Site icon ETHIO12.COM

«የአማራ ፖለቲካ በጩኸት የተሞላ፣ ዝርው እየሆነ፣ አጋርና ሀይል ከማሰባሰብ ይልቅ ገፊና ሀይል በታኝ ዝንባሌ እያሳየ ይገኛል»

የአማራ ህዝብ ጠላቶች አንድነቱን ለመሸርሽር፣ ሀይሉን ለመበተን፣ አቅሙን ለማዳከም፣ አጋር አልባ ለማድረግ፣ “በዘላቂነት ማህበራዊ ረፍት ለመንሳት” ብሎም ቀጣይ የፖለቲካ ሀይል እንዳይሆን ለማድረግ የታቀዱና የተቀናጁ ሴራዎችን ሲፈፅሙበት ቆይተዋል። የተለያዩ ስልቶችን በመጠቀም ህዝቡን ከማዕከል ገፍቶ ማስወጣት የጠላቶቹ ግብ ነው።

ስለሆነም የህዝቡ ትግል ለነዚህ የሴራ ስምሪቶች ማርከሻ መሻት ይሆናል፣ ትግሉ በሂደት እየተጠናከረ ወደ ማዕከል (progressively towards the center) መቃናት አለበት፣ ፖለቲካውም ከዳርቻ (pheripheral) ቅኝት እየተላቀቀ መሄድ ይኖርበታል ማለት ነው። ደመነፍሳዊ ከሆነው የኩርፊያና የጩኸት ፖለቲካ እየተላቀቀ ምክንያታዊነትን እየተላበሰ ሊሄድ ይገባል።

ከፖለቲካ ርምጃ በፊት የሀይል አሰላለፍ ትንተና (correllation of forces) መስራት ያስፈልጋል። የሀይል አሰላለፍ ትንተና ገቢራዊ አዋጭነትን (pragmatism) እንጂ ምኞትን (wishful thinking) መሰረት ማድረግ የለበትም—On the basis of what works, based on merits, and not divorced from reality.

ሆኖም በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የአማራ ፖለቲካ በጩኸት የተሞላ፣ ዝርው እየሆነ፣ አጋርና ሀይል ከማሰባሰብ ይልቅ ገፊና ሀይል በታኝ ዝንባሌ እያሳየ ይገኛል። በየፊናውና በደመነፍስ የሚደረግ እንዘጭ እምቦጭና ጩኸት በሌላው ጎራ ምን እየተከናወነ እንደሆነ እንኳ ለመስማት አያስችልም!

አንዳንድ ወገኖች የሚያደርጉትን ኃላፊነት የጎደለው እንቅስቃሴ ስናይ ግራቀኙን የማየትና የማጤን አቅማቸውን (second thoughts) የነሳቸው ምን ይሆን? ያስብላል። ስትራቴጂካዊ ጉዳዬችን ሙሉ በሙሉ በመዘንጋት በደራሽ አጀንዳዎች የመጠለፍና ቅርብ አዳሪ የመሆን አደጋ አንዣቧል።

በርግጥ ይህ ሰርግና ምላሽ የሆነላቸው አካላት እንዳሉ ተመልክተናል። ከኛ መዳከምና ውድቀት ብሎም ከድፍን ሀገር ምስቅልቅል ትርፍ ለማጋበስ የተሰለፉት ኃሴት ላይ ናቸው።

Ah, it is just their calling, walk of life! ለፖለቲካ ትርፍ ሲባል እናቶችና ህፃናት ሳይቀሩ በግፍ የሚገደሉበት ዘመንና ሀገር ውስጥ እንገኛለን፣ የፖለቲካል ሞራሊቲ የሁሉም አካል መርህ ሊሆን አይችልም! ጥረታችን ጠላቶቻችን የተመኙልንን ውድቀት የሚያሳካ መሆን የለበትም!

የትግሉ ሁሉ ማሳረጊያ እና የብሄራዊ ፖለቲካችን ማደማደሚያ በሆነው የድርድር መድረክ (ምዕራፍ) ውስጥ በብቃት ለመሳተፍና ግባችንን ለማሳካት ከፈለግን ተገቢውን ቅድመ-ዝግጅት ማድረግ የግድ ይሆናል። ሌላው ቢቀር የጊዜን ፋይዳ እንኳ በቅጡ መገንዘብ ይገባል። በተዓቅቦ የምናሳካው የፖለቲካ ስራ እንደሚኖርም መገመት ጠቃሚ ነው። ሁሉንም የመናገር አባዜ ሊጠናወተን አይገባም—የተለየ ነገር ሲያጋጥመን ልማድ ነው በሚል አድማጭ ሊያሳጣንም ይችላል!

የድርድር መድረክ የበዓል ፕሮግራም አይነት አይደለም፣ አጀንዳ መለየት፣ የድርድር አቅም መፍጠር፣ በተጓዳኝ የሚኖረውን መገመትና ሳይንሳዊ መውጫ መንገድ መቀየስን የሚጠይቅ ከባድ ማዕቀፍ ነው።

ለማንኛውም የምንፈልገውን ሁሉ ማግኘትና ማሳካት አንችልም፣ ስለዚህ ሶብር አድርገን ወሳኝ የሆኑ ስትራቴጂክ ጉዳዬችን መለየትና አጥብቆ መያዝ ይገባናል።

ለተሻለ አላማ ተባብረን መሰለፍ ካለብን ጊዜው አሁን ነው!

Yesuf Ibrahim

Exit mobile version