ETHIO12.COM

በአዲስ አበባ በ300 ሚሊዮን ዶላር እጅግ ዘመናዊ የተባለ ሆስፒታል ግንባታ በይፋ ተጀመረ

May be an image of one or more people, people standing and outdoors

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ በአዲስ አበባ ከተማ በ300 ሚሊዮን ዶላር 12 ቢሊዮን ብር ወጪ ዘመናዊ አለም አቀፍ ደረጃውን የተጠበቀ ሆስፒታል ግንባታ በይፋ አስጀመሩ፡፡

በሮሃ ሜዲካል ካምፓስ ኃ.የተ.የግ.ማ አማካኝነት በአዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 13 በተለምዶ አድዋ ፓርክ ተብሎ በሚጠራው ቦታ 300 ሚሊዮን ዶላር /ከ12 ቢሊየን ብር ባላይ ወጪ የህክምና መንደር ግንባታ በይፋ ተጀምሯል፡፡በመርሐግብሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እንዳስታወቁት ሆስፒታሉን ግንባታ እውን ለማድረግ አስተዋጽኦ ላበረከቱት አካላት ምስጋና አቅርበዋል ።የሮሃ ህክምና ማዕከል ተጨማሪ እና በህክምናው ዘርፍ ብቁ የሆኑ ባለሙያዎችን ለማፍራት ያግዛል ብለዋል ።

ቦታ አጥሮ መቀመጥ አይቻልም ያሉት ዶክተር አብይ አህመድ ሆስፒታሉ በተቀመጠለት ጊዜ እንዲያልቅ አስፈላጊውን ክትትል ይደረጋል ብለዋል።አያይዘውም ከህክምና ማዕከል ግንባታ ጎን ለጎን መከላከልን መሰረት ያደረገ የጤና ስርዓት ተግባራዊ እንዲሆን በከተማዋ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ምቹ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራ እንዲገነባ አሳስበዋል ።ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ በሆስፒታሉ የመሰረተ ድንጋይ ማስቀመጥ ስነስርዓት ላይ እንደገለፁት የተያዘውን የብልፅግና ጉዞ የሚሰምረው ጤናማ ማህበረስብ መገንባት ስንችል ነው ብለዋል ።

ይህን ጤናማ ማህበረሰብ ለመገንባት ደግሞ የጤና ተቋሞቻችንን በሰለጠነ የሰው ኃይልና ቁሳቁስ ከማሟላት ባሻገር ፣ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆስፒታሎችን መገንባትና ለአገልግሎት ማብቃት ይደር የማይባል ስራ መሆኑን በመረዳት በከፍተኛ ትኩረት በመስራት ላይ እንደሚገኙ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ገልጸዋል ፡፡

ይህ ፕሮጀክት ለከተማዋ ነዋሪዎች ብቻ ሳይሆን፣ ወደ ከተማዋ የሚመጡ እንግዶችን ጤናቸውን በብቃት በመንከባከብ የጤና ቱሪዝም መዳረሻ ከማድረጉም ባለፈ ዘመናዊ ህክምና ፍለጋ ወደ ተለያዩ ሀገራት በመሄድ የሚወጣውን የውጪ ምንዛሬ ለማስቀረት እና ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ምክትል ከንቲባዋ ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም የህክምና ባለሙያዎችን በማፍራት ለሌሎች የህክምና መስጫ ተቋማት አጋዥ ጉልበት ሆኖም ያገለግላል ብለዋል ምክትል ከንቲባዋ፡፡

ሮሃ የህክምና መስጫ ማዕከል ብቻም ሳይሆን መንፈስን ደስ የሚያሰኝ ዘመናዊ ፓርክ የተካተተበት ነው ።አዲስ አበባን የጤና ቱሪዝም ማዕከል የመሆን ህልሟን ታሳካ ዘንድ እንደ ሮሃ ያሉ ተጨማሪ ማዕከላት እንዲኖራትም ተግተን መስራታችንን እንቀጥላለን ብለዋል ፡፡ የሮሃ ህክምና ካምፓስም ለፕሮጀክቱ ግንባታ ምክንያት ለሚነሱ ነዋሪዎች መልሶ ማቋቋሚያ እና ማደራጃ ይውል ዘንድ አስፈላጊውን ድጋፍ ስላደረገ ምስጋና እንደሚገባው ምክትል ከንቲዋ አመልክተዋል ፡፡

የሮሃ የህክምና መንደር አምስት ዘመናዊ እና አለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆስፒታሎች እና ከ1,100 አልጋዎች በላይ ያካተተ ነው።በተጨማሪም የህክምና ማዕከሉ የተለያዩ በቴክኖሎጂ የላቁ ልዩ የህክምና መስጫዎችን ፣ የህክምና ትምህርት ቤት ፣ የህክምና ምርምር ማዕከል እና ሌሎችንም የተለያዩ የአገልግሎት የሚሰጡ ህንፃዎች የተካተቱበት እንደሆነ ተገልፆል፡፡

ሆስፒታሉ ፣ የልብ ፣ የጭንቅላት እና የጀርባ አጥንት ህክምና ፣ በአይነታቸው ለየት ያሉ የውስብስብ ተዛማጅ ህክምናዎች እና ልዩ የንቅለተከላ ቀዶ ጥገና ፣ ስኮሊዮሲስ ቀዶ ጥገና ፣ የካንሰር ህክምና (ኦንኮሎጂ) ፣ ኒውሮ ሰርጀሪ ፣ አይ. ቪ. ኤፍ. (IVF) ፣ የልብ ቀዶ ጥገና የመሳሰሉትን በኢትዮጵያ የማይገኙ ግልጋሎቶች ጨምሮ ይሰጣል መባሉን የዘገበው የአዲስ አበባ ከተማ ካውንስል ነው።


Exit mobile version