Site icon ETHIO12.COM

ከአዲስ አበባ ውጪ ባሉ አካባቢዎች ከኮቪድ-19 ጋር በተያያዘ ጥብቅ ቁጥጥር እንደሚደረግ ተገለጸ

ከዚህ በፊት በነበረው መረጃ አብዛኛው ሥርጭት የሚከሰተው አዲስ አበባ ውስጥ እንደነበር የገለጹት ዶክተር ደረጀ፤ ካለፉት ሁለት ሳምንታት ወዲህ ግን በክልሎች የቫይረሱ ወረርሽኝ እየተስፋፋ መምጣቱን አመልክተዋል። በአንዳንድ የክልል ከተሞች ከሚመረመሩ ቫይረሱ የሚገኝባቸው ከ30 በመቶ በላይ ሆኗል ብለዋል።

ከአዲስ አበባ ውጪ የኮቪድ 19- ጥንቃቄ 10 በመቶ ብቻ መሆኑ ተጠቆመ

እየተባባሰ የመጣውን የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ለመከላከል ከአዲስ አበባ ውጪ ባሉ የክልል አካባቢዎች ጥብቅ ቁጥጥር ሊደረግ መሆኑን የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ። የኮቪድ-19 ፕሮቶኮልን አጠባበቅ በአዲስ አበባ 70 በመቶ ፣ ከአዲስ አበባ ውጭ ባሉ የክልል አካባቢዎች 10 በመቶ መሆኑም ተጠቆመ። የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ በተለይም ለአዲስ ዘመን እንደገለጹት፤ ከአዲስ አበባ ውጪ ባሉ የክልል አካባቢዎች የሚታየውን ከፍተኛ መዘናጋት ለመቅረፍ ጥብቅ ቁጥጥር ይደረጋል።

ለዚህም ከክልል እስከ ቀበሌ ድረስ ካሉ አመራሮችና የፀጥታ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው። በየአካባቢው ያሉ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ያላደረገ ሰው ማስተናገድ እንደሌለባቸው ያመለከቱት ዶክተር ደረጀ ፣ ወረርሽኙን ለመከላከል የተቀመጡ የክልከላ ህጎችን ያላከበረ የትኛውም የአገልግሎት ሰጪ ተቋም እስከመዘጋት ይደርሳል ብለዋል። እንደ ዶክተር ደረጀ ገለጻ፤ በሁሉም አካባቢዎች ኮቪድ-19 አስከፊ ደረጃ ላይ ደርሷል። በተለይም ከተሞች አካባቢ ሥርጭቱ ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ ነው። በቀን በአማካኝ እስከ አንድ ሺ 500 ሰዎች ቫይረሱ እየተገኘባቸው ነው።

ከባለፈው ሳምንት ጋር ሲነፃፀር አሃዙ በእጥፍ ጭማሪ አሳይቷል። በህክምና ማዕከላትም የፅኑ ህሙማን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን ያመለከቱት ዶክተር ደረጀ ፣ በአሁኑ ወቅት የኮቪድ-19 ምርመራ ከሚወስዱ ውስጥ 26 በመቶ የሚሆነው ቫይረሱ እንደሚገኝባቸው አስታውቀዋል። ከዚህ በፊት በነበረው መረጃ አብዛኛው ሥርጭት የሚከሰተው አዲስ አበባ ውስጥ እንደነበር የገለጹት ዶክተር ደረጀ፤ ካለፉት ሁለት ሳምንታት ወዲህ ግን በክልሎች የቫይረሱ ወረርሽኝ እየተስፋፋ መምጣቱን አመልክተዋል። በአንዳንድ የክልል ከተሞች ከሚመረመሩ ቫይረሱ የሚገኝባቸው ከ30 በመቶ በላይ ሆኗል ብለዋል።

በክልል አካባቢዎች ሥርጭቱ እየተስፋፋ የመጣው በመዘናጋት መሆኑን ያመለከቱት ዶክተር ደረጀ ፣ ቫይረሱ አዲስ አበባ ውስጥ ብቻ ያለ እስከሚመስል ድረስ የጥንቃቄ ጉዳይ የተረሳ መሆኑን አስታውቀዋል።ጤና ሚኒስቴር ባለፈው ሳምንት ባደረገው የዳሰሳ ጥናት የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ አጠቃቀም፣ የእጅ መታጠብ፣ እና የሳኒታይዘር አጠቃቀም ዝቅተኛ ሆኖ መገኘቱን ጠቁመው ፣ በአንዳንድ አካባቢዎች ጭራሹንም የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ እንደማይታይ አመልክተዋል።

‹‹በመከላከል ሂደቱ ላይ የአመራር ድክመት ታይቷል›› ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ከዚህ በኋላ በየደረጃው የተቋቋመው ግብረ ሃይል ከፍተኛ ቁጥጥር ያደርጋል ብለዋል። አመራሩን ለማንቃት ከጤና ሚኒስቴርና ከኢትዮጵያ የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ጋር እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። የፖሊስ አካላት የጤና ሚኒስቴርና ጠቅላይ አቃቤ ህግ ባወጡት መመሪያ መሰረት የወጡ ህጎችን እንዲያስፈጽሙ አቅጣጫ መሰጠቱን ገልጸዋል።

ለስድስተኛው አገር አቀፍ ምርጫ በሚደረግ የፓርቲዎች ቅስቀሳ ላይም ሆነ ሌሎች ህዝብ የሚበዛባቸው ቦታዎች ላይ ተገቢው ጥንቃቄ እንደሚደረግ ሚኒስትር ዴኤታው አመልክተው፣ የወጡ የክልከላ ህጎችን የተላለፈ የመንግስትም ይሁን የግል አካል በጥፋቱ ልክ የእርምት እርምጃ ይወሰድበታል ብለዋል። በሚዘጋጁ መድረኮች ላይ ተገቢው ጥንቃቄ መደረጉን የሚከታተል ግብረ ሃይል ተቋቁሟል። የህግ ማስከበር ሥራውም በፀጥታ አካሉ ብቻ ሳይሆን በጤና ባለሙያዎችም ክትትል እንደሚደረግበት ሚኒስትር ዴኤታው ጠቁመዋል።ክትባቱ ምንም አይነት ተጓዳኝ ህመም ለሌለባቸው ከ65 ዓመት በላይ ለሆኑ ሰዎች እንደሚሰጥ ጠቁመው ፣ ከ54 እስከ 64 ዓመት ላሉት ግን የሚሰጠው ተጓዳኝ ህመም ላለባቸው ነው ብለዋል። ክትባቱ ባለፈው ሰኞ መጀመሩንም አስታውቀዋል።

ዋለልኝ አየለ – አዲስ ዘመን

Exit mobile version