Site icon ETHIO12.COM

“በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ከ319 የእዳታ እህል የጫኑ ከባድ ተሽከርካሪዎች መቀሌ ደርሰዋል” OCHA

 ከ300 በላይ የእዳታ እህል የጫኑ ከባድ ተሽከርካሪዎች በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ትግራይ ክልል ዋና ከተማ መቀሌ መድረሳቸውን የተባበሩት መንግሥታት አስታወቀ፡፡

በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ይህን የሚያክል የእርዳታ እሕል የጫኑ ተሽከርካሪዎች ትግራይ ሲገቡ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ ድጋፍ ማስተባበሪያ ማዕከል ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

“319 የእርዳታ እህል የጫኑ ከባድ ተሽከርካሪዎች በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ትግራይ ደርሰዋል፤ ይህ ከሰኔ 2013 ዓ.ም ወዲህ በአንድ ሳምንት ውስጥ ትግራይ የገባ የእርዳታ እህል የጫኑ ከፍተኛ የተሽካሪዎች ቁጥር ነው” ብሏል ተቋሙ በመግለጫው፡፡

ወደ ትግራይ ይደረግ የነበረ የሰብአዊ ድጋፍ የማቅረብ ተግባር ሕወሓት የአፋር ክልል ዞን ሁለት ውስጥ የሚገኙ አራት ወረዳዎችን በወረራ መያዙን ተከትሎ ለሦስት ወራት ያህል ሰብአዊ እርዳታ የማጓጓዙ ሂደት መስተጓጎሉ ይታወሳል፡፡

ሆኖም የኢትዮጵያ መንግሥት ለሰብአዊነት ቅድሚያ በመስጠት የተናጠል ተኩስ የማቆም እርምጃ መጋቢት ወር ላይ ማወጁን ተከትሎ እርዳታ ዳግም ወደ ክልሉ መግባት መጀመሩ የሚታወስ ነው፡፡

ከዚያ ጊዜ ጀምሮ 571 ከባድ ተሽከርካራች 15 ሺሕ 500 ቶን የእርዳታ እህል ጭነው ትግራይ መግባታቸውን የተባበሩት መንግሥታት በመግለጫው ይፋ አድርጓል፡፡

በትግራይ ክልል እየተደረገ ያለውን የነብስ አድን እርዳታ ስርጭት ለተረጂዎች ሙሉ በሙሉ ተደራሽ ለማድረግ ተጨማሪ 68 ሺሕ ሜትሪክ ቶን ምግብ እንደሚያስፈልግም ተቋሙ በመግለጫው ጨምሮ አስታውቋል፡፡

Exit mobile version