ ይህ መልኩን የሚቀያይረው ዓላማቸው እንዳይከሽፍ ሁሉም ዜጋ ያለ ሃፍረት ሊታገል እንደሚገባ በፓናል ውይይቶችና በተለያዩ አገራዊ መድረኮች በተደጋጋሚ የሚወተወት ጉዳይ ነው።