Site icon ETHIO12.COM

ለባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት የተዘረጋ የኤሌክትሪክ ሽቦ የሰረቁ በጽኑ እስራት ተቀጡ

ለባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት የተዘረጋ የኤሌክትሪክ ሽቦ ቆርጠው የሰረቁ ሁለት ተከሳሾች በጽኑ እስራት ተቀጡ

ለአዲስ አበባ የቀላል ባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት የተዘረጋ የኤሌክትሪክ ሽቦ ቆርጠው የሰረቁ ሁለት ተከሳሾች በጽኑ እስራት መቀጣታቸውን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ፡፡

ተከሳሽ ፀጋዬ ቴዎድሮስ እና ያብስራ ተስፋዬ በ1996 ዓ.ም የወንጀል ህግ አንቀጽ 32(1)ሀ እና የቴሌኮሙኒኬሽንና የኤሌክትሪክ ሀይል መሰረተ ልማት አውታሮችን ደህንነት ለመጠበቅ የወጣውን አዋጅ ቁጥር 464/2005 አንቀጽ 4ን በመተላለፍ ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ ቆይቷል፡፡

ተከሳሾቹ ንብረትነቱ የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንዚት አገልግሎት የሆነ 40 ሜትር ርዝመት እና 80 ሺ ብር የዋጋ ግምት ያለውን የባቡር የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ ሽቦ ቆርጠው መውሰዳቸውን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡

የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት የተከሳሾቹን ጥፋተኝነት በማስረጃ በማረጋገጥ እና ጥፋተኞችን ያርማል ሌሎችን ያስጠነቅቃል በማለት ፀጋዬ ቴዎድሮስ በ7 አመት ከ8 ወር ጽኑ እስራት እንዲሁም ያብስራ ተስፋዬ በ7 አመት ጽኑ እስራት እንዲቀጡ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

በመሰረተ ልማቶች ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን አስቀድሞ ለመከላከልም ህብረተሰቡ ከፀጥታ አካላት ጋር ያለውን ቅንጅት አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ሲል የአዲስ አበባ ፖሊስ መልእክቱን አስተላልፏል።

EPD

Exit mobile version