Site icon ETHIO12.COM

አዲስ አበባ- “ ብሔርን መሰረት ያደረገ ማዋከብ እንዳለ ተደርጎ የሚሰራጨው መረጃ አሉባልታ ነው”

በመዲናዋ ብሔርን መሰረት ያደረገ ማዋከብ እንዳለ ተደርጎ የሚሰራጨው መረጃ ከእውነት የራቀ አሉባልታ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ የኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ዮናስ ዘውዴ ገለጹ።

የመዲናዋ ነዋሪዎች በኢትዮጵያ ላይ የተቃጣውን የህልውና አደጋ በመቃወም ያካሄዱት ሰልፍ የዓለምን ትኩረት የሳበ እንደነበርም ተናግረዋል።

የ ‘ህወሃት’ እና ‘ሸኔ’ አሸባሪ ቡድኖችን ሀገር የማፍረስ ተልእኮ ለማስፈጸም እንደሚንቀሳቀስ የሚጠረጠር የየትኛውም ብሔር ተወላጅ በቁጥጥር ስር እንደሚውልም ነው የተናገሩት፡፡

የአዲስ አበባ የኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ዮናስ ዘውዴ ዛሬ በሰጡት መግለጫ የከተማዋን ሰላም ለማረጋገጥ የጸጥታ አካላት ከህዝቡ ጋር በመሆን በተቀናጀና በተናበበ መልኩ እየሰሩ ስለመሆኑ አንስተዋል።

በመዲናዋ የተጠርጣሪ ቤቶች ላይ የፍተሻ ስራ ከመጀመሩ በፊት የአዲስ አበባ የጸጥታ ቢሮ ፍቃድ ያላቸውም ሆነ ፍቃድ የሌላቸው የመሳሪያ ባለቤቶች እንዲያስመዘግቡ መደረጉን ነው የገለጹት፡፡

አዲስ አበባ የበርካታ ዓለም አቀፍ ተቋማት መቀመጫና የፖለቲካ ማዕከል እንደመሆኗ መጠን ሰላሟን ለማስጠበቅ የጸጥታ አካላት ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰሩ ስለመሆኑ ገልጸዋል፡፡

በዚህም የአዲስ አበባ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ፣የአዲስ አበባ ፖሊስ ፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ የሪፐብሊካን ጥበቃ የኦሮሚያ ፖሊስ በጋራ እየሰሩ መሆናቸውን የቢሮው ኃላፊ ገልጸዋል።

በመዲናዋ በተደረገው የፍተሻ ስራ በቁጥር 27 ሺህ የሚሆን የትግራይ ልዩ ሃይል የደንብ ልብስ፤ የአፋር ልዩ ኃይል የደንብ ልብስ፣ የፌዴራልና የአዲስ አበባ ፖሊስ የደንብ ልብሶች፣ የጦር ሜዳ መነጽሮች፣ ኮምፓስ፣ ሳተላይትና የጦር መሳሪዎች መገኘታቸውን አንስተዋል።

በተጨማሪ በርካታ የባንክ ደብተሮች፣ ፓስፖርቶችና የተለያዩ የውጭ ሀገራት የብር ኖቶች መገኘታቸውን ነው የተናገሩት፡፡

የጸጥታ አካላት የመዲናዋን ሰላም ለመጠበቅ እያከናወኑ ያሉትን ፍተሻና ተጠርጣሪዎችን የመያዝ ተግባር ከብሔርና ማንነት ጋር ለማያያዝ የሚጥሩ አካላት መኖራቸውን ጠቅሰው፤ ይህም ከእውነት የራቀ አሉባልታ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የ ‘ህወሃት’ እና ‘ሸኔ’ አሸባሪ ቡድኖችን ሀገር የማፍረስ ተልእኮ ለማስፈጸም እንደሚንቀሳቀስ የሚጠረጠር የየትኛውም ብሔር ተወላጅ በቁጥጥር ስር እንደሚውልም ነው የተናገሩት፡፡

በቁጥጥር ስር በሚውሉ ተጠርጣሪዎች ላይ አስፈላጊው ማጣራት እንደሚከናወንም ነው የተናገሩት፡፡

በሌላ ዜና የመዲናዋ ነዋሪዎች በኢትዮጵያ ላይ የተቃጣውን የህልውና አደጋ በመቃወም ያካሄዱት ሰልፍ የዓለምን ትኩረት የሳበ እንደነበርም የቢሮው ኃላፊ ተናግረዋል፡፡

የመዲናዋ ነዋሪዎች ሀገርን ለማደን ለቀረበው ጥሪ እየሰጡት ላለው ምላሽ ምስጋናም አቅርበዋል።

ከቀናት በፊት በመዲናዋ ለመከላከያ ሰራዊትና በህልውና ዘመቻው እየተሳተፉ ላሉ የጸጥታ አካላት የተደረገው የገቢ ማሰባሰብ ስራ ስኬታማ እንደነበርም አቶ ዮናስ ተናግረዋል፡፡

በመርሃ-ግብሩ በሁለት ቀናት ብቻ ከአንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡን ጠቅሰው፤ ይህም ሃብት የሚፈጠረው ሀገር ሲኖር ብቻ መሆኑን መልዕክት የሰጠ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ለከተማዋ ሰላምና ደህንነት መጠበቅ እያበረከቱት ያለውን አስተዋጽኦ አድንቀው፤ በቀጣይ ይህን ተግባር አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

-አካባቢህን ጠብቅ

_ ወደ ግንባር ዝመት

_ መከላከያን ደግፍ

ህዳር 02 ቀን 2014 (ኢዜአ)

Exit mobile version