Site icon ETHIO12.COM

በንፁኃን ደም መነገድ ይቁም! በንፁኃን ደም መነገድ ይቁም! በንፁኃን ደም መነገድ ይቁም!

ኢትዮጵያ ውስጥ የንፁኃን ዕልቂት የሚቆመው መቼ ነው? ይህንን መረን የለቀቀ ፍጅት ከማውገዝና ሐዘን ከመቀመጥ በዘለለ፣ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማስቆም እንዴት ያቅታል? የወገኖቻችን ዕልቂት በአራቱም ማዕዘናት አልቆም ብሎ ድንጋጤ፣ ሐዘን፣ ተስፋ መቁረጥና ንዴት ሲፈራረቁ ከየት ወዴት እየተሸጋገርን ነው ተብሎ መጠየቅ የለበትም ወይ? በአንድ ሥፍራ የሚፈጸም ፍጅት ከንዴትና ከቁጭት አልፎ፣ በሌላ ሥፍራ ወደ በቀል ቢሸጋገር አገር መፍረሷ እኮ ነው፡፡ ውስጣዊ የፖለቲካ ችግርን ሥርዓት ባለው መንገድ መፍታት ያልቻሉ ኃይሎች፣ የፖለቲካዊ ቁማራቸውን በንፁኃን ደም እያወራረዱ ኢትዮጵያ ቁምስቅሏን እያየች ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ምኅዳር ውስጥ ጡንቻን አፈርጥሞ በመውጣት ሁሉንም ነገር ለመቆጣጠር በሚደረግ ሽኩቻ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በማንነት ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች ዕልቂት ከመጠን በላይ እየተለመደ ነው፡፡ ይህ ጉዞ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊያንን የት ያደርስ ይሆን ተብሎ አይታሰብም ወይ? ከሥልጣናቸው ውጪ የአገር ጉዳይ ምንም የማይመስላቸው ኃይሎች ምንድነው የሚፈልጉት? ኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶቿ ከያሉበት ተጠራርተው መከራ በደገሱላት በዚህ ወቅት፣ አቅሟ እንዲዳደከምና እጇን በቀላሉ እንድትሰጥ ለምን ተፈለገ? በታላቁ የህዳሴ ግድብ ምክንያት መላ ትኩረቷን ኢትዮጵያ ላይ ያደረገችው ግብፅ፣ በውስጥ ወኪሎቿ አማካይነት ኢትዮጵያዊያንን እርስ በርስ እያስተራረደች መሆኗ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ ታዲያ ለምን ይሆን ኢትዮጵያን አደገኛ ምዕራፍ ውስጥ የሚከቱ ደባዎች እየተፈጸሙ ንፁኃን የሚያልቁት? በንፁኃን ደም መነገድ መቆም አለበት፡፡

በሌላ በኩል በገዥው ፓርቲ ብልፅግና የአማራና የኦሮሚያ ቅርንጫፎችና በሚመሩዋቸው ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥታት ሹማምንት መካከል የሚስተዋሉ ኃላፊነት የጎደላቸው መግለጫዎች፣ አስቸኳይ የእርምት ዕርምጃ ካልተወሰደባቸው ችግሩ ተስፋፍቶ አገረ መንግሥቱን ሊያተራምስ ይችላል፡፡ በዚህ አደገኛ ወቅት እየተፈጸሙ ያሉ ጥቃቶችንና ዕልቂቶችን በጋራ በማውገዝ በጋራ የአፀፋ ዕርምጃ መውሰድ ሲገባ፣ በተለያዩ ደረጃዎች ባሉ ካድሬዎች በሚተላለፉ ነውጠኛ ቅስቀሳዎች ተጨማሪ ጉዳቶችን ማስከተል ጤነኝነት አይደለም፡፡ አንድ ፓርቲ ውስጥ የተጠለሉ ሁለት ተቀናቃኝ ኃይሎች በሚያደርጉት የሥልጣን ትንቅንቅ ንፁኃን እያለቁ፣ ቤተሰቦቻቸው በሐዘን እየተቆራመዱና ኢትዮጵያዊያን ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ውስጥ ሆነው እያነቡ ሌላ ዙር ግጭቶችን መጠንሰስ ወንጀል ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ተቆጥረው የማያልቁ በርካታ ችግሮች እንዳሉ ለማንም እንግዳ ነገር አይደለም፡፡ እነዚህን ችግሮች የሚረዳ ማንኛውም ቅን ዜጋ ባሉት ላይ ሌላ ከመጨመር ይልቅ፣ ችግሮቹ ደረጃ በደረጃ እንዴት ቢፈቱ ይሻላል በማለት ለመፍትሔ የሚረዱ ሐሳቦችን ነው የሚያቀርበው፡፡ በሌላ በኩል ግን ከዚህ በተቃራኒ ባሉት ችግሮች ላይ ተጨማሪ ችግሮችን እየቀፈቀፉ፣ አገርን ቁምስቅሏን የሚያበዙ በመበርከታቸው ከግጭት አዙሪት ውስጥ መውጣት አልተቻለም፡፡ ለአገርና ለሕዝብ ፋይዳ የሌላቸው ፖለቲከኞች፣ አሁንም ድረስ በቀላሉ ሊፈቱ የሚችሉ ችግሮችን እያጦዙ አገር ያምሳሉ፡፡ በዚህ ጦስም ንፁኃን በማንነታቸው ምክንያት ብቻ ሕይወታቸውን ይገብራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ምድር ሁከት፣ ጥቃት፣ ግድያና ማፈናቀል የዘወትር ተግባር እየሆኑ ያሉት፣ አብዛኞቹ ፖለቲከኞች የግጭት ነጋዴዎች ስለሆኑ ነው፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) መንግሥት የሕዝቡን ሰላምና ደኅንነት የማስከበር ኃላፊነት ሲኖርበት፣ የአገርን ብሔራዊ ደኅነነት የማስጠበቅ ግዴታም አለበት፡፡ ይህንን ኃላፊነቱን ለመወጣት ደግሞ በሕግ የተሰጠው ሥልጣን አለው፡፡ በዚህ ሥልጣኑ ሕግና ሥርዓት ማስከበር ግዴታው ነው፡፡ ምንም እንኳ መንግሥት ኃላፊነቱን በአግባቡ ለመወጣት ብልኃትና ጥበብ ቢያስፈልገውም፣ ሕግ የማስከበር ተግባሩ ግን ፈፅሞ ለድርድር መቅረብ የለበትም፡፡ የዜጎችን መብቶችና ነፃነት የማክበር ሥራው ሳይዘነጋ፣ ሕገወጥ ድርጊቶችን በሕግ አደብ ማስገዛት የግድ ነው፡፡ በተለይ የአገርን ሰላም የሚያናውፅ፣ የዜጎችን ሕይወትና ንብረት አደገኛ ሁኔታ ውስጥ የሚከት ድርጊት ሲያጋጥም ኃላፊነትን መዘንጋት ያስጠይቃል፡፡ በዚህ ጊዜ በርካቶች ኦነግ ሸኔ የሚባለው ታጣቂ ኃይል እንዴት ከመንግሥት አቅም በላይ ሆነ ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡ በመንግሥትም ሆነ በገዥው ፓርቲ መዋቅሮች ውስጥ ለኦነግ ሸኔ ድጋፍ የሚሰጡ ቢኖሩ እንጂ፣ የዚህ ኃይል ጥቃቶች አድማሳቸውን እያሰፉ አገር ወደ ማፍረስ አያመሩም ነበር ይላሉ፡፡ ኦነግ ሸኔ የሚባለው ኃይል የገዥው ፓርቲ ፖለቲከኞች ድጋፍ እንደሌለው በተግባር ማሳየት ካልተቻለ፣ ሁኔታው ወደ አደገኛ ምዕራፍ እየተሸጋገረ እንደሚሄድ መጠራጠር እንደማይገባም ያሳስባሉ፡፡ መንግሥት ሆይ የንፁኃን ደም በከንቱ እየፈሰሰ የት ነው ያለኸው?

የኢትዮጵያን ሰላም በማደፍረስ ከፍተኛ ሚና የሚጫወቱ ኃይሎች ስለመኖራቸው በተደጋጋሚ ብዙ ተብሎበታል፡፡ በማኅበራዊ የትስስር ገጾች ሐሰተኛ መረጃዎችንና ምሥሎችን ከሚያሰራጩ ጀምሮ፣ እጃቸውን በማስረዘም ግጭቶችን በገንዘብና በተለያዩ መንገዶች የሚያበረታቱ አሉ፡፡ እነዚህ የራሳቸው ጥቅም እንዳይጓደል ተግተው የሚሠሩ ኃይሎች፣ የእነሱ ዓላማ እንዲሳካ ማንኛውንም ድርጊት ይፈጽማሉ፡፡ ኢትዮጵያዊያንን በብሔር ከፋፍለው ከማጋጨት አልፈው፣ ቤተ እምነቶችን እያቃጠሉ የሃይማኖት ጦርነት ለማስነሳት ሰይጣናዊ ድርጊቶችን ፈጽመዋል፡፡ ከዚህ ቀደም በማኅበረሰቡ ውስጥ የነበሩ መልካም እሴቶችን በመሸርሸር ጥርጣሬና አለመተማን እየፈጠሩ ነው፡፡ የብዙኃኑን ዝምታና ችላ ባይነት እንደ ጥሩ አጋጣሚ በመጠቀም፣ ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ አጥፊ ቅስቀሳዎችን ያደርጋሉ፡፡ ሐሰተኛ ወሬዎችን እየፈበረኩ ይነዛሉ፡፡ ማመዛዘን የማይችሉ ግለሰቦችን እየተጠቀሙ ሁከት ያስነሳሉ፡፡ በስሜት እየኮረኮሩ ለውድመት ያሰማራሉ፡፡ ለዘመናት ተሳስሮ የኖረውን ሕዝብ ለማለያየት አስፀያፊ ስድቦችን ያሠራጫሉ፡፡ ቁጡዎችንና በስሜት የሚነዱትን ለአፀፋ እያዘጋጁ ግጭት ይቀሰቅሳሉ፡፡ እውነቱን እንነጋገር ከተባለ እነዚህ ኃይሎች ይታወቃሉ፡፡ ምን እንደሚፈልጉ ጭምር ይታወቃል፡፡ አገርን ማረጋጋት ከተፈለገ ሕጋዊ መንገዶችን በሚገባ መጠቀም ይቻላል፡፡ ለአገር ህልውና ሲባል ሕጋዊ ዕርምጃ መውሰድ ተገቢ ነው፡፡ ሕዝብም በየአቅጣጫው መንግሥትን እየጠየቀ ያለው ይህንን ነው፡፡

ከመስከረም 2011 ዓ.ም. የቡራዩ ጥቃት ጀምሮ እስከ ሰሞኑ የወለጋና የመተከል ዕልቂት ድረስ የነበሩትን ጭፍጨፋዎችና ውድመቶች በአንክሮ ለሚከታተል ማንኛውም ዜጋ፣ ለሰላማዊ የፖለቲካ ፉክክር ጀርባቸው የሰጡ አክራሪ ብሔርተኛ ድርጅቶች አመራሮችና ደጋፊዎች ምን ዓይነት ድርጊቶችን ያከናውኑ እንደነበር ግልጽ ይሆንለታል፡፡ በተለያዩ የፓርቲ ሚዲያዎችና የማኅበራዊ ትስስር ገጾች ይተላለፉ የነበሩ ቅስቀሳዎችና መልዕክቶች ኢትዮጵያዊያንን በመከፋፈል ማጣላት፣ የማዕከላዊ መንግሥቱን አቅም በማዳከም የክልሎችን መዋቅሮች ማፈራረስ፣ የብሔር አባል ያልሆኑ ማኅበረሰቦችን መግደል፣ መዝረፍና ማፈናቀል፣ ለዘመናት አብረው የኖሩ አማኞችን በሃይማኖት ለማጣላት መስጊዶችንና አብያተ ክርስቲያናትን ማቃጠል፣ ገለልተኛ መሆን የሚገባቸው የፀጥታ አካላት ውስጥ ሰርጎ በመግባት የዓላማ አስፈጻሚ ለማድረግ መሞከር፣ በታዋቂ አክቲቪስቶቻቸው አማካይነት ኢትዮጵያዊነትን የሚያመክኑ የማያቋርጡ ሐሰተኛ የታሪክ ትርክቶችን ማነብነብ፣ ወዘተ የተለመዱ ድርጊቶች ሆነው ነው የዘለቁት፡፡ በሰው አገር በሥርዓት እየኖሩ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ዕልቂትና ውድመት እንዲደርስ የሚፈልጉ ብሔርተኞች ሳይቀሩ፣ ኢትዮጵያን የማፈራረስ ዘመቻ አካል መሆናቸውን ከተደጋጋሚ ቅስቀሳዎቻቸው በሚገባ ለመታዘብ ተችሏል፡፡ ይህ ሁሉ የሥልጣን ጥመኞችና አገር አፍራሾች አረመኔያዊ ድርጊት፣ ኢትዮጵያ በኮሮና ወረርሽኝና በህዳሴ ግድቡ ምክንያት ከግብፅ ጋር በተናነቀችበት ወቅትም ሊረግብ አልቻለም፡፡ የእነዚህ ኃይሎች ዋነኛ ዓላማ ኢትዮጵያን በመበታተን የግንጠላ መርሐ ግብራቸውን ለማሳካት በመሆኑ፣ ከኋላቸው ደግሞ ታሪካዊ ጠላት የሆነችው ግብፅ አለችበት፡፡ የውስጥ ተላላኪዎች ንፁኃንን እየገደሉ አገር የሚያተራምሱት የግብፅ ተከፋይ ስለሆኑ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዳር እስከ ዳር መንቃት አለበት፡፡ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ አገር አፍራሾችን በማሳፈር ታሪክ መሥራት ይጠበቅበታል፡፡

ታሪካዊ ጠላቶች ኢትዮጵያውያንን የሚከፋፍሉትና የሚያፋጁት በውስጥ ተላላኪዎች አማካይነት እንደሆነ መገንዘብ ይገባል፡፡ አሁንም የተፈለገው ይህንን አንድነት በመበተን ኢትዮጵያዊያንን በብሔርና በሃይማኖት ጭምር እርስ በርስ ማባላት ነው፡፡ ከአሁን በኋላ በታሪካዊ ጠላቶች ረቂቅ ሴራ ላለመበለጥ አንድነትን ማፅናት የግድ ይላል፡፡ ምንጫቸው የማይታወቅ ከፋፋይና በታኝ ወሬዎችንና አሉባልታዎችን በማስወገድ፣ በንቁ አዕምሮ የታሪካዊ ጠላቶችን አፍራሽ ፕሮፓጋንዳዎች ማምከን ያስፈልጋል፡፡ ዘወትር እየተታለሉ እነሱ ወጥመድ ውስጥ መውደቅ ማብቃት አለበት፡፡ ኢትዮጵያ የምትጠናከረው በልጆቿ አንድነት ብቻ እንደሆነ በተግባር ማረጋገጥ ይገባል፡፡ ኢትዮጵያን ከግጭትና ከውድመት ነፃ ለማድረግ ይህ ትውልድ ትልቅ ኃላፊነት እንዳለበት መተማመን ያስፈልጋል፡፡ መንግሥት ኦነግ ሸኔ የሚባለው ኃይል እንደማያቅተው የታወቀ ስለሆነ ውስጡን ይፈትሽ፡፡ በመንግሥት ድክመት ንፁኃን በማንነታቸው ምክንያት እየታደኑ ማለቅ የለባቸውም፡፡ ኦነግ ሸኔ የሚባለው ኃይል ከማንም በላይ ሆኖ አይደለም ንፁኃንን በማንነታቸው ምክንያት እየፈጀ ያለው፡፡ መንግሥትና ገዥው ፓርቲ ውስጥ የተሰገሰጉ ኃይሎች እጃቸው በንፁኃን ደም እየጨቀየ ነው፡፡ መንግሥት በአስቸኳይ ውስጡን አጥርቶ ለፍርድ ያቅርባቸው፡፡ በንፁኃን ደም መነገድ ይቁም!

Reporter Amharic edotrial


Exit mobile version