Site icon ETHIO12.COM

የሰብአዊ መብት ኮሚሽን “የግፍ ደረጃ መዳቢ” – የማይካድራ ምርመራ ላይ ደባ እየተሰራ መሆኑ ተሰማ፤ ኮሚሽኑ ምላሽ ከለከለ

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን የሚባለው ተቋም የማይካድራን ጭፍጨፋና ግፍ አስመልክቶ ግርድፍ የምርመራ ሪፖርት ካቀረበ በሁዋላ ለምን አጠቃሎ ግኝቱን ይፋ እንደማያደርግ ለተጠየቀው ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነም። መረጃው ተሰባስቦ ቢጠናቀቅም የዘገየው ደባ እየተሰራ በመሆኑ እንደሆነ ኢትዮ 12 መረጃ ደርሷታል።

በኢትዮጵያ በአሰቃቂነቱ ይህ ዜና እስከተዘገበበት ድረስ ቀዳሚ እንደሆነ ማረጋገጫ የተሰጠበት የማይካድራ የዘር ማጥፋት ወንጀል “ ሳምሪ” በሚባሉ የትህነግ የወጣቶች አደረጃጀት ታስቦበት፣ በእቅድ ተይዞ፣ ገጀራ እንዲከፋፈል ተደርጎ፣ ሰዎች እንዳያመልጡ መውጪያ መግቢያ ተዘገቶ በትግራይ ልዩ ሃይልና ሚሊሻ ድጋፍ የተፈጸመ ለመሆኑ በቂ መረጃ መቅረቡ አይዘነጋም። ኮሚሽኑም በዚህ ደረጃ ባይሆንም አጠቃላይ ምልከታው ትህነግ ላይ የሚቋጭ የግፍ ወነጀል መሆኑንን አመላክቶ እንደነበር ይታወሳል።

ኮሚሽኑ ከሕዳር 5 እስከ ሕዳር 9 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ በማይካድራ ከተማ እንዲሁም በአብርሀጅራ፣ በሳንጃ፣ በዳንሻ፣ በሁመራ እና በጐንደር ከተማ ተዘዋውሮ ምርመራ በማድረግ የደረሰበትን ግኝት የመጀመሪያ ደረጃ ቀዳሚ ሪፖርት ይፋ ሲያደረግ፣ ” … ጠቅላላ ድርጊቱና ውጤቱ ግፍና ጭካኔ የተሞላበት በሲቪል ሰዎች ላይ የተፈጸመ የጭፍጨፋ ወንጀል ነው” ብሎ የተፈጸመው ግፍ ከፍተኛ የጦር ወንጀልና ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት እንደሆነም አመላክቶ ነበር።

መጀመሪያ ላይ ጥቃቱን የጀመሩት በወልቃይት አማራዎች ላይ መሆኑን የሚገልጸው ወጣት ዳንኤል ንጹሐን ሰዎችን በየመንገዱ እየደበደቡ፤ በሳንጃ አንገታቸውን እየቀሉ ሲገሏቸው ተመልክቻለሁ። ሰው ሮጦ እንዳያመልጥ እንኳን መንገዱ በሚሊሻ ተከቧል። ሩጠው ለማምለጥ የሚሞክሩትን በጭካኔ በጥይት እየመቱ ገድሏቸዋል” ሲሉ ከደቡብ ሰርቶ ለመኖር ወደ አካባቢው የሄዱና ሸሽቶ የመውጣት እድል ያገኙ ነዋሪ ድርጊቱ ምን ያህል የተቀናጀ እንደሆነ መስክረዋል።

“የማይካድራ ጭፍጨፋ ለረጅም ጊዜ የሚቆይ ሰብዓዊ፣ ስነልቦናዊ ቀውስና ጥልቅ ሀዘን ያስከተለ ነው” ሲል የኮሚሽኑ ሃላፊ  ዶ/ር ዳንኤል በአስከፊ መልኩ የሳሉት ይህ ግፍ “ለምን የመጨረሻ ግኝቱ ተዳፈነ?” ሲሉ ጥያቄ የሚያነሱ ከሶስት ሳምንት በፊት ጥቆማቸውን ለኢትዮ12 አቅርበዋል።

“የማይካድራ ጭፍጨፋ ለረጅም ጊዜ የሚቆይ ሰብዓዊ፣ ስነልቦናዊ ቀውስና ጥልቅ ሀዘን ያስከተለ ነው” – ዶ/ር ዳንኤል

ከወንጀሉ ዘግናኝነት የተነሳ ” የጭፍጨፋው ሰለባ ቤተሰቦች ህይወታቸውን እንደቀድሞ ለማስቀጠል አዳጋች ሁኔታ ላይ ናቸው” ያሉት ኮሚሽነሩ ስለምን ጊዜ መግዛት እንደፈለጉ የሚጠይቁ ክፍሎች የአማራ ክልል መንግስትን፣ የተቀናቃኝ ፓርቲ አመራሮችን፣ ጉዳዩን የሚከታተሉ የመንግስት አካላትን፣ አክቲቪስት ነን ብለው በክልሉ ህዝብ ስም የሚንቀሳቀሱትን፣ እንዲሁም በተንታኝነት ማዕረግ ብልጽግናን የተቃወሙ እየመሰላቸው በአማራና በሌሎች ብሄረሰብ አባላት የአካባቢው ነዋሪዎች ላይ የተፈጸመው ዘግናኝ ግፍ እንዲድበሰበስ የየበኩላቸውን አስተዋጾ እያደረጉ መሆኑንን ገልጸዋል።

በማይካድራ ከሺህ በላይ ንጹሃን በሳንጃ መታረዳቸው፣ በየጊዜው አዳዲስ መቃብሮች እንደሚገኙና በቂ ማስረጃዎች እየቀረቡ ባለበት ሁኔታ ጉዳዩን ለማድበስበስ የተኬደበትን አግባብ ” የግፍ ደረጃ መዳቢዎች ደባ” ሲሉ ነው ጥቆማ አቅራቢዎቹ ያስታወቁት።

” ሳልሳዊ ወያነ ትግራይ፣ የታላቋ ትግራይ ብሔራዊ ሸንጎ ባይቶና እና የትግራይ ነጻነት ፓርቲ በጋራ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን የማይካድራ የጅምላ ጭፍጨፋን አስመልክቶ ያወጣው ሪፖርት በተቀረው የትግራይ አካባቢ የከፋ የሰብአዊ መብት ጥሰት እንዲፈጠር አስተዋጽዖ ነበረው ” ማለታቸውን ሰሞኑንን በጀርመን ድምጽ ሚሊዮን ሃይለስላሴና ከመቀለ ያስተላለፈው ዘገባ ያመለክታል።

በማይካድራው የግፍ ጭፍጨፋ ምርመራ የመቸረሻ ግኝት መዘገየት ቅር የተሰኙ ጥቆማቸውን የላኩት የጀርመን ድምጽ ይህን ዘገባ ከማስተላለፉ በፊት ነበር። በዚሁ መነሻ  በማርች 9 በኢሜልና በኮሚሽኑ የፊስቡክ የግል መልዕት ማስቀመጫ ሳጥን ማብራሪያ በዛጎል የድረ ገጽ ጋዜጣ ስም ማብራሪያ እንዲሰጠን ጠይቀን ነበር።

ጥቆማ የሰጡን ወገኖች የማይካድራን ጭፍጨፋ ፈጻሚዎች የአማራ ልዩ ሃይልና የመንግስት ታጣቂዎች እንደፈጸሙት ለማስመሰል ሱዳን ከሚገኙ የሳምሪ አባላት መካከልና ሊታመኑ ይችላሉ ከሚባሉ አዛውንት የትግራይ ሰዎች ለምስክርነት መዘጋጀታቸውን፣ ለዚህም ስልጠና መውሰዳቸውን ጠቁመዋል። ከዚሁ ጋር ጎን ለጎን አቅጣጫውን ለማሳት የሚዲያ ዘመቻ ጎን ለጎን እንደሚጀምሩ፣ እንዲሁም ይህ ዘመቻ ከአክሱሙ የኮሞሽኑ ምርመራ ይፋ ከሆነ በሁዋላ የቀድሞ ቅድመ ሪፖርትን እንዲቃረን ለማድረግ የታሰበ ነው።

በማርች 21 የጀርመን ድምጽ እንደዘገበው የትግራይ ተቀናቃኝ ፓርቲ ናቸው የሚባሉት  … ሳልሳዊ ወያነ ትግራይ፣ የታላቋ ትግራይ ብሔራዊ ሸንጎ ባይቶና እና የትግራይ ነጻነት ፓርቲ በጋራ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን የማይካድራ የጅምላ ጭፍጨፋን አስመልክቶ ያወጣው ሪፖርት በተቀረው የትግራይ አካባቢ የከፋ የሰብአዊ መብት ጥሰት እንዲፈጠር አስተዋጽዖ ነበረው፤ ሪፖርት  ሚዛናዊ አይደለም። ኮሚሽኑ ገለልተኛ ባለመሆኑ ከተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ጋር በህብረት መስራራቱን እንደሚቃወሙና የማይካድራው ቅድመ ምርመራ አግባብነት እንደሌለው ነበር ያስታወቁት።

ኮሚሽኑ እያከናወነ ያለውን ተግባር በማድነቅ በላክነው የማብራሪያ ተማጽኖ የማይካድራው ሪፖርት እንዲዘገይ ለምን ተደረገ? ተኝታችሁበታል ይባላል? ቅድሚያ ለሌሎች የሰብአዊ መብት ጥሰቶች የሚሰጠው በምን መስፈርት ነው? የመከላከያ ሰራዊት ላይ የተፈጸመው ጭፍጨፋስ “ግፍ” ላለመባልና በልዩ ዝግጅት ራሱን ችሎ እንዲሰራ ያልተደረገው ለምንድን ነው? የሚሉና መስለ ጥያቄዎች ብናነሳም ኮሚሽኑ ምላሽ አልሰጠም። ሁለት ሳምንታት ብንጠብቅም ደግመን ብናሳስብም አዲስ ነገር መስማት አልቻልንም። የትግራይ ተቃዋሚ ፓሪዎች ላነሱት ተቃውሞ  የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን አማካሪና ቃል አቀባይ አቶ አሮን ማሾ አጠቃላይ ማስተባበያ ከሰጡ በሁዋላ ተቃውሞ ስለቀረበበት የማይካድራ ሪፖርት ” የማይካድራ ሪፖርት ቅደመ ሪፖርት ነው። ማጣራቱ በደንብ ሲጠናቀቅ ሙሉ ሪፖርት ይወጣል” የሚል ምላሽ አቅርበዋል። ይህንን ተከትሎ አንድም የአማራ አክቲቪስት፣ ክልል ሃላፊዎች፣ የትቀናቃኝ ፓርቲዎችና ያገባናል ባዮች ምላሽ እንዲሰጡ አልተጋበዙም ወይም ራሳቸውን ችለው ምላሽ ሲሰጡ አልተሰሙም።

አቶ አሮን የማይካድራው ጭፍጨፋ ሪፖርት ጅምር እንጂ ሙሉ ስዕል የሚሰጥ እንዳልሆነ በገደምዳሜ ጠቆም አድረገው በሰጡበት ምላሽ  የአክሱም የምርመራ ግኝት በቅርቡ ይፋ እንደሚሆን ተናግረው ነበር። በ 21.03.21 ይህንን ብለው በ25.03.21 ሪፖርቱ ይፋ ሆኗል። እነ አምነስቲና ሲኤን ኤን የቀረቡትን ሪፖርት የደገመው የኮሚሽኑ ሪፖርት ፈጣን መሆኑ ተመስግኗል።

በግፍ መጠኑ፣ በተጎጂዎች ብዛት፣ በወንጀሉ ኩነትና ቅንብር እንዲሁም ዘግናኝነት ትልቅ ስለተባለው የማይካድራ ጭፍጨፋ መዘገየት ሃሳብ የገባቸው እንደሚሉት የማይካድራው የግፍ ጭፍጨፋ መልኩን እንዲቀይር፣ መነሻ ምክንያቶቹ የአማራ ክልል ልዩ ሃይሎች እንደሆኑ ተደርጎ እንዲቀርብና ከሰላም ማስከበሩ በሁዋላ ተመፈጸሙ የተባሉ የፍትህ ጥያቄዎች እንዲገቡበት እየተደረገ ነው።

ይህንኑ የሚያመላክት አንዳንድ ቅድመ መረጃዎች ለኮሚሽኑ ቅርብ በሆኑና ለውጭ አገር ጋዜጠኖች በአስተርጓሚነት በሚሰሩ አንዳንድ አካላት በአስተያተት መልክ በማህበራዊ ገጾች እየተዘዋወሩ መሆናቸውንም ጥቆማ የሰጡት ወገኖች አስታውቀዋል።

ጥቆማ ሰጪዎቹ እንደሚሉት ዶክተር ዳንኤል ኢትዮጵያን በዋናነት ለማጥፋት ከምትሰራዋ አገር እንግሊዝ መምጣታቸው ዛሬ ዛሬ ጥያቄ እየሆነባቸው ነው። ከዚህም በላይ በዶክተር ዳንኤል መለኪያ ግፍ እንዴት ደረጃ እንደሚወጣለት ግልጽ አይደለም። ለዚህም ይመስላል ” የግፍ ደረጃ መዳቢ” ሲሉ ኮሚሽኑ ራሱን እንዲያይ ያሳሰቡት። ማሳሰብ ብቻም ሳይሆን ” የሰብአዊ መብት ተቆርቋሪነት ስራ ልክ እንደ ሃይማኖት መሪነት ስራ የህሊና መቀደስን የሚጠይቅ፣ ለህሊና መገዛትንና እውነትን የማክበር ሃላፊነት ነው” ሲሉም ገልጸዋል።

ዝግጅት ክፍላችን ኮሚሽኑ መረጃ መስጠት አንዱ የሰብአዊ መብት አካል መሆኑንን ተረድቶ ምላሽ ከላከለን የምናትም እንደሆነ ከወዲሁ ለመግለጽ እየወደድን ” የግፍ ደረጃ መዳቢ” በሚል የቀረበው አግባብ ትክክል ሆኖ እንዳገነነው ለመግለጽ እንወዳለን።

Exit mobile version