Site icon ETHIO12.COM

በርካታ የበይነ መረብ ሚዲያዎች ጥሪውን አላከበሩም ፤”ህግ በማያከብሩ ሚዲያዎች እርምጃ ይወሰዳል”

በአዲሱ የመገናኛ ብዙኃን አዋጅ መሠረት ሕጋዊ ሆነው እንዲመዘገቡና ፈቃድ እንዲያወጡ  የተወሰነባቸው የበይነመረብ ሚዲያዎች የሕጋዊነት ምዝገባ፣ እስከ ግንቦት 15 ቀን 2013 ዓ.ም. እንዲያካሂዱ ጥሪ ቢቀርብም ጥሪውን አክብረው የተመዘገቡት ጥቂት መሆናቸው ተጠቆመ። ቀነ ገደቡ ካለፈ ያልተመዘገቡት የበይነ መረብ ሚዲያዎች በሙሉ ሕገወጥ እንደሚሆኑ ይፋ ሆነ።

የመገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን  ሕጉን ዋና ዳይሬክተር አቶ መሐመድ እድሪስን ጠቅሶ ሪፖርተር እንዳስታወቀው ባለስልጣኑ ህግን አክብረው በማይሰሩ ሚዲያዎች ላይ እርምጃ እንደሚወስድ አስጠንቅቋል። ” ይታወቅልን” ሲሉ ዋና ዳይሬክተሩ እንዳሉት እስካሁን የነበረው መለሳለስ አይቀጥልም። ህግን በማያከብሩት ላይ ህጋዊና አግባብነት ያለው እርምጃ ይወሰዳል።

ሕግ ለማስከበር ባለሥልጣኑ ከመቼውም በላይ ቆፍጣና ሆኖ እንደሚሰራ አቶ መሀመድ የገለጹት ለፓርላማ ቋሚ ኮሚቴ ሪፖርት ባቀረቡበት እንደሆነ የሪፖርተር ዜና ያስረዳል። ከዚህ በፊት የነበረው እንቅስቃሴ መለሳለስ የበዛበት፣ ጥሰቶችና ግድፈቶች ሲያጋጥሙ ባለሥልጣኑ የሚሰጣቸውን የዕርምት ማስጠንቀቂያዎች  ወይም ግብረ መልስ እንደ ግብዓት ከመውሰድ ይልቅ፣ ውድቅ በማድረግባለሥልጣኑ መሳለቂያ የመሆን ደረጃ የደረሰቡት ሁኔታ እንደነበረ በመግለጽ፣ የሚዲያ ተቋማት ይህን ያህል ሲወርዱ ዝም ብሎ ማየት የባለሥልጣኑ ችግር እንደነበር ጠቁመዋል።

የሚዲያዎችን፣ በተለይም በዩቲዩብ የሚሰራጩት ላይ መንግስት እጅግ የተለሳለሰ አቋም የያዘበት ምክንያት አብዛኞችን እይነጋገረ የቆየ ጉዳይ መሆኑ ይታወሳል። አንዳንዶቹ ” አገራቸው የት ነው” በሚባል ደረጃ ህዝብን ከህዝብ፣ ክልልን ከክልል፣ ቤተሰብን ከቤተሰ ለማጋጨት ሆን ብለው የሚሰሩ፣ ለሚያቀርቡት ዝግጅት ጥንቃቄ የማይወስዱ፣ እጅግ በወረደ ደረጃ ሙያዊ ሽታ የሌላቸው፣ ለልዩ ዓላማና ለማተራመስ የተፈጠሩ የሚመስሉ …” በሚል ጠንካራ ትችት የሚሰነዘርባቸው እንደሆነ በተደጋጋሚ አስተያየት ሲሰጥ ስለነበር የባልስልጣኑንን ሪፖርት የሰማው ቋሚ ኮሚቴ ይህን አንስቶ ስለመሞገቱ በሪፖርተር ዜና አልተካክተተም። ይሁን እንጂ ይህንን ሃሳብ የሚያጸና ሃሳብ ግን ሃላፊውን ጠቅሶ አካቷል።

የተሳሳተ መረጃን ማቆም የሚቻለው የመንግሥት አካላት ስለፈጸሙትና እየፈጸሙት ስላለው ሥራ፣ ሚዲያ ሲጠይቃቸው መልስ መስጠት ሲችሉ እንደሆነም አቶ መሐመድ አመልክተው “ይሁን እንጂ ሚዲያው  በዘገባው በአገራዊ ጉዳዮች የማይደራደር መሆን አለበት። ሰላም ብሔራዊ ጥቅማችን ነው” ሲሉ ሁሉም በአገሩ ጉዳይ ሃላፊነት ሊወስድ እንደሚገባ መናገራቸው በዜናው ተመልክቷል። በተመሳሳይ የመንግሥት ተቋማትና አመራሮቻቸው በሮቻቸውን ለሚዲያ ተቋማት ክፍት በማድረግ ለሕዝብ መድረስ ያለበት መረጃ እንዲደርስ፣ ጋዜጠኞች ሊታገዙ እንደሚገባ አቶ መሐመድ ጥሪ አቅርበዋል። ሃላፊዎች በሮቻቸውን በመክፈት የሚፈልጉትን ብቻ ሳይሆን የማይፈልጉትንም የመጠየቅና የመመለስ ልምድ ሊያካብቱ እንደሚገባ በማሳሰቢያ መልክ መክረዋል።

ፎቶ – ሪፖርተር



Exit mobile version