Site icon ETHIO12.COM

ካመጡ አይቀር እንዲህ ጠማቂውን ነው፤ የሚያንቅርርማ እዚህስ መች ጠፋ! (በድሉ ዋቅጅራ).

ጠ/ሚ ሀይለማርያም ደሳለኝ ኢ/ር ስለሺ በቀለን፣ ጠ/ሚ አብይ አህመድ ብርቱካን ሚደቅሳን አመጡ፡፡
.
ኢ/ር ስለሺ ኒውዮርክ፣ ለተባበሩት መንግስታት ይሰሩ ነበር፤ ትልቅ ደሞዝ ነበራቸው፤ ልጆቻቸው ጥሩ ትምህርት ይማሩ ነበር፡፡ ደምወዛቸውም ሆነ ኑሯቸው ኢትዮጵያ አይታሰብም፡፡
ብርቱካን ሚደቅሳ ሀርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ዲግሪዋን ሰርታ እዚያው አሜሪካ እየኖረች ነበር፡፡ ኢትዮጵያ እያለች በወጣትንቷ ብዙ መከራ ተቀብላለች፤ ብዙዎች በገንዘብና በፖለቲካ ጥቅም ለሚቸረችሩት ፍትህ አንገቷን ሰጥታለች፤ ስለዲሞክራሲ መከበር ፖለቲከኛ ሆና ምርጫ በማሸነፏ በተደጋጋሚ ታስራለች፤ አሸባሪ ተብላ እድሜ ልክ እስራ ተፈርዶባታል(?)፡፡ በወጣትነቷ በተጋተችው የሚያንገሸግሽ መከራ የተነሳ ከህልሟ ተፋትታ በስደት ትኖር ነበር፡፡
.
ሁለቱ ጠ/ሚንስትሮች ሁለቱን ወደሀገራቸው ጋበዝዋቸው፡፡ ለኢ/ሩ የድሎት ኑሮ፣ ለብርቱካን የደረሰባት መከራ አላስቀራቸውም፡፡ ይልቁንም ለሀገራቸው ያላቸው ቀናኢነት፣ ለወገናቸው ያላቸው ፍቅር ጥሪውን እንዲቀበሉ አደረጋቸው፡፡
.
ቁምነገሩ ጥሪውን ተቀብለው መምጣታቸው አይደለም፤ ያመጣቸው የሀገርና የወገን ፍቅር ላይ ለእውነት ያላቸው ታማኝነትና ክብር ተደምሮ በአጭር ጊዜ የሰሩት ተግባር እንጂ፡፡ ኢትዮጵያ ከውስጥ የከሀዲ ጁንታዎች፣ ከውጭ የእጅ አዙር ቅኝ ገዢዎች ጥቃት በጠነከረባት በዚህ ወቅት፣ ኢ/ር ስለሺ የኢትዮጵያ የልማት ጉዞ ከተጀመረበት ከታላቁ ህዳሴ ግድብ ጋር፣ ወ/ት ብርቱካን ደግሞ የዲሞክራሲያዊነትና ፍትሀዊነት ፍንጭ ከታየበት፣ በተወዳዳሪ ፓርቲዎች ተቀባይነት ካገኘ፣ ከሁልም በላይ ሰላማዊ ሆኖ ከተጠናቀቀው 6ኛው ምርጫ ጋር ግብራቸው በታሪክ ሲወሳ ይኖራል፡፡
.
ወደ ሀገራችሁ ግቡና ለወገናችሁ ስሩ ሲባሉ፣ ‹‹ስንት ይከፈለናል? ምን አይነት ቤት ይሰጠናል; . . ወዘተ. እያሉ የሚደራደሩ አሉ፡፡ በውጭ የበጎ አድርጎት ድርጅቶች ጥያቄያቸው ተሟልቶ መጥተው በአመታት ጠብ የሚል ስራ ያልሰሩ በርካቶች ናቸው፡፡ እነዚህን ሰዎች ሳስብ ነው፣ . ‹‹ካመጡ አይቀር ጠማቂውን ነው፤ ወገኑን በደስታ የሚያሰክረውን! የሚያንቃርርማ እዚህስ ማች ጠፋ!›› የምለው፡፡

Exit mobile version