Site icon ETHIO12.COM

የሚኒስትሮች ምክር ቤት ለሰባት ኩባንያዎች የከፍተኛ ደረጃ የማዕድን ምርት ፈቃድ እንዲሰጥ ተጠየቀ

– ኩባንያዎቹ ከ47 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ እንደሚያስገኙ በተካሄደው የአዋጭኘነት ጥናት ተገምቷል
የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከ47 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለሚያስገኙ ሰባት ኩባንያዎች፣ የከፍተኛ ደረጃ ማዕድን ምረት ፈቃድ እንዲሰጥ ተጠየቀ።
ለሚኒስትሮች ምክር ቤት የቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ለመጀመርያ ጊዜ የከፍተኛ ደረጃ የብሮሚንና የክሎሪን ማዕድን ምርት ፈቃድ እንዲሰጥ የተጠየቀበት እንደሆነ የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል።
በጥቅሉ ወደ ምርት ለመግባት የከፍተኛ ደረጃ የምርት ፈቃድ እንዲሰጣቸው የተጠየቀው ለሰባት ኩባንያዎች ሲሆን፣ የኩባንያዎቹ አጠቃላይ ካፒታል 18.58 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ምንጮች ገልጸዋል።
ከማዕድንና ነዳጅ ሚኒስቴር የማዕድን ምርመራ ፈቃድ ወስደው አዋጭ የወርቅ ምርመራ ሲሠሩ የነበሩ አራት የወርቅ ማዕድን ኩባንያዎች፣ ሁለት የእምነበረድ፣ ከጨዋማ ሐይቅ የብሮሚንና የክሎሪን ማዕድን ፍለጋ በማከናወን ላይ የነበረ አንድ ኩባንያ ናቸው። የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስቴር የሕግ፣ የቴክኒክና የኢኮኖሚ ባለሙያዎች ቡድን በማቋቋም የኩባንያዎቹን ማመልከቻ ገምግሟል።
በዚህም የኩባንያዎቹን የምርት ቦታና ዓይነት፣ መነሻ ካፒታላቸውን፣ የፕሮጅክቶቹ አዋጭነትና ኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦ እንደ ገመገመ፣ እንዲሁም የባለሙያዎቹ አስተያየትን በማከል የውል ስምምነት ድርድር ከኩባንያዎቹ ጋር አድርጎ የመጨረሻ የውሳኔ ሐሳቡን ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ማቅረቡን ከምንጮች የተገኘው መረጃ ያመለክታል። ኩባንያዎቹ ከ47 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ እንደሚያስገኙ አዋጭነት ጥናት መገመቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከፍተኛ የወርቅ ማዕድን የማምረት ፈቃድ የጠየቁት አራት ኩባንያዎች ለመሰማራት የጠየቁበት የወርቅ ክምችት የሚገኘው በጋምቤላ ክልል ሲሆን፣ ብሮንዝና ክሎሪን ለማምረት ከፍተኛ የማዕድን ማምርት ፈቃድ የጠየቀው ኩባንያ ደግሞ በአፋር ክልል የሚገኘውን ክምችት ለማምረት መጠየቁን መረጃው ያመለክታል።
ምንጭ፡- ሪፖርተር

Exit mobile version