Site icon ETHIO12.COM

ሀሰተኛ መንግስታዊ ሰነዶችን በማዘጋጀት ለግል ጥቅም አውለዋል በተባሉ ላይ ክስ መሰረተ

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ፍትህ ሚኒስቴር ሀሰተኛ መንግስታዊ ሰነዶችን በማዘጋጀትና በመገልገል በጉምሩክ ኮሚሽን የተወረሰ ንብረትን በማውጣት ለግል ጥቅም አውለዋል የተባሉ ሁለት ግለሰቦች ላይ የሙስና ወንጀል ክስ መሰረተ፡፡

እንደ ዐቃቤ ህግ ክስ ሰይድ ፋንታው አሊ እና ጥላሁን አበጋዝ ሁን የተባሉ ተከሳሾች የሙስና ወንጀል አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀጽ 23(1)(ሀ) ስር የተመለከተውን በመተላለፍ አንዳርጋቸው ብስራት በተባለ አስመጪ ስም ወደ ሀገር ገብቶ ከቃሊቲ ወደብ መውጣት ባለበት ተገቢ ጊዜ ባለመውጣቱ በኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን የተወረሰ ብዛቱ 89 ካርቶን አጠቃላይ የዋጋ ግምቱ ብር 1 ሚሊዮን 538 ሺህ 392.81 የሆነ የመኪና መለዋወጫ ከሚገኝበት ከኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ቃሊቲ ቅ/ጽ/ቤት ትክክለኛ የአሰራር ሂደቶችን ተከትሎ የወጣ በማስመሰል ለዚህም እንዲረዳቸው በተለያዩ ግለሰቦች ስም ሀሰተኛ ሰነዶችን በማዘጋጀትና እቃውን በማውጣትና ለግል ጥቅማቸው በማዋል ወንጀል መጠርጠራቸዉን አስታዉቋል ፡፡

የክስ መዝገቡ በዝርዝር እንደሚያስረዳዉ 1ኛ ተከሳሽ ሀሰተኛ ሰነዶችን በመጠቀም እቃዎቹን በኮንቴነር ወስጥ አድርጎ በከባድ ተሸከርካሪ አስጭኖ ከኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉሙሩክ ባለስልጣን ቃሊቲ ቅርንጫፍ ይዞ ከወጣ በኋላ በአንደኛ የዐቃቤ ህግ ምስክር አማካኝነት ለሁለተኛ ተከሳሽ በመላክ፣ 2ኛ ተከሰሽ በበኩሉ በቀን 16/03/2014 በአንደኛ ተከሳሽ አማካኝነት ከጉምሩክ የወጣውን የመኪና መለዋወጫ ትክክለኛ የንብረቱ ባለቤት ሳይሆን መስሎ የተቀበለ እና ለዚሁ ጉዳይ በተከራየው መጋዘን ውስጥ እንዲራገፍ ካደረገ በኋላ የወንጀሉን ፍንጭ ለማጥፋት በማሰብ ዕቃዉ የተጫነበትን ኮንቴነር ፍቃዱ ይትባረክ ለተባለ ግለሰብ የሸጠለት በመሆኑ ሁለቱም ተከሳሾች በፈፀሙት ሀሰተኛ መንግስታዊ ሰነዶች በማዘጋጀትና በመገልገል በጉምሩክ ኮሚሽን የተወረሰ ንብረትን በማውጣት ለግል ጥቅም ማዋል የሙስና ወንጀል ክስ ቀርቦባቸዋል፡፡

በመሆኑም ተከሳሾቹ ጥር 17/2014 ዓ/ም በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሙስና ወንጀከል ችሎት የቀረቡ ሲሆን፥ የቀረበባቸው ክስ እና ማስረጃ በችሎት ተነቦላቸው የክስ መቃወሚያ ያላቸው እንደሆነ ከጥር 26/2014 በፊት እንዲያቀርቡ እና ዐቃቤ ህግ ምላሽ እንዲሰጥ ትዕዛዝ የተሰጠ ሲሆን ፍርድ ቤቱም በሚቀርበው መቃወሚያ ላይ ብይን ለመስጠት ለጥር 26/2014 ቀጠሮ መስጠቱን ከፍትህ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ይመላክታል፡፡

Exit mobile version