Site icon ETHIO12.COM

አሜሪካ ኢትዮጲያን ከአጉዋ ተጠቃሚነት ለማቀብ ያሳየችውን ዝንባሌ እንድታጤን ተጠየቀች

በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ አለመረጋጋቶች በተለይም በሰሜኑ ክፍል የዘለቀውን ግጭት መሠረት በማድረግ አሜሪካ ኢትዮጵያን ከአጉዋ ተጠቃሚነት የማቀብ ፍላጎት ስለማሳየቷ እየተነገረ ነው። ይህ ፍላጎት ባልተገባ አተያይ የተቃኘ በመሆኑ የአሜሪካ መንግስት ተመልሶ እንዲያጤነው በሀዋሳ ኢንደስትሪያል ፓርክ የተሠማሩ አምራቾች ጠይቀዋል። ናሳ ጋርመንት የተሰኘው ንብረትነቱ የኢትጵያውያን የሆነው የጨርቃጨርቅ አምራች በ7 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር መዋእለ ንዋይ የተጀመረ ነው። በኢንዱስትሪ ፓርኩ ውስጥ ሁለት ሼዶች አሉት።

ለ 1 ሺህ 400 ሰራተኞች የስራ እድል ፈጥሯል። የድርጅቱ ዋና ስራ አስፈጻሚ ራግቨንድራ ፓተር እንደተናገሩት ድርጅቱ የሚያመርታቸው የጨርቃጨርቅ ምርቶች ሙሉ በሙሉ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ናቸው። 99 በመቶው ለአሜሪካ ገበያ ፤ ቀሪው አንድ በመቶ ለአውሮፓ እና እንግሊዝ ገበያ የሚቀርብ ነው ብለዋል።ድርጅቱ ከዚህ በኋላ ለ2-3 አመታት የሚዘልቅ የምርት ትእዛዝ እንዳለው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለዘርፉ ምቹ ናት ያሉት ዋና ስራ አስፈጻሚው የሰው ሀይል እና የመንግስት ድጋፍን ለአብነት ጠቅሰዋል ።



ሀገሪቱ ካለምንም የኢኮኖሚ ጣልቃ ገብነት ያላትን እምቅ ሀብት ከተጠቀመች የአለም የጨርቃጨርቅ ምርት ኤክስፖርት ገበያ መሪ የምትሆንበት ጊዜ ሩቅ አይደለም ብለዋል። ባንግላዴሽ በአመት ከ15 ቢሊዮን ዶላር የጨርቃጨርቅ ምርት ኤክስፖርት በማድረግ የወቅቱ መሪ ስትሆን ኢትዮጲያ አሁን በዘርፉ ያላትን እንቅስቃሴ አጠናክራ ከቀጠለች ከ10 አመታት በኋላ የቀዳሚነቱን ደረጃ እንደምትረከብ ገልጸዋል ።

ናሳ ጋርመንት ባለፈው አመት ከኤክስፖርት 6 ሚሊዮን ዶላር ያገኘ ሲሆን በተያዘው አመት ከ23-25 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት ማቀዱን ጠቁመዋል ። ሆኖም ያለፈው ውጤትም ሆነ ቀጣይ እቅድ መሰረታቸው የኢትዮጲያ የአጉዋ ተጠቃሚነት እድል መሆኑን አንስተዋል። በአጉዋ ተጠቃሚነት ዙሪያ ኢትዮጲያን ለማቀብ የታየው ፍላጎት ሊጤን የሚገባው ነው ያሉት ዋና ስራ አስፈጻሚው በነበረበት መቀጠል እንዳለበት አስረድተዋል። ኢፔክ ግሩፕ ሌላው በሀዋሳ ኢንደስትሪያል ፓርክ የሚገኝና በተመሳሳይ ዘርፍ የተሰማራ ድርጅት ነው ።

ለ2300 ዜጎች የስራ እድል ፈጥሯል። የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ ዋሲም ሲዲኩዊ እንደገለጹት ሌሎች ተጨማሪ 3 ፋብሪካዎችን በፓርኩ ስራ ለማስጀመር ታቅዷል። በዚህም ተጨማሪ ከ6000 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል። ነገር ግን ይህ እውን የሚሆነው የሀገሪቱ የአጉዋ ተጠቃሚነት እስከተረጋገጠ ድረስ መሆኑን አስገንዝበዋል። በመሆኑም የኢትዮጲያ መንግስት አስፈላጊውን ውይይት በማድረግ የአሜሪካ መንግስት እውነታውን አውቆ ፍላጎቱን እንዲመረምር መገፋፋት አለበት ብለዋል። በአምራች ድርጅቶች በኩል የመንግስትን ጥረት እንደሚደግፉ እና የበኩላቸውን እንደሚወጡ ሀላፊዎቹ አስታውቀዋል ።

source – ኢትዮ የንግድ እና ኢንቨስትመንት መድረክ

Exit mobile version