Site icon ETHIO12.COM

የመጀመሪያውን የአማርኛ ቴሌፕሪንተር የፈጠሩት አቶ ተረፈ ራስወርቅ ከ1928 – 2014

በኢትዮጵያዊ የቴሌኮም ታሪክ የመጀመሪያውን የአማርኛ ቴሌፕሪንተር የፈጠሩት አቶ ተረፈ ራስወርቅ በ86 ዓመታቸው ሚያዝያ 30 ቀን 2014 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ።

በ 1928 ጣልያን በኢትዮጵያ ላይ ዳግማዊ ወረራ ባደረገ ጊዜ የሸዋ ነገስታት መቀመጫ በሆነችው አንኮበር ተወልደው በህጻንነታቸው የአርበኝነትን ኑሮ ከወላጆቻቸው ጋር እንዲኖሩ የተገደዱት አቶ ተረፈ ራስወርቅ ከዛ ጭፍጨፋ በመትረፋቸው እናታቸው “ተረፈ” ብለው ስም እንዳወጡላቸው ይናገራሉ።

የመጀመሪያ እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በአዲስ አበባ ተፈሪ መኮንን ት/ቤት ከተከታተሉ በኋላ በቀዳማዊ ኃ/ሥላሤ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የጀመሩትን ትምህርታቸውን ወደ አሜሪካ በመሄድ ከ Rensselaer Polytechnic Institute በእሌክትሪክ ምህንድስና የባችለር ዴግሪያቸውን ተቀብለው ኢትዮጵያን በሙያቸው ለ 10 ዓመታት ባገለገሉበት ጊዜ የአማርኛ ቴሌፕሪንተር እና የአማርኛ የጽህፈት መኪና (Amharic typewriter) ንድፍ አውጪ (Designer) በመሆን የፈጠራ ባለቤት መሆን ችለዋል። ከ 60 ዓመት በፊት ይህን ድንቅ ስራ ላበረከቱት ለ አቶ ተረፈ ራስወርቅ የኢትዮጵያ መንግስት እውቅና አለመስጠቱ በጣም ያሳዝናል። በህይወት እያሉ እውቅና ሰጥተናቸው ቢሆን ኖሮ ሌሎች የሳቸውን ፈለግ ተክትለው ለአገር እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ባደረጉ ነበር።

በዚህ ልዩ የሙያ ክህሎታቸው በተባበሩት መንግስታት ድርጅት (United Nations) ስር ሆኖ በመላው ዓለም በአገራት መከከል ለሚደረገው የስልክ ፣ ቴሌግራፍ ፣ የፋክስ፣ የኢንተርኔት እና ሳተላይት ወ.ዘ.ተ ደረጃ በሚያወጣው The International Telecommunication Union ልዩ ኤጀንሲ ውስጥ ለ 30 ዓመታት የአፍሪካ ሪጅናል ዳይሬክተር እና የዋና ፀሃፊው አማካሪ በመሆን አገልግለዋል። ይህ ኤጀንሲ መቀመጫው ጄኔቫ/ ስዊዘርላንድ ሲሆን በስሩ 193 አገራትን ፣ ክ 900 በላይ አህጉር አቀፍ እና አለም አቀፍ ድርጅቶችን፣ የትምህርት እና የንግድ ተቋማትን ያቀፈ ነው።
https://en.wikipedia.org/wiki/International_Telecommunication_Union

አቶ ተረፈ ራስወርቅ ከ40 አመት የስደት ኑሮ በኋላ ወደ አገራቸው በመመለስ በትውልድ ከተማቸው አንኮበር የፈረሰውን የዳግማዊ አጼ ምኒልክ ቤተ መንግስትን በማደስ ለቱሪስት መስህብ እንዲሆን ያደረጉ ድንቅ ኢትዮጵያዊ ነበሩ።

በአቶ ተረፈ ራስዎርቅ ከዚህ ዓለም በሞት መለየት ምክንያት የተሰማኝን ጥልቅ ሃዘን ለመላ ቤተሰባቸው መግለጽ እወዳለሁ።

ነብስ ይማር !!!

Solomon Tadesse
Boston, Massachusetts

Exit mobile version