ETHIO12.COM

መረራ ለማ መገርሳን ወቀሱ፤ “በይፋ ኦህዴድ ፈርሷል በል ሲባል እምቢ አለ”

ለድርጅት ስራ ወደ አሜሪካ ያቀኑት ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና የቀድሞውን የኦሮሚያ ርዕሰ መስተዳድር ወቀሱ። መረራ ወቀሳውን የሰነዘሩት በመድረክ ሳይሆን ከመድረክ ውጪ በተደረገ መደበኛ ያልሆነ ውይይት ላይ ነው። ” ለማ ኦህዴድ መፍረሱን በገሃድ እንዲያውጅ ተጠይቆ እምቢ አለ። ለሁሉም ጥፋት ሃላፊነቱ የሱ ነው” ብለዋል።

መረራ በርካታ ጉዳዮችን አንስተው በነጻነት በተናገሩበት በዚህ የጠረጴዛ ንግግር የነበረ ለኢትዮ 12 የአሜሪካ ተባባሪ እንዳስረዳው አቶ ለማ ብጁላይ ጥያቄውን ተቀብለው ኦህዴድ መፍረሱን በሚድያ ቢያውጁ ዛሬ ኦሮሚያ ላይ ሌላ ፖለቲካና አመራር ይኖር እንደነበር መረራ ተናግረዋል። ” ለማ አይሆንም አለ። ከአብይ ጋር ምን ቃል ቢገባቡ እንደሆነ እስካሁን ሊገባኝ አልቻለም” ሲሉ በመገረም ሁኔታውን ትውስታቸውን ገልጸዋል።

ነገሩ እንዲህ ነው። “የኦሮሞ ፖለቲካ ፓርቲዎችን በቅንጅት ለመስራት የሚያስችል የኦሮሞ አመራሮችን በአንድ ጥላ ሥር የሚያሰባስብ (ጋዲሳ ሆገንሳ ኦሮሞ) እንዲመሰረት ተስማምተዋል” የሚለው ዜና ሲሰማ የተባለው ሁሉ በኦሮሞ ህብረተሰብ ዘንድ ደስታን የፈጠረ ነበር። ውስጡ የገባቸውም ያልገባቸውም በሚዲያ ሰፊ ሽፋን የተሰጠውና በተደጋጋሚ ጥያቄው የህዝብና የሽማግሌዎች እንደሆነ የተሰበከለት ስምምነት አካል የሆነው ዋና ስብሰባ በስካይ ላይት ሆቴል ሲደረግ የፓርቲው ሊቀመንበር ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አያውቁም ነበር።

ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ተሸሽጎ ውስጥ ውስጡን ሲሰራ የነበረው ስራ በመጨረሻ የፓርቲዎቹን ውህደት ይፋ ለማድረግና ወደ አንድ ሽግግር ለመምጣት ስካይ ላይት ሆቴል አቶ ዶክተር አብይ ሲቀሩ ሁሉም ተገኝተዋል። ስብሰባው በፊርማ ስነስርዓት ሊቆጭ ደቂቃዎች በቀሩበት ቅጽበት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በድንገት ሆቴሉ ውስጥ ይገባሉ።

ይህን ጊዜ ” ማን ሹክ አላቸው” በሚል መደናገጥ ይፈጠራል። ስብሰባውን የሚመሩት የመድረክ አስተዋዋቂን ጨምሮ በታዛቢነትና በንግድነት የተገኙ፣ አባገዳዎችና እንግዶች ከጀርባ ያለውን ሚስጢር አያውቁም። ጠቅላይ ሚኒስርቱ ልክ የፊርማው ስነ ስረዓት ሊደረግ ደቂቃዎች ሲቀሩ በመግባታቸው መመካከር ባለመቻሉ የፕሮግራሙ መሪ ” እንኳን ደህና መጡ” በሚል አቀባበል እንዲደረግላቸው ከጠየቀ በሁዋላ ወደ ፊርማ ስነ ስርዓቱ አመራ። የፊርማ ደንቡ የየድርጅቶቹ መሪዎች ለፊርማ ሲቀመጡ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይም ለኦህዴድ በተያዘው ቦታ ጉብ አሉ። ፈረሙ። አጭር ንግግር ካደረጉ በሁዋላ የተፈረመውን ውል ሰብስበው ይዘው ወደ ቢሯቸው ሄዱ። ከዛ በሁዋላ ምን እንደሆነ አልታወቀም።

ይህ ከሆነ በሁዋላ እነ ጃዋር፣ እነ አቶ በቀለ፣ እነ አቶ ዳውድ፣ ወዘተ ተደጋጋሚ አስቸኳይ ስብሰባ በማድረግ አቶ ለማ ኦህዴድ መፍረሱን በይፋ እንዲያውጁና አዲሱ ፓርቲ ስራ እንደጀመረ እንዲያስታውቁ በተደጋጋሚ ቢጠየቁም ” የለም አይሆንም” ማለታቸውን ነው ፕሮፌሰር መረራ በወቀሳ ያስታወቁት።

እንደተባለው ቢያደርጉና ከአቶ ለማ በስተቀር ማንም ባልተካተተበት ሁኔታ”ኦህዴድ ፍርሷል” በሚል አቶ ለማ አውጀው ቢሆን ኖሮ ምን ሊመታ እንደሚችል ብዙም እንዳልታሰበበት መረራ አልሸሸጉም። ይሁን እንጂ አቶ ለማ “አደጋው የከፋ ይሆናል። አገር ይበተበጣል። ግብታዊ መሆን አያዋጣም” በሚል ምላሽ ይሰጡ እንድነበር ጉዳዩን አስቀድመው ሲከታተሉ የነበሩ ተናግረዋል። መረራ ግን ከወቀሳ ውጪ አቶ ለማ ለምን ” እምቢ” እንዳሉ ሚስጢር አድርገውታል።

May be an image of 5 people
ህብረቱ ሲመሰረት

” ለማ በምን እንደቆረበ አይገባኝም” ያሉት መረራ ዛሬ በኢትዮጵያ ፖለቲካ አቶ ለማ መገርሳ ምንም እንደሆኑ አመልክተዋል። በጠርጴዛ ውይይቱ ወቅትፕሮፌሰር መረራ እየሳቁ በቀልድ አዋዝተው ጃዋርን እንደሚያደንቁ ተናግረዋል። ” እኛ 30 ዓመት ጮኸን ምንም ሳናገኝ እሱ ገንዘብ በጆንያ ይሰበስብ ነበር” በማለት የማስተባበር አቅሙን ገልጸዋል።

Exit mobile version