ራሱን የኦሮሞ ነጻ አውጪ ሰራዊት ብሎ የሚጠራው ታጣቂ ሃይል አመራሮች የሰላም ጥሪ ተቀብለው ሊገቡ መሆኑ ተሰማ። ይህን የሚያመቻቹ ወገኖች ከፍተኛ ሩጫ ላይ እንደሆኑም ታውቋል። የበታች አመራሮች በየአቅጣጫው እጅ እየሰጡ ነው።
በቅርቡ ” ነገሮች ተበላሽተዋል። አዛዥና ታዛዥ የለም። የሚሰማ ጠፍቷል” በሚል ማብራሪያ ሲሰጥ የተድመጠው ጃልመሮን ጨምሮ በርካታ የቡድኑ አመራሮች የሰላም ጥሪ ተቀብለው እንዲገቡ ጥድፊያ ላይ ያሉት ቀደም ሲል በታንዛንያና ዛንዚባር የተደረገውን ንግግር ያመቻቹት ወገኖች እንደሆኑ ዜናውን ያካፈሉን አመልክተዋል።
አገር በቀል ባህላዊ መስመር የሚከተሉት እነዚህ ወገኖች የአገር መከላከያ በስፋት እያካሄደ ያለውን ዘመቻ ተከትሎ እየተመዘገበ ያለው ውጤት ጥረታቸውን ሊሳካላቸው ጫፍ መድረሱን ጠቁመዋል። የመከላከያ ዙሪያ መለስ ዘመቻና የሕዝቡ መሰላቸትና ምሬት ሌላው ድጋፍ ሰጪ ምክንያት እንደሆነም ተሰምቷል።
በኦነግ የትግል ታሪክ አስረክቦት የማያውቀውን የወርቅ ማውጫና የቤጊ ምሽጎች ሙሉ በሙሉ ማጣቱን ተከትሎ አመራሮቹ ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ማፈግፈጋቸው ተመልክቷል።
በጋምቤላ በኩል የተሰለፈው የአገር መከላከያ ቀለበቱን እያጠበበ መምጣቱን ተከትሎ በቅርቡ ምን ሊከሰት እንደሚችል ባይታወቅም፣ አሁን ላይ የኦነግ ሰራዊት መሪዎች የሰላም ጥሪ እንዲቀበሉ እየተደረገ ያለው ጥረት እጅግ አበረታች ምላሽ ማግኘቱ ተሰምቷል። ሰሞኑን እጅግ ሰፊ ቁጥር ያላቸው የሸኔ ታጣቂዎች በየግንባሩ እጅ መስጠታቸው የዚሁ የተጀመረው ስራ ጅማሮ እንደሆነ ዜናውን ያጋሩን አስታውቀዋል።
የዘወትር ተባባሪያችን የኦፌኮ አባል ” አሁን ላይ አማራጩ የሰላም መንገድ ብቻ ነው። ህዝብም ተማሯል። በውስጣቸውም ክፍፍሉ ሰፍቷል። ይህንንም ራሳቸው ይፋ አድርገውታል” ሲሉ ለጉዳዩ እንግዳ እንዳልሆኑ ጠቁመዋል።
ዜናውን ያጋሩን እንዳሉት አሁን ላይ ቀን ቆርጦ መናገር ባይቻልም፣ በኦሮሚያ ነፍጥ ያነሱ ወገኖች በሰላማዊ ትግል ሽፋን የሚገፏቸውን አካላት ገፍተው ወደ አንድ ሰላማዊ መድረክ ተጠቃለው እንደሚመጡ አመልክተዋል።