Site icon ETHIO12.COM

“የት እጅ እንስጥ” ኤርትራዊያን፤ “እጅ ስጡ” ደብረጽዮን

የትህነግ መሪ ዶክተር ደብረጽዮን የኤርትራ ወታደሮች እጅ እንዲሰጡ ላቅረቡት ጥሪ የኤርትራ አክቲቪስቶች ” የት መጥተን እጅ እንስጥ?” ሲሉ ጥሪው የጭንቀት እንደሆነ በመጥቀስ አጣጣሉ። ቅዠት መሆኑንንም አመልክተዋል።

ከፕሬዚዳንት ኢሳያስ፣ ከጦር መሪዎቻቸውና ባለስልጣኖቻቸው በስተቀር ለኤርትራ ሕዝብ ልዩ ክብርና ፍቅር እንዳላቸው በትህነግ ስም የገለጹት ዶክተር ለኤርትራ የጦር ሰራዊት እጅ እንዲሰጡ ጥሪ ሲያቀርቡ የትግራይ ጦር ኤርትራን ከቦ ፣ የጦር የበላይነት ተቀዳጅቶ ወይም ቁልፍ ቦታዎችን ይዞ ስለመሆኑ አላስታወቁም። ይልቁኑም ጆ ባይደን በፈረሙት የቅድመ ማዕቀብ ትዕዛዝ የኤርትራ ሃይል ከትግራይ እንዲወጣ ተጠይቋል።

በካናዳ የሚኖሩት አክቲቪስት አቶ ዮሃንስ እንዳሉት ኤርትራ እንዳለቀላት ወያኔ መናገር ከጀመረ አስራ ስምንት ዓመት ሆኗል። የኢትዮጵያ መንግስት እንዳለቀለት መናገር ከጀመሩ ሶስት ዓመት ሆኗቸዋል። ከቀድሞ ይልቅ አሁን ጉልበታቸው ሞቶና በችግር እየተጠበሱ ባለበት ሁኔታ ” የኤርትራን ሰራዊት እጅ ስጥ ብሎ ጥሪ ማስተላለፍ የአስተሳሰብ ጤንነት መጓደልና የተስፋ መቁረጥ ጉዳይ ነው” ብሏል።

“በራሱ ምኞትና ቅዠት የሚመራው ትህነግ ከምን ተነስቶ ይህን ጥሪ እንዳቀረበ የትግራይ ተወላጆች ራሳቸው ይጠይቁታል” ያሉት አቶ ዮሃንስ ” ድሮ ሁሉ በጁ እያለ ያልሆነለትን ምኞት ዛሬ በችግር ተዘፍቆና ዙሪያውን ተወሮ ያለ ቡድን የአንድን አገር ሰራዊት ናና እጅህን ስጠኝ ሲል መስማት የዘመኑ ታላቅ ኮመዲ ነው” ብለዋል።

ከለውጡ በሁዋላ “ታላቋ ትግራይ” በኢትዮጵያና ኤርትራ ፍርስራሽ ላይ እንደምትገነባ የትህነግ አመራሮችና ድደጋፊዎች፣ መደበኛ አደረጃጀቶች በተደጋጋሚ ሲናገሩ እንደነበር፣ የኤርትራን ደጋማ ስፍራዎች ወደ ትግራይ ጠቅልለው ቆላውን ሌላ ግዛት ለማድረግ ንድፍ ማዘጋጀታቸውን ሲያስታውቁ እንደነበር በመጥቀስ የኤርትራ ተወላጆች ሲናገሩ እንደነበር ይታወሳል።

የትህነግ ደጋፊ የትግራይ ተወላጆች በገሃድ የኤርትራ ደጋማ ስፍራዎች የትግራይ አካል መሆናቸውን በመጥቀስ ውስጥ ለውስጥ እንቅስቃሴ መጀመሩንና ድርጅታቸው ሻዕቢያን አስወግዶ ታላቋ ትግራይ እንደምትገነባ በተደጋጋሚ በይፋ ይናገር እንደነበር ይታወሳል። አሁንም ይህ አሳብ በሂደት ላይ እንደሆነ ያምናሉ።

” ኢትዮጵያዊ አይደለንም” የሚሉ ጥቂት የትግራይ ተወላጆች ከላይ የተገለጸውን ሃሳብ እንደሚናፍቁ ቢገለጽም ” አሁን ላይ መለየት አያዋጣም” የሚሉ መኖራቸውን ጠቅሰን መዘገባችን ይታወሳል።

Exit mobile version