Site icon ETHIO12.COM

መልስ የሚሻ ዜግነታዊ ጥያቄ – ሻለቃ ፈይሳ ናኔቻ

በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ነጭና ጥቁር እኩል መሆኑን በተግባር በሐሳብ ሞግቶ ፣ በአውደ ውጊያ ተዋግቶ ያረጋገጠ ለነፃነትና ክብሩ ማንኛውንም መስዋዕትነት ለመክፈል ቅንጣት ታህል ወደኃላ የማይል የዓለም ጭቁኖች መብት ተሟጋችነቱን በጥቂቱ ማንሳት ወደ ጥያቄው ይበልጥ ያንደረድረናል።

ጥያቄው ትንሽና ትልቅ ምሁርና መሐይም የሚል ሳይሆን የወል ጥያቄ ነው። ሀገሩን የሚያፈቅር ፣ በነፃነቱ የማይደራደር ፣ ላቡን ጠብ አድርጎ ሠርቶ የሚያድር ፣ ለእምነቱ በእምነቱ የሚኖር የዚች ጠይም ወይዘሮ ዜጋ የሆነን ሁሉ ይመለከታል።አዎን ጥያቄውም ነጠላ አይደለም።

አቅምና ጊዜው የፈቀደውን ብቻ እናንሳ። ተቆጥረው የማያልቁ ፀጋዎችን ይዘን ስለምን ደሃዎች ሆንን? እንዴት ተፈጥሮ ያለስስት የለገሰቻት ምድር ዜጎች ይራባሉ? ስለምን ዓለምን መመገብ ሲገባቸው እርዳታ ይቀበላሉ? የስልጣኔ መሠረት ሆነው ሳለ የዓለም ጭራ ይሆናሉ? ወዘተ ወዘተ ወዘተለዘመናት የቁጭታችን መንስኤ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ተጀምሮ ወደ ፍፃሜ እየተቃረበ ነው።

የወንጪ ፣ ኮይሻና ጎርጎራ ሐይቆች ፓርክ ግንባታዎች እውንነት በእንጦጦ ፓርክ ስኬት ግንባታ ተረጋግጧል። ያውም በራስ ሐሳብና የፋይናንስ አቅም! ኢትዮጵያ ሐብቷ ላይ ያንቀላፋችበትን ዘመን በልጆቿ ጥረት ለማካካስ ቆርጣ በተነሳችበት ወቅት ሁሉም በአቅምና ችሎታ መረባረብ ሲገባው የሚገርሙ ብቻ ሳይሆኑ የሚያሳምሙ ክስተቶች ይታያሉ።ለእኛ ለኢትዮጵያውያን የማይመጥነውን የጉስቁልና ዘመን ለማለፍ ቋንቋችንን የባቢሎን ዘመን ለማድረግ የሚራጨውን መርዝ ምንጭ ማዋቅ አውቀንም ለወል ጥቅማችንንና ፍላጎታችን መሳካት በህብረት ማድረቅ ብቻ ያሻግረናል።

በትውልድ ተገቢው ሥፍራችን ላይ ያኖረናል።በዚህ ፀሐፊ እምነት ችግሮቻችን ውስጣዊም ውጫዊም ናቸው። ውስጣዊው ግን ይብሳል። የታሪክ ምሁራን ለኢትዮጵያ ታሪክ የተለያዩ አሃዛዊ ቁጥር ያስቀምጣሉ። ትክክለኛውን ለእነሱ ትተን የሺህ ዓመታት በሚለው ለጊዜው እንቀጥል።

ውስጣዊ ችግራችን የሚብሰው ታሪካችንን በመካድ ነው። ዓለም የሚያውቀውን የወል የኩራት ታሪካችንን ክደን ፣ በአንጡራ ሃብቷና በብድር የተገኘውን ሃብት ተጠቅመን ትውልዱን የሚከፋፍል ፣ ጥላቻን በየደጁ የሚያድል ትርክት ፈጥረን ከነበረን ማንነታችን በአስተሳሰብ አጥረን ፣ እንድንገኝ መደረግ ፣ ከብርሃን የወል ዘመናችን ይልቅ የወል የጨለማ ጊዜን እንድንናፍቅ የተጀመረውን የከፍታ ውጥን እንዳናደንቅና ለስኬቱ በጋራ እንዳንታጠቅ አድርጎናል።አሊያም ጉዞአችን ወደዚያ ይመስላል።

ይሄ አካሄዳችን አዎንታዊ ለውጣችንን ለማይፈልጉ ታሪካዊ ጠላቶቻችን ምቹ ሁኔታ የፈጠረ ይመስላል። (ይመስላልና ሆኗል የተለያዩ መሆናቸውን ልብ ይሏል ) ፡፡ ባንዳ መቼም የማይጠፋ ተውሳኳ ነው። ትናንት ነበሩ ፤ ዛሬም አሉ ፤ ነገም ይኖራሉና ! እነሱ የሚሰጡንን ወንዝ የማያሻግር አጀንዳ ተቀብለው ከእነሱ በላይ ሊያባሉን የሚለፉትን ማየቱ ሀገራችን ከተውሳክ ፀድታ ላለመፈጣሯ በቂ ማሳያ ይመስለናል።

ከፊታችን የዚህን ትውልድ ታሪክ ሠሪነት የሚያረጋግጡ ፤ ከኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ችግሮች የሚያወጡ ፣ ጅማሮዎች አሉ። ትውልዱ ይሄንን ዕድል መጠቀም ሐሳቦቹንንና ጅምሮቹን መደገፍ ፤ አሊያም ጠላቶቻችን ባዘጋጁልን ቦይ እየፈሰሰ ለሀገሩ ውድቀት ፣ ለጠላት ፍላጎት ስኬት እንቅፋት ለመሆን መሰለፍ የሚሉት አማራጮች ቀርቦለታል።

የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት 


Exit mobile version