Site icon ETHIO12.COM

ሰነዶችን በኦንላይን ለማረጋገጥ የሚያስችለውን የመግባቢያ ሰነድ ከባንኮች ጋር ተፈረመ

ኤጀንሲው በሰነዶች የሚፈጸሙ የማጭበርበር ወንጀሎችን ለመከላከል ሰነዶችን በኦንላይን ለማረጋገጥ የሚያስችለውን የመግባቢያ ሰነድ ከባንኮች ጋር ተፈራረመ፡፡

የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ኤጀንሲ በሰነዶች የሚፈጸሙ የማጭበርበር ወንጀሎችን ለመከላከል ሰነዶችን በኦንላይን ለማረጋገጥ የሚያስችለውን የመግባቢያ ሰነድ በአዲስ አበባ ከተማ ከባንኮች ጋር ተፈራረመ፡፡

በፊርማ ስነ-ስርዓት መድረኩ ላይ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ሙሉቀን አማረ እንደተናገሩት በሀገራችን ዲሞክራሲያዊ ስርዓትን ለመገንባት እና ልማትና እድገትን በማፋጠን ብልፅግናን ለማረጋገጥ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችን በይበልጥ አጠናክሮ አስተማማኝ መሰረት እንዲይዙ የህግ የበላይነትን በማረጋገጥ ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠር ቁልፍ ጉዳይ መሆኑን ገልፀው፤ የፌዴራል የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ኤጀንሲም በህግ የተሰጠውን ተልዕኮና ኃላፊነት ተግባራዊ በማድረግ ሕዝብና መንግስት የሚጠብቁትን ውጤት ለማሳካት ከመቸውም ጊዜ በበለጠ ጥረት በማድረግ ላይ ነው ብለዋል፡፡

በዚህም መሰረት ተቋሙ ሁሌም በለውጥ ሂደት ላይ የሚገኝ ሲሆን በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአገልግሎት አሰጣጡ ላይ እያጋጠሙ የሚገኙ በሀሰተኛ ሰነድ የመገልገል ተግዳሮቶችን እና ይህንኑ ተከትሎ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን በመረዳትና የተቋሙን ተጨባጭ ሁኔታ መሰረት ያደረገ ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት ለመስጠት፤ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሶፍትዌር ሲስተም በማበልጸግ ስር-ነቀል ተቋማዊ የአሰራር ለውጥ ሊያመጣ የሚችል አቅጣጫ በመከተል ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል፤ በመሆኑም የዛሬው የስምምነት ሰነድ መሰረቱን የሚያደርገው በባንኮች በኩል ሀሰተኛ የውክልና ሰነዶችን በመያዝ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን ለመከላከልና የአሰራር ስርዓቱንም ለማዘመን ሲባል በኤጀንሲውና በሁሉም የመንግስትም ሆነ የግል ባንኮች በኩል የመረጃ ኔትወርክ ትስስር የተፈጠረ በመሆኑ ይህንን ትስስር በመጠቀም ባንኮች በደንበኛቸው ተወካይ በኩል የሚቀርብላቸውን የውክልና ሰነዶች እንደ ከዚህ ቀደሙ ወደ ኤጀንሲው መላክ ሳያስፈልጋቸው በዚህ የመረጃ ትስስር ያለምንም ተጨማሪ ወጭ በደቂቃዎች ውስጥ ከኤጀንሲው የመረጃ ቋት በኦንላይን የሚያረጋግጡበት ስርዓት መፍጠር በመቻሉ አሰራሩን ተግባራዊ ለማድረግ ሲባል የዛሬው የመግባቢያ ስምምነት የፊርማ ስነ-ስርዓት ተዘጋጅቷል ብለዋል፡፡

በመድረኩ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ ንግግር ያደረጉ ሲሆን ይህ አይነቱ አሰራር በሰነዶች የሚፈጸሙ የማጭበርበር ወንጀሎችን ለመቀነስ ዋነኛ ሚና እንዳለው ገልጸው በባንኮች በኩልም የደንበኞቻችሁን ገንዘብ ከመዘረፍ የሚያድን አሰራር ነው ብለዋል፡፡ አያይዘውም ኤጀንሲውም ይህን በጎ ጅማሮ አጠናክሮ እንዲቀጥል እና እንዲያጎለብት ጠቁመው በጠቅላይ ዐቃቤ ህግም በተግባራዊነቱ በኩል እገዛ የሚያስፈልግ ከሆነ ለማገዝ ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡

የስምምነት ፊርማውን አቢሲኒያ ፣ዘመን፣ ህብረት፣ብርሀን፣አዲስ ኢንተርናሽናል፣ ወጋገን፣ዓባይ፣ደቡብ ግሎባል፣ንብኢንተርናሽናል ፣አንበሳ ኢንተርናሽናል አዋሽና ኦሮሚያ ኢንተርናሽናል ባንኮች በፕሬዝደንቶቻቸውና በተወካዮቻቸው አማካኝነት ከኤጀንሲው ጋር ተፈራርመዋል፤ ከሁለት ወር በፊትም ኤጀንሲው ከኢትዮያ ንግድ ባንክ ጋር ስምምነቱን ተፈራርሞ ተግባራዊ ያደረገ ሲሆን 1700 በሚሆኑ በየትኛውም አካባቢ በሚገኙ ቅርንጫፎች አማካኝነትም አገልግሎቱ እየተሰጠ ይገኛል፤ በተመሳሳይም ከሁለት ሳምንት በፊትም ኤጀንሲው ስምምነቱን ከቡና ኢንተርናሽናል ባንክ ጋር የተፈራረመ ሲሆን አገልግሎቱ በሁሉም ቅርንጫፎች በኩል በስፋት እየተሰጠ መሆኑ ተገልጷል፡፡

የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ኤጀንሲ ለኢፌዴሪ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ተጠሪ ከሆኑ ተቋማት ዉስጥ አንዱ መሆኑ ይታወሳል፡፡

Exit mobile version