Site icon ETHIO12.COM

ለማደኛው ወንጀለኛ አስራ አመስት ዓመት ጽኑ እስራት ተፈረደበት

ከባድ የውንብድና ወንጀሎችን ደጋግሞ የፈጸመው ግለሰብ ከህግ ተጠያቂነት ማምለጥ አልቻለም፤ በፈጸመው ወንጀልም በ15 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ተወስኖበታል

ተከሳሽ መስፍን አበበ በ1996 ዓ.ም የወጣውን የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ወንጀል ህግ አንቀፅ 671/ለ/ ስር የተመለከተውን በመተላለፍ በፈፀመው ከባድ የውንብድና ወንጀል በዐቃቤ ሕግ ክስ ተመስርቶበት ክርክር ሲደረግ ቆይቶ በስተመጨረሻ በ15 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ተወስኖበታል፡፡
የክስ መዝገቡ እንደሚያስረዳው ተከሳሽ ህዳር 17 ቀን 2014 ዓ.ም በግምት ከቀኑ 7፡00 ሰዓት ሲሆን በቦሌ ክ/ከተማ ወረዳ 01 ክልል ልዩ ቦታው ቦሌ ሚካኤል መቶ አስር ሰፈር ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ የግል ተበዳይ ሊዲያ ብርሀኑ የተባለች የራይድ አገልግሎት እንድትሰጠው ተስማምተው ኮድ 3B 19136 አ/አ በሆነ መኪናዋ ተሳፍሮ ከላፍቶ ኮንዶሚኒየም ቦሌ ሚካኤል አድርሳው 155 /አንድ መቶ አምሳ አምስት/ ብር ክፈል ስትለው እስኪ ስልክሽን አምጪ ሂሳቡን ልየው በማለት ከተቀበላት በኋላ ከወገቡ ጩቤ በማውጣት በዚህ ነው የምዘከዝክሽ ብሎ በማስፈራራት 1ኛ አንድ ሳምሰንግ ሞባይል ሞዴሉ S9 የዋጋ ግምቱ 20,000 /ሀያ ሺህ/ ብር፤ 2ኛ የጋብቻ የወርቅ ቀለበት 3 ግራም ባለ 21 ካራት የዋጋ ግምቱ 15,000 /አስራ አምስት ሺህ/ ብር፤ 3ኛ 140 /አንድ መቶ አርባ/ ብር ጥሬ ገንዘብ በአጠቃላይ 35,140 /ሰላሳ አምስት ሺህ አንድ መቶ አርባ/ ብር የሚገመት ንብረት ወስዶ ተሰውሯል፡፡

ተከሳሹ በሌላ መዝገብ በተመሳሳይ ድርጊት መስከረም 01/2014 ዓ.ም ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ሲሆን በቦሌ ክ/ከተማ ወረዳ 01 ክልል ልዩ ቦታው ካባ ሰፈር ተብሎ ከመሚጠራው አካባቢ የግል ተበዳ ባዩሽ ደመቀ ወ/ስላሴ የተባለችው ገለሰብ በሰረገላ ታክሲ አገልግሎት ከሳሪስ አቦ ዘንባባ ሆቴል አስከ ገርጂ ለመውሰድ በደረሳት ጥሪ መሰረት ተከሳሽን በምታሽከረክረው በኮድ 3-07790 በሆነ ሰረገላ ታክሲ ያሳፈረችና ጉዞ ከጀመሩ በኋላ እናቴን አሳፍረናት እንሄዳለን በማለት ወደ ሰፈር ውስጥ አስገብቷት ከመኪናው ወርዶ አንድ ግቢ በር በማንኳኳት አንዲት ሴት በሩን ከፍታ ካናገረችው በኋላ ተመልሶ በመምጣት የጋቢና በሩን ክፈችልኝ እናቴ እየመጣች ነው ሲላት በሩን ስትከፍትለት ጋቢና በመግባት ጩቤ አውጥቶ አንገቷ ላይ አጣብቆ በመያዝ ያለሽን ነገር በሙሉ አምጪ ብሎ በማስፈራራት 1ኛ የሴት ቦርሳ የዋጋ ግምቱ 3000 /ሶስት ሺህ/ ብር 2ኛ 7600 /ሰባት ሺህ ስድስት መቶ/ ጥሬ ገንዘብ 3ኛ አንድ አይፎን የዋጋ ግምቱ 4000 /አራት ሺህ/ ብር፤ 4ኛ ሳምሰንግ ጋላክሲ ተንቀሳቃሽ ስልክ የዋጋ ግምቱ 7000 /ሰባት ሺህ የሆነ እና የተለያዩ ሰነዶች የውጭ ሀገር መንጃ ፍቃድ፤ የተለያዩ የባንክ ደብተሮች፤ የስራ ቪዛ በአጠቃይ የዋጋ ግምታቸው 21,600 /ሀያ አንድ ሺህ ስድስት መቶ/ ብር የሚያወጣ ንብረት ይዞ ሮጦ ካመለጠ በኋላ በክትትል የተያዘ በመሆኑ በፈፀመው ከባድ የውንብድና ወንጀል ክስ ተመስርቶበት ፍርድ ቤት ቀርቧል፡፡

ተከሳሽ በችሎት ቀርቦ የዕምነት ክህደት ቃሉን ሲጠየቅ ድርጊቱን አልፈፀምኩም በማለት ክዶ የተከራከረ ስለሆነ ዐቃቤ ሕግ ክሴን ያስረዳሉ ያላቸውን የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎች በችሎት አቅርቦ አሰምቷል፡፡
ፍርድ ቤቱም ይህን ከመረመረ በኋላ የተከሳሽ የመከላከል መብቱ ተጠብቆለት ተከሳሽ የዐቃቤ ህግን ክስ ማስተባበል ባለመቻሉ ምክንያት ችሎቱ የጥፋተኝነት ውሳኔ አስተላልፎበታል፡፡

በዚህም መሰረት ፍ/ቤቱ የካቲት 30/2014 ዓ.ም በዋለው ችሎት ተከሳሽን ያርማል መሰል አጥፊዎችን ያስተምራል በማለት በ15 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ሲል ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ምንጭ የፌድራል ፍትህ ሚኒስቴር

Exit mobile version