ETHIO12.COM

ዜጎች በሳይበር ዘመቻቸው “ነጩ ወያኔ” ሲሉ ብሊንከንን አወገዙ፤ ዓለም ወደ ቀልቡ እንዲመለስ የ”ፍትህ” ያለህ አሉ

ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ ዓለም ኢትዮጵያ ላይ የያዘውን ያልተገባና ሚዛናዊነት የጎደለው አቋሙን እንዲስተካከል፣ የውጭ አገር መንግስታት እያደረጉ ያሉትን ቅጥ ያጣ ጫናና ጣልቃ ገብነቶችን፣ በተጨማሪም ህፃናትን ለውትድርና እየተጠቀመ ባለው የህወሓት ቡድን ላይ ጫና እንዲደረግ የሚጠይቅ የትዊተር ዘመቻ አካሂደዋል። በተለይም አንቶኒ ብሊንከን ” ነጭ ወያኔ” በሚል ክፉኛ ተንኳሰዋል። ሊንዳ ቶማስም በተመሳሳይ ተወግዘዋል።

በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የትዊተር ዘመቻው በተለይም አሸባሪው ሕወሓት እያደረገ ያለውን ትንኮሳ እና ህጻናትን ለውትድርና መጠቀሙ የህጻናት መብቶችን እና ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችን የሚጣረስ በመሆኑ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲያወግዘው የሚጠይቅ ነው። ይህን ከፍተኛ ወንጀል እንደ መልካም አድረገው የዓለም አቀፍ ሚዲያዎች የህጻናቱን ምስል አስደግፈው መዘገባቸው የሚታወስ ነው።

ይህ አሸባሪ ቡድን ” አልደገፋችሁኝም” በሚል በርካታ ንጹሃንን ማረዱ፣ መረሸኑና አስሮ እያሰቃየ እንደሚገኝ ከበቂ በላይ መረጃ ቢኖርም እኚሁ የተንሸዋረረ አቋም የያዙት አገራትና ዓለም ዓቀፍ ተቋማት ዝምታን መምረጣቸው እጅግ አነጋጋሪ ሆኗል። በዚህ ዘመቻ ይህ ጉዳይ እጅግ ጎልቶ የወጣ ሆኗል። ትህንግ እየፈጸመ ያለውን የሰብአዊ መብት ጥሰትና ትንኮሳ በአስቸኳይ ያቆም ዘንድ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ጫና እንዲያሳድርም በዘመቻው ተጠይቋል። ዓለም አቀፍ ሚዲያዎችም በትግራይ ስላለው ግጭት እያቀረቡት ያለው መረጃ በእውነታ ላይ ያልተመሰረተ መሆኑንም የዘመቻው ተሳታፊዎች አንስተዋል፡፡

” ወዳጅ” እያለች የምትጠራው አሜሪካም በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ የያዘችው አቋምና በውስጥ ጉዳይ ላይ እያደረገች ያለው ጣልቃ ገብነት አግባብነት የሌለውና አሸባሪውን ቡድን የሚደግፍ ነው በሚል የዘመቻው ተሳታፊዎች ተቃውሟቸውን ገልጸዋል፡፡ አሜሪካ በዓለም ላይ አሸባሪ ከሚባሉ አካላት ጋር ግንኙነት እንደማታደርግ ሁሉ ከትህነግ አሸባሪ ቡድን ጋር በቀጥታም ሆን በተዘዋዋሪ ገጥማ ኢትዮጵያ ላይ እያደረገች ያለው ዘመቻ በእጅጉ ተወግዟል።

በተለይም አይሁዳዊው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አንቶኒ ብሊንከን በኢትዮጵያ ላይ የያዙት አቋም የለየለት ሚዛን የሳተ፣ አንዳንዶች እንደሚሉት የአሸባሪው ቡድን አባል እስከመምሰል የደረሰ፣ ስራቸውን ሁሉ ትተው በወያኔ ጉዳይ የተጠመዱ ሆነው መታየታቸውን በቃላት ብቻ ሳይሆን በምስልም አስደግፈው የዘመቻው ተሳታፊዎች አኮስ ሰዋቸዋል። ምዕራባውያን አሸባሪው ህወሓት ከፊት ለጦርነት ያሰለፋቸው ህፃናት ጉዳይ ግድ ሳይሰጣቸው ባለየ ማለፋቸው ተገቢነት እንደሌለውም በስፋት መጠቀሱን ተከትሎ አንዳን አፍሪካ ተኮር ሚዲያዎች ድርጊቱን በማውገዝ ኮንነው ጽፈዋል።

ትግራይንና የትግራይን ሕዝብ ሲጠብቅ በኖረው በመከላያ ሰራዊትና በማይካድራ ንጹሃን ላይ ትህነግ የፈፀመውን ዘግናኝ ጭፍጨፋን በማስታወስ ምዕራባውያን ለዚህ የከፋና በዓለም ዓቀፍ ተቋማት ሳይቀር ገሃድ ለሆነ ወንጀል ጆሮ ዳባ ማለታቸው የዘመቻው ሌላው አበይት የመቃወሚያና አሜሪካንን ጨምሮ ዓለም በጥቅሉ ሚዛኗን እንደሳተች ለማሳየት የቀረበ ጉዳይ ነበር።

አሜሪካን ጨምሮ ምዕራባውያን ሃገራት የኢትዮጵያን ጉዳይ በፍትሃዊነት እንዲመረመሩ፣ ሉዓላዊነቷን እንዲያከብሩና ከመቶ አስራ አምስት ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ያላትን አገር ለማፍረስ የሚያደርጉት መረባረብ እንዲያቆሙ በዘመቻው ተጠይቋል።


Exit mobile version