Site icon ETHIO12.COM

ህወሃት ለምን ጦርነቱን መቀጠል ወሰነ? ዉሳኔውስ ለህወሃት አክሳሪ ወይስ አትራፊ?

የህወሃት አመራሮች 8 ወር ሙሉ ዋሻ ለዋሻ ሲሳደዱ እንደመቆየታቸው፣ ከመጠን ያለፈ የፍርሃት እና የመሳደድ የአዕምሮ በሽታ የመጋለጥ እድላቸው ሰፊ ነው። በዚህም ምክንያት የከበባቸውን ስጋት ለማራቅ የተጣደፈ፣ ትርፍ እና ኪሳራው ያልተሰላ ጦርነት የመቀጠል ዉሳኔ ሊወስኑ ይቻልሉ።

[ በ ማስተዋል ደሣለው ]

ህወሃት የፌደራል መንግስቱ ያወጀዉን የተኩስ አቁም ጥሶ፣ በአማራ እና አፋር ክልሎች በኩል የከፈተው ጦርነት፣ ከ8 ወር በፊት ይሄን ጦርነት ከመጀመሩ የማይተናነስ ትልቅ ስትራቴጅክ ስህተት ነው።
ለምን?

  1. ህወሃት አሁን ያለዉን ጦርነት ለመቀጠል የሚያስችል ኢኮኖሚያዊ፣ አስተዳደራዊ እና ፖለቲካዊ አቅሙ ተዳክሟል። ጦርነት ከሚያስከትለው ሰፊ ኢኮኖሚያዊ ዉድመት ባልተናነሰ፣ ለወታደር ቀለብ፣ ልብስ፣ ጫማ፣ ነዳጅ፣ የጦር መሳሪያ እና ለሌሎች የጦርነት ግብዐቶች ሰፊ ሃብት ይጠይቃል። ጦርነቱ ለሳምንታት እና ለወራት እየተራዘመ በሄደ ቁጥር ህወሃት ላሰማራው በመቶ ሽወች የሚቆጠር ሰራዊት ቀለብ እና ማጓጓዣ ማቅረብ እየተሳነው ይመጣል። ይሄም የሰራዊቱን ስምሪት ፍጥነት፣ የማጥቃት እና መከላከል ብቃቱን፣ ለዉጊያ ተነሳሽነቱን ያሽመደምደዋል።
  2. ህወሃት በ 4ቱም አቅጣጫ ስለተከበበ የሚፈልጋቸውን ነገሮች ከውጭ ለማስገባት የሚችልበት በር የለዉም። ስለዚህ ጦርነቱ በተራዘመ ቁጥር ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ እና ወታደራዊ ጫና ህወሃት ላይ ይፈጥራል።
  3. የህወሃት ሰራዊት ከአፋር እስከ ጠለምት በሺወች ኪሎሜትር ተራርቆ ለማጥቃት ተበትኗል፣ በኤርትራ ድንበር በኩልም ሰራዊት ማሰማራት ግዴታው ነው። የህወሃት ሰራዊት በተራራቁ ቦታወች ለማጥቃት መሰማራት፣ ለመልሶ ማጥቃት እና ለመቆረጥ ያጋልጠዋል፣ ጊዜ እየገፋ በሄደ ቁጥር የሚገጥመው የነዳጅ እና የሎጅስቲክ እጥረት ችግሩን የከፋ ያደርግበታል።
  4. የህወሃት ሰራዊት ከትግራይ አልፎ ወደ አማራ እና አፋር ክልል ሲገባ ትግራይ እንዳለው የሚደብቀው እና የሚደግፈው ህዝብ አያገኝም፣ እንዲያውም ህዝብ 27 ዓመት ህወሃት የፈፀመበትን ግፍ ስለሚያውቅ አምርሮ ይወጋዋል። ዛሬ እንደ 83 የሚተባበረው እና መንገድ የሚመራው ያሬድ ጥበቡ እና ታምራት ላይኔ ስለማያገኝ፣ በማያውቀው አካባቢ ያለ መንገድ መሪ እና መረጃ ነጋሪ እንዲዋጋ ይገደዳል። በተጨማሪም ሰራዊቱ ሰሞኑን በገባባቸው የአማራ እና አፋር አዋሳኝ አካባቢወች ሰላማዊ ሰወች ላይ እየፈፀመው ያለው ግድያ፣ የድሃ ገበሬ ጎተራ ገልብጦ እህል እና ዱቄት መዝረፍ፣ የነዋሪውን ሃብት መዝረፍ እና ማውደም ህዝቡ የበለጠ እንዲጠላው ያደርጋል።
  5. የህወሃት ጦርነቱን መቀጠል ትግራይ ውስጥ ከፍተኛ ሰብዓዊ ቀውስ ይፈጥራል። በጦርነቱ ምክንያት የእርዳታ ዕህል፣ ነዳጅ፣ ሸቀጦች እና ሌሎች አስፈላጊ ነገሮች ወደ ትግራይ ሳይገባ ለረጅም ጊዜ በቀጠለ ቁጥር፣ ከፍተኛ ሰብዓዊ ቀውስ ይፈጠራል። ይሄም ህወሃት ጦርነቱን በፈለገው መንገድ እንዳይሄድ አንቆ ይይዘዋል። ቀውሱ እየከፋ ሲሄድ ህዝቡ የህወሃትን መንገድ ትክክለኛነት እንዲጠይቅ ያደርጋል፣ የውስጥ መከፋፈል፣ በጦርነቱ የህዝብ መሰላቸት ያስከትላል።

ታዲያ ህወሃት ለምን ጦርነቱን ማስቀጠል መረጠ?

4 ምክንያቶች ይታዩኛል።

  1. ህወሃት ህልዉናው እንዲቀጥል የወልቃይት ሱዳንን መስመር መቆጣጠር ብቸኛ አማራጩ ስለሆነ

ህወሃት ወልቃይትን መያዝ እና አለመያዝ የህልዉናው መሰረት እንደሆነ ያውቃል። ይሄን የሚያውቀው የኢትዮጵያ መንግስትም፣ ወልቃይት ላይ ያለ የሌለ ሃይሉን አስፍሯል። በተጨማሪም ህወሃት ወደ ሜዳማው ወልቃይት ከመግባቱ በፊት ተራራማውን የጠለምት መልከዓ ምድር መቆጣጠር ግዴታው ነው፣ ካለበለዚያ መሃል ላይ ተቆርጦ ሊመታ ይችላል። ህወሃት ሰሞኑን ጠለምት ላይ ሲዋጋ የሰነበተው ለዚህ ነው። ስለዚህ በሰሜን ጎንደር፣ በሰሜን ወሎ፣ በዋግህምራ እና በአፋር በኩል ጥቃት መክፈት ለህወሃት 4 ጥቅም አለው።

• መንግስት በወልቃይት መስመር ያሰፈረውን ሰራዊት እንዲያንቀሳቅስ በማድረግ ሃይሉን ማሳሳት።

• በጠለምት፣ ስሜን፣ ወገራ ሰንጥቆ በማለፍ ጎንደርን ስጋት ላይ መጣል። እንዲሁም የጎንደር፣ ሁመራን መስመር በመበጠስ፣ ወልቃይት ላይ የሰፈረውን ሰራዊት መቁረጥ። የስሜን ተራሮችን መቆጣጠርም ትልቅ ስትራቴጅካዊ ጥቅም ይኖረዋል።

• በአፋር በኩል የአዲስ አበባ ጅቡቲን መስመር ስጋት ላይ መጣል፣ ከቻለ መዝጋት እና የሃገሪቱን ኢኮኖሚ በማናጋት መሃል አገር ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ቀውስ መፍጠር። በጅቡቲ በኩል ከውጭ ቀጥታ መገናኘት።

• በራያ፣ ወልዲያ፣ ደሴ መስመር የቻሉትን ያህል ወደመሃል አገር በመግፋት መሃል አገሩን ስጋት ላይ መጣል።

• የአማራ እና አፋር ክልሎችን በማወክ የፌደራል እና የክልሎችን የመከላከል አቅም ማዳከም እና ትርምስ መፍጠር።

  1. ህወሃት ከጊዜ ጋር እሩጫ ላይ ስለሆነች

ጊዜ በሄደ ቁጥር ህወሃት ወታደራዊ፣ ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ አቅሙ እንደሚዳከም ያውቃል፣ ከዉስጥም የጦርነቱ ዳፋ ሲበዛ ጥያቄ መነሳት ይጀምራል፣ ህዝብም ያጉረመርማል። ይሄ ከመሆኑ በፊት አዳዲስ አካባቢወችን መያዝ ተጨማሪ የጦርነት ግብዐቶችን (ዕህል፣ ልብስ፣ ነዳጅ ወዘተ) ለማግኘት ይጠቅማል፣ የስነልቦና እና የፕሮፓጋንዳ ጥቅምም አለው። ወደ ድርድር ከተገባም ሰፊ ቦታ መያዝ የተሻለ የመደራደር አቅም ኢንዲኖር ያደርጋል።

  1. የህወሃት አመራሮች 8 ወር በዋሻ በመቆየታቸው የስጋት በሽታ (ፓረ’ኖያ) ስላደረባቸው

የህወሃት አመራሮች 8 ወር ሙሉ ዋሻ ለዋሻ ሲሳደዱ እንደመቆየታቸው፣ ከመጠን ያለፈ የፍርሃት እና የመሳደድ የአዕምሮ በሽታ የመጋለጥ እድላቸው ሰፊ ነው። በዚህም ምክንያት የከበባቸውን ስጋት ለማራቅ የተጣደፈ፣ ትርፍ እና ኪሳራው ያልተሰላ ጦርነት የመቀጠል ዉሳኔ ሊወስኑ ይቻልሉ።

  1. የበሰበሰ ዝናብ አይፈራም

የህወሃት ባለስልጣናት ባለፉት 8 ወራት ሁሉን ነገራቸውን አጥተዋል፤ ስልጣናቸዉ እና ሃብታቸው ዛሬ የለም። ስለዚህ አመራሮቹ ጦርነቱን ብንቀጥል ልናገኘው የምንችለው እንጅ ምንም የምናጣው ነገር የለም ብለው እንዲያስቡ ያደርጋል። መሃል ላይ ወጣቶች እና ህፃናት ህይወታቸውን፣ አካላቸውን እና ወጣትነታቸውን አያጡም እያልኩ አይደልም። ⁾⁾

Begemder chanell

Exit mobile version