Site icon ETHIO12.COM

ገቢ የማያስገኙ የዜና ርዕሶች

የማኅበራዊ ሚዲያ ሰለባዎች ዓይነታቸው ብዙ ነው። ልጆቻቸው የማኅበራዊ ሚዲያ ተግዳሮቶችን (ቻሌንጅ) በመውሰድ እልህ ውስጥ ገብተው የሞቱባቸው ጥቂቶች አይደሉም። “Blackout Challenge” የተሰኘው የቲክቶክ ተግዳሮት ፉክክር ውስጥ የገቡ ሕጻናትና ወጣቶች ሕይወታቸውን አጥተዋል። ሌሎች ጥቂት የማይባሉ ደግሞ የማኅበራዊ ሚዲያ ሱሰኛ ሆነው ሕይወታቸው የተበላሸ አሉ። የተጎጂው ቁጥር ሥፍር የለውም፤ የማኅበራዊ ሚዲያ አውታሮቹን የሚከስሱ ወላጆች ቁጥርም እንዲሁ እጅግ በርካታዎች ናቸው።

በማኅበራዊ ሚዲያ ዘገባ ምክንያት ሕይወታቸውን ከሚያጡት በተጓዳኝ አገራቸውንም እያጡ ያሉ ጥቂቶች አይደሉም። የዛሬ ስድስት ዓመት በቱርክ የተካሄደው መፈንቅለ መንግሥት የማካሄድና ሤራውን የማክሸፍ ሥራ ላይ የማኅበራዊ ሚዲያ ትልቅ አስተዋጽዖ አለው። አገር ወዳድ ቱርካውያን የወሬ ሰለባ አንሆንም ብለው አገራቸውን ሲያድኑ ሤራው የተካሄደባቸው ፕሬዚዳንት ረሲፕ ኤርዶጋን ሤራውን ለማክሸፍ ስልካቸውንና ማኅበራዊ ሚዲያን መጠቀማቸው በዋናነት የሚጠቀስ ነው።

ከላይ እንደተባለው የማኅበራዊ ሚዲያ ሰለባዎች ሕይወታቸውን እስከማጣት የደረሱ ናቸው። ሌሎች ደግሞ አሉ ዓይናቸው እስኪያብጥ፣ ጆሮአቸው እስኪደማ የወሬ ሱስ ሰለባ የሆኑ። ጠዋት ሲነሱ (ተኝተው ካደሩ) “ዛሬ ምን አለ” ብለው እንደ ነገረኛ ሰው በወሬ ቀናቸውን የሚጀምሩ። እነዚሀ ሰዎች ከጠዋቱ የመጸዳዳት ተግባራቸው በፊት በዜና ስም የሚለጠፍ ተራ ወሬና የመንደር አሉባልታ እንዲጸዳዳባቸው ራሳቸውን በፈቃዳቸው አሳልፈው የሰጡ ከንቱዎች ናቸው።

ከዚህ ዓይነት የቀን ጅማሮ በኋላ እንዲህ ዓይነቱ ሰው በልቡ ማኅደር ያለውም ሆነ ቀኑን ሙሉ ከአፉ የሚወጣው ጽድቅ ሳይሆን ርኩሰት፣ ነውር፣ ብልግና እና ውርደት ነው። ልቡን ለክፋትና ርኩሰት ባዘጋጀበት መጠን ቀኑን ሙሉ እያነፈነፈ አእምሮውን የሚሞላው ይህንን እየቀመሙ በሚግቱት ግጭት ጠማቂዎች፤ ክፋት ጠንሳሾችና አእምሮአቸው የላሸቀ የጭንቅላት ጉዳተኞች የወሬ መርዝ ነው። ከንጋት ጀምሮ ወደ ውስጡ ባስገባው መርዝ መጠን እርሱም በየፊናው መርዙን ሲተፋ ይውላል። ይህንን በማስፈጸም ማኅበራዊ ሚዲያ የተዋጣለት መሣሪያ ነው።

ባለፉት ሁለት ሦስት ቀናት በአገራችን የተዋጣለት ሥራዎች ተከስተዋል። በወለጋ የተጨፈጨፉትን ወገኖቻችን ልባችንን እያደማ ሌቦችን ወደሚገባቸው ቦታ ማስገባት ወሳኝ ሥራ ሆኖ ተስተውሏል። መከላከያም ከሸኔ ጋር ሲፋለም፣ ሠልጣኞችን ሲያስመርቅና ሌሎች ለአገር ግንባታ ወሳኝ የሆኑ ተግባራትን ሲፈጽም ነው የሰነበተው።

በተለይ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ የተሰገሰጉ ሌቦች በቁጥጥር ሥር የዋሉበት ያለፉት ሁለት/ሦስት ቀናት የሁሉም ትኩረት ተመሳሳይ ተግባራት በሁሉም የሥልጣን ተዋረድ ይቀጥል የሚል ነበር። በኮንዶሚኒየምም ሆነ በዕርዳታ ጉዳይ ሕዝብን ከመዝረፍ አልፈው የትህነግን የፖለቲካ ዓላማ ለማሳካት የተቀናጀ ሤራ ሲፈጽሙ የነበሩ በተያዙ ቀን እየተናበቡ የሚሠሩት አጀንዳ ሰጪዎቻችን የወሬአቸው ቀዳሚ ዜና ያደረጉትን ጉዳይ ምን እንደነበር መመልከቱ ከማኅበራዊ ሚዲያ ሱስ ለመላቀቅ ዓይን ከፋች ነው።

የትህነግና የግብጽ ልሳን የሆነው 360 ዋና ርዕስ ያደረገው ይህንን ነው፤

የአማራ ተቆርቋሪ ነኝ የሚለው የቀድሞው እስክስታ ወራጅና የዳዊት ወልደጊዮርጊስ አጋፋሪ አበበ በለው ደግሞ ይህንን ነው ቀዳሚ መረጃ አድርጎ ያቀረበው፤

በአስከፊው የትህነግ የግፍ ዘመን የመዝናኛ ፕሮግራም ያዘጋጅ የነበረው ማየት የተሳነው ቴዎድሮስ ጸጋዬ በማኅበራዊ ሚዲያው ጠጅ ለሚያሰክራቸው ተከታታዮቹ ይህንን ነው ርዕሰ ጉዳዩ ያደረገው፤

ሲሻው ቀዳሽ ዲያቆን፣ ሲሻው አራጅ ወያኔ፣ ሲሻው ወታደር፣ ሲሻው ደግሞ የሚዲያና ፖለቲካ ተንታኝ የሆነው ለ360ውም የዩትዩብ ጡረተኞች የዕለቱን አጀንዳ የሚሰጣቸው ስታሊን ደግሞ ዋና አጀንዳው ይህ ነበር፤

እነዚህ እየተናበቡ አገር በማፍረስ አጀንዳ ላይ የተሰማሩ፤ የየዋሆችን ልብ ለመስለብ ኢትዮጵያዊ ስምና ሠንደቅ ከፊት ለፊታቸው የሚያደርጉ፤ “ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር” እያሉ የሚምሉ የኮንዶሚኒየም ሌቦች ሤራ በተጋለጠበትና፤ ከረሃብተኛ የዕርዳታ እህልና ገንዘብ እየነጠቀ ራሱን ሲያበለጽግ የነበረው ምትኩ በተያዘበት ዕለት ለእነርሱ ይህ ለዐቅመ አጀንዳ የደረሰ፤ ለትንታኔ የበቃ ጉዳይ አልነበረም። እንደ እውነቱ ከሆነ ብቁ ሳይሆን ቀርቶ አይደለም። ያለተጠበቀው ኩነት በተከታታይ ያቀዱትን አጀንዳ የእንቧይ ካብ ስላደረገባቸው ነው። ከእነዚህ ግን የተለ ሌላ በወገኖቹ ደም የሚሸቅጥ አለ …   

በአምላክ ስም አማትቦ ጀምሮ የጥላቻ ቃላትን በመትፋት ሰይጣንን የሚያስንቀው፤ አእምሮው የተቃወሰ መሆኑን በራሱ አንደበት የመሰከረው ዘመድኩን በቀለ ደግሞ ሰሞኑን ሁሉ “አጀንዳዬን አልቀይርም”፤ “ኑ ለቅሶ እንድረስ” እያለ በወለጋ ወገኖቻችን ጭፍጨፋ ላይ ሲነግድ ነበር የከረመው። በዚህ የደም ንግድ ብዙዎችን አንዴ ጥቁር ሲያስለብስ፤ አንዴ ሲስለቅስ ከከረመ በኋላ እንደለመደው “(የስድብ) አገልግሎቴን በዚህ ደግፉ” ብሎ ለአንድ ሳምንት እንደማይኖር መረጃ ሰጥጦ ተሰናብቷል። ቆፈናሙ የጀርመን ብርድ ሳይገባ ፈታ፣ ላላ፣ ዘና ልበል፤ ከቤተሰቦቼ ጋር ልዝናናበት ተውኝ ብሎ አጀንዳውን ቀይሯል። አስለቅሶ፣ “ለአገልግሎቱ” መደጎሚያ ብሩን ሰብስቦ፣ አልቀይርም ያለውን አጀንዳ ቀይሮ ለሳምንት ተሰናብቷል።

ዘመድኩን እንደምክንያት የሰጠው የጀርመን መንግሥት በ9 ዩሮ ተዝናኑ ብሎናል የሚል ነው። ምነው ያ ሁሉ አማራ ተጨፍጭፎ ገና ደሙ ሳይደርቅ አንተ እንዴት አጀንዳ ለመቀየር አንጀትህ አስቻለህ? ብሎ የሚጠይቅ የለም። እንዴት በቀን 90 ጊዜ ትህነግና እነ ጃል መሮ የሚልኩልህን ፎቶ “የአማራ ደም” እያልህ እየለጠፍህ በአስከሬን ሳንቲም ስትሰበስብ እንዳልቆየህ አሁን ለመዝናናት ልብህ እሺ አለ? ብሎ የሚሞግት የለም። እኛን በየቀኑ “አጀንዳዬን አልቀይርም” ስትለን ቆይተህ ለምን እና እንዴት አጀንዳህን ለመቀየር ደፈርህ? የጀርመን መንግሥት በግድ ተዝናኑ፤ ካልተዝናናችሁ ትቀጣላችሁ አላለም፤ ምነው አንተ መዝናናቱ ግዴታ አደረግኸው? በተለይ እንዳንተ ዓይነቱ “አጀንዳዬን አልቀይርም” ባይ ምነው ለጀርመን መንግሥት “አይ እኔ ለቅሶ ላይ ነኝ፤ ሐዘን ላይ ተቀምጫለሁ፤ አልዝናናም፤ ተውኝ ላልቅስበት” ማለት አቃተው? በማለት ከተከታዮቹ የሚሞግት የለም። ምክንያቱም የአእምሮ መላሸቅ ሰለባ ስለሆኑ እውነቱ ውሸት፤ ውሸቱ እውነት ሆኖባቸዋል። በአደንዛዥ ዕፅ እንደሚደነዝዝ ሰው በወሬ ድግምግሞሽ ማሰብ እስከሚሳናቸው ደንዝዘዋል።   

በአሁኑ ሰዓት ከድምጺ ወያኔ፣ 360፣ TMH፣ ርዕዮት፣ ኢትዮ ፎረም ወዘተ እኩል ትግራይ ከሚሰሙ መካከል አንዱ ዘመድኩን በቀለ ሆኗል። ትህነግ ደጋፊህ ሆኖ ለሕዝቡ እንድትሰማ ሲፈቅድልህ በመናገር ነጻነት ስላመነ ሳይሆን ከድምጺ ወያኔ እኩል ካድሬው ስለሆንህለትና አጀንዳውን ፈጻሚ ምርጥ ወያኔ ስለሆንህለት ነው። ትህነግ ማለት አማራ ጠላታችን ነው፤ አማራን ማዋረድ፣ መግደል፣ መጨፍጨፍ፣ ማፈናቀል፣ መቅኖቢስ ማድረግ አለብን የሚለው ማለት ነው። የወልቃይትን ሕዝብ ከምድረገጽ ለማጥፋት ለ30 ዓመት የሞከረውና አሁን በቅርቡ ደግሞ አማራ ክልል መጥቶ ሒሳብ አወራርዳለሁ ባለው መሠረት የክልሉን መሠረተ ልማት አውድሞና ሊጥ ጠጥቶ የተባረረው ትህነግ ዘመድኩን በቀለ በሮማኖት አደባባይ መቀሌ ላይ እንዲሰማ ፈቅዷል። መረጃው እነሆ!

ትህነግ ሲያበሰብስ እንዲህ ነው። በአንድ በኩል ወዳጅ መስሎ ግፋ በለው፤ አብሬህ ነኝ ይላል። በሌላው ደግሞ የትህነግ ደጋፊ መሆንህን ለዓለም ያሳውቅብሃል። ዘመድኩን መቀሌ ላይ ሲደመጥ ቀድተው የላኩት ማንም ሳይሆኑ የትህነግ ካድሬዎች ናቸው። ዘመድኩን ተጠቁሯል፤ አጀንዳው የትህነግ አጀንዳ ነው። የፈለገ ቢያማትብ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ቢያውቅና ቢመረምር ቢያገላብጥ ዘመድኩን በቀለ የሚያራምደው አጀንዳ ከትህነግ አጀንዳ ጋር የሚመሳሰል ነው።

ከመግቢያው ላይ የተጠቀሱት የኮንዶሚኒየም ሌቦች እና የዕርዳታ ማስተባበሪያ አመራር መያዝ ገቢ የሚያስገኙ የዜና ርዕሶች አይደሉም። ሥርዓት ለማፍረስ የሚጠቅሙ የዜና ርዕሶችም አይደሉም። የዩትዩብ ተመልካች የሚስቡ አይደሉም። መንጋውን ለመመገብ የሚጠቅሙ ምግቦች አይደሉም። ተጨፈጨፈ፣ ተገደለ፣ ተሰደደ፣ … የሚሉት ናቸው ገቢ የሚያስገኙ የዜና ዘገባዎች። ይህንን የሚያውቁት ሸቃጮች ደግሞ መዘገብ ያለበትን ሳይሆን ኪሳቸውን የሚያደልብላቸውን እና መንጋውን እንደፈለጉ የሚነዱበትን ነው ቀን ተሌት የሚያወሩት። ታላቁ መጽሐፍ እንደሚለው “በድን ወዳለበት በዚያ አሞሮች ይሰበሰባሉ”።

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

Exit mobile version