Site icon ETHIO12.COM

በኢትዮጵያ – ከ3ኛ ክፍል ተማሪዎች 65 በመቶው ማንበብ አይችሉም፤ መምህራን 85 በመቶው ብቁ አይደሉም

በኢትዮጵያ – ከ3ኛ ክፍል ተማሪዎች መካከል 65 በመቶው ማንበብ አይችሉም፤

– የሚያስተምሩትን ትምህርት ከተፈተኑ መምህራን 85 በመቶው ብቁ አይደሉም

በኢትዮጵያ ካሉ የ3ኛ ክፍል ተማሪዎች 65 በመቶ ማንበብ እንደማይችሉ፤ የሚያስተምሩትን ትምህርት ከተፈተኑ መምህራን 85 በመቶ የሚሆኑት ብቁ አለመሆናቸው ተገለጸ።

ለትምህርት ስርዓቱ ውድቀትና ማነቆ ናቸው በተባሉ ተግዳሮች ላይ የትምህርት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በጅማ ዩኒቨርሲቲ መክረዋል።

የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና የትምህርት ሚኒስትር ዲኤታዉ ዶክተር ፋንታ በላይ ዛሬ የጅማ ዩኒቨርሲቲን በጎበኙበት ወቅት የትምህርት ስርዓቱ በኢትዮጵያ ያለበትን ደረጃ በግልፅ አስቀምጠዋል።

የትምህርት ስርዓቱን ከውድቀት ለመታደግና ሀገር ከሚገጥማት ተግዳሮት ሊታደግ የሚችል ትውልድ ለመፍጠር ችግሮች ላይ ግልፅ ውይይት ማድረግና ለመፍትሄ ማስቀመጥ ወሳኝ መሆኑን ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ ካሉ የ3ኛ ክፍል ተማሪዎች 65 በመቶ ማንበብ እንደማይችሉ፣ የሚያስተምሩትን ትምህርት ከተፈተኑ መምህራን 85 በመቶ የሚሆኑት ብቁ አለመሆናቸው ፣ ላለፋት ሰባት ዓመታት በየጊዜው የሀገር አቀፍ ፈተና መሰረቁም በመረጃ የተደገፈ ድክመት ሲሆን ፥ በተጨማሪ ትምህርት ቤቶችም 99 በመቶ አስፈላጊውን መስፈርት እንደማያሟሉ ተጠቁሟል ።

ለስርዓቱ ድቀት መነሻና ማነቆዎች የትምህርት ስርዓቱን ከፖለቲካው ጋር በመለየት ዩኒቨርሲቲዎች ከክልላዊና ብሄር ተኮር እሳቤ በማላቀቅ ተማሪን ማብቃት ግባቸው ሊሆን እንደሚገባ ሚኒስትሩ መግለጻቸውን የኤፍቢሲ ዘገባ ያሳያል።

ዩኒቨርሲቲዎችም የሚያከናውኑት የህንፃ ግንባታ ተማሪን ከማብቃት ግብ ጋር ሲነፃፀር የላቀ በመሆኑ የሚያስተቻቸው ስለመሆኑ የተጠቆመ ሲሆን ፥ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ከተጣረሰ አሰራር መውጣትና ከፖለቲካ መነጠል የትምህርት ስርዓቱን ከውድቀት ይታደገዋል ተብሏል ።

በቀጣይም ምክክሩ በቦንጋ ዩኒቨርሲቲ እንደሚቀጥል ታውቋል።

(ኢ ፕ ድ)

Exit mobile version