Site icon ETHIO12.COM

“ሕወሀት መቸም ቢሆን የአማራ ህዝብ ወዳጅ ሊሆን አይችልም !”

ህወሓትና የዐማራ ሕዝብ!

  1. ሕወሀትና የአማራ ህዝብ ትውውቅ

ከሰሞኑ በወያኔ ባለስልጣናት ዘንድ ወያኔ የአማራ ህዝብ ወዳጅ እንደሆነ፤ ከፀጥታ ኃይሎቹ ጋርም መዋጋት እንደማይፈልግ፤ በአጠቃላይ ከአማራ ህዝብ ጋር ጠብ ውስጥ መግባት እንደማይፈልግ የሚያሳይ አዲስ ፖለቲካ ጀምረዋል፡፡ አጀንዳው በተጠና መልኩ የተጀመረ እንደሆነ ልብ ማለት ይገባል፡፡ ከሰሞንኛው የወያኔ አዲስ ፖለቲካ መገንዘብ እንደሚቻለው፤ ወያኔ የዚህ አጀንዳ ደጋፊዎችን ከአማራዎች ለማግኘት ከፍተኛ ጥረት እንደሚያደርግና እያደረገ መሆኑን ነው፡፡ በዚህ አጀንዳ ዙሪያ ያለኝን ምልከታ እንደሚከተለው አቅርቢያለሁ፡፡

የዐማራ ሕዝብና ህወሓት፣ ከ1981 ዓ.ም. በፊት ይሄን ያህል የጠነከረ ትውውቅ ነበራቸው ብሎ መናገር አይቻልም፡፡ የዐማራ ሕዝብ በሩቁ ትግራይ ውስጥ የደርግን አገዛዝ የሚቃወሙ አማጺያን (ወንበዴዎች፣ ገንጣይ አስገንጣዮች) አሉ እየተባለ ሲታወጅ ከመስማት ውጭ የዐማራ ሕዝብ ስለ ህወሓት ምንነትና ዓላማ ያን ያህል ዕውቀት አልነበረውም፡፡ ይህ ማለት ግን አንዳንድ የብሔሩ ምሁራን እና ነባር የዐማራ ብሔር የኢህዴን ታጋዮች ስለህወሓት ባሕርይና የዐማራን ሕዝብ ህወሓት እንዴት እንደሚመለከተው የሚያውቁ አልነበሩም ማለት አይደለም፡፡

ህወሓትና የዐማራ ሕዝብ በተወሰነም ቢሆን መተዋወቅ የጀመሩት መጀመሪያ ላይ ከ1972 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ ወልቃይት በገቡበት ወቅት ነው፡፡ ሰፋ ባለ መልኩ የዐማራ ሕዝበ የህወሓትን ዓላማና መሠረታዊ ባህርይ ማወቅ የቻለው ግን ወልቃይትን፤ ጸገዴን፤ጠለምትና ራያን በኃይል ወደ ትግራይ ክልል ካስገባበት ከ1984 ጀምሮ ነው፡፡ በርግጥ ህወሓት መጀመሪያ ላይ በ1972 ዓ.ም. ወልቃይትን በኃይል ከተቆጣጠረ በኋላ ቀስ በቀስ የጠለምትን፣ የጠገዴን፣ እንዲሁም የአርማጭሆን በረሃማ አካባቢዎች በመቆጣጠር ማስተዳደር ችሎ ነበር፡፡

ህወሓት፣ ወደ ጠገዴና አርማጭሆ ወረዳዎች የገባው፣ ልክ እንደወልቃይት በጦርነት ሳይሆን፣ ሕዝቡ ወኪሎቹን ልኮ በፍላጎቱ ነበር፡፡ የእነዚህ አካባቢ የዐማራ ሕዝብ፣ ህወሓትን በፍላጎት ጭምር ተቀብሎ አብሮ የታገለው ደርግን ለመጣል እንጂ፣ ዘሩን ቀይሮ ትግሬ ለመሆን አልነበረም፡፡ ሌላው ህወሓትና የዐማራ ሕዝብ በተወሰነም ቢሆን መተዋወቅ የጀመሩት፣ በ1973 ዓ.ም. የኢህዴንን መመሥረት ተከትሎ በተካሄደ የተቀናጀ እንቅስቃሴ ነበር፡፡ ኢህዴን ከተመሠረተ በኋላ የትጥቅ ትግሉን በዋናነት በጎንደርና ወሎ ክ/ሀገሮች አንዳንድ አካባቢዎች ማስፋፋት ሲጀምር፣ ህወሓትም ኢህዴንን ለማገዝ በሚል ሽፋን አድማሱን አስፍቶ ይንቀሳቀስ ስለነበር ነው፡፡ በነዚህ አካባቢዎች ትውውቁ የተጀመረው በኢህዴን አጋፋሪነት መሆኑ ይታወቃል፡፡

ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ኢህዴንን ተጠቅሞ፣ህወሓት ወደ ዐማራ ሕዝብ መሬቶች በስፋት እንዲገባ መንገዱን ጠረገለት፡፡ ከዚህ በኋላ በተለይም በሁለቱ ክ/ሀገሮች (ጎንደርና ወሎ) ህወሓትና የዐማራ ሕዝብ ከድሮው በተሻለ ሁኔታ መተዋወቅ ቻሉ፡፡ ስለ እውነት በዚያን ወቅት በህወሓት ታጋዮች ብዙም የሚከፋ ሰው አልነበረም፤ መጨረሻው “ጅብ እስኪይዝ ያነክሳል” ሆነ እንጂ፡፡ በዚያን ወቅት የህወሓት ታጋዮች ያን ያህል ስግብግብነትም አይታይባቸውም ነበር፡፡ ብቻ እኔ እስከማስተውሰው ድርስ የህወሓት ታጋዮች አንጻራዊነት ተቀባይነት ነበራቸው፡፡ በሂደት ህወሓት ኢህዴንን የሚደግፍ ኃይል ያስፈልጋል በሚል፣ ቁጥሩ በርከት ያለ የሠራዊትና የፖለቲካ ሠራተኞችን በስፋት በዐማራ መሬት ላይ የማሰማራት ዕድሉን አገኘ፡፡

በዚህም መሠረት በዋነኛነት ከ1976-1984 ዓ.ም. ህወሓት በሁሉም የዐማራ መሬት ላይ እንደልቡ ነገሰ፤ በጸጥታው መዋቅርም ሆነ በአስተዳደር ሥራው ረዘም ላሉ ዓመታት ህወሓቶች ከኢህዴን ባልተናነሰ ሁኔታ በዐማራ ሕዝብ የውስጥ ሁኔታዎች ላይ ወሳኝ ሁነው መታየት ጀመሩ፡፡ ይሁን እንጂ የህወሓት ባሕርይ በተለይም ደርግ ከተደመሰሰ በኋላ የዐማራን ሕዝብ ግራ እያጋባ መጣ፡፡ የጎንደርና የወሎን የዐማራ መሬቶች በትግሉ ወቅት ያገኘውን ቀድሞ አካባቢዎቹን የማወቅና የመቆጣጠር አጋጣሚ ተጠቅሞ ወደ ትግራይ ጠቀለላቸው፡፡ አንዳንድ ንብረቶችንም ከዐማራ መሬት እየነቀለ ወደ ትግራይ ሲያጓጉዝ ሕዝቡ ተመለከተ፣ እንዲሁም ለትግራይ ብሔር አባላት ያጋደለ አያያዝ ተመለከተ፡፡ ብቻ ህወሓት ለረዥም ዓመታት፣ በዐማራ መሬት ውስጥ ያለማንም ኃይ ባይነት የአሻውን የሚያደርግበት ሁኔታ ተፈጠረ፡፡ የዐማራ ሕዝብም ግራ ተጋባ፤ ይህን የህወሓት ያልተገባ ፍላጎትና እንቅስቃሴ የሚያስቆምለትና ከህወሓት ጥቃት የሚጠብቀው ኃይልም እንደሌለው እየተገነዘበ መጣ፡፡

  1. እውን ህወሓት የዐማራ ሕዝብ ወዳጅ ነው? ሊሆንስ ይችላል?

የወልቃይትን ሕዝብ የዐማራነት እውቅና ይረጋገጥልን ጥያቄ ተከትሎ የተከሰተውን በዐማራና የትግራይ ሕዝቦች ውዝግብ አስመልከቶ አንዳንድ የትግራይ ባለሥልጣናት የዐማራና የትግራይ ሕዝቦች የቆየ ወዳጅነት እንዳላቸው ሲሰብኩ ነበር፡፡ ከነዚህ መካከል በወቅቱ የትግራይ ክልል ፕሬዝዳንት የነበሩት አቶ አባይ ወልዱ ዋነኛው ሰው ነበሩ፡፡ አቶ አባይ፣ በ2008 ዓ.ም. ህወሓት ወልቃይት ላይ በጠራው ፀረ- የወልቃይት አስመላሽ ኮሚቴ እንቅስቃሴ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ንግግር ሲያደርጉ እንዲህ አሉ፤ “እኚህ ሰዎች (የወልቃይት ዐማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴዎችን መሆኑ ነው) የትግራይን ሕዝብ ወዳጅ ከሆነው የዐማራ ሕዝብ ጋር ሊያጋጩን ነውና ልናስቆማቸው ይገባል፡፡”

እንግዲህ ልብ በሉ፣ በህወሓት መሪዎች እምነት የትግራይ ሕዝብና ህወሓት አንድና ያው ናቸው፡፡ እኔም ይሄንን የአቶ አባይ ወልዱ ንግግር በሰማሁ ጊዜ፣ እራሴን በራሴ እንዲህ ስል ጠየኩ፡፡ እውን ህወሓት የዐማራ ሕዝብ ወዳጅ ነው? ሊሆንስ ይችላል? ከሆነስ ወዳጅ ናቸው ሊያስብሉ የሚያስችሉ ምን ዓይነት ጽሑፎች ወይም ድርጊቶች ይኖሩ ይሆን? ብዬ ማምሰልሰል ጀመርኩ፡፡ ባገኘሁት ምላሽ ግን አይደለም፤ ህወሓት የትግራይ ብሔርተኞችና ሊህቃን ሳይቀር ከጥንት ጀምሮ ዐማራን እንደወዳጅ ከመመልከት ይልቅ፣ በጥርጣሬና በጥላቻ የመመልከት ዝንባሌና ታሪክ እንዳላቸው፣ በራሱ በህወሓትና ደጋፊዎቹ የተጻፉ አንዳንድ ጽሑፎችን በማየት አረጋገጥሁ፡፡ በመሬት ለይ የነበሩና አሁንም ድረስ ያሉ እውነታዎችን በመሸፋፈን የህወሓትንና ዐማራን ሕዝብ ወዳጅነትና አብሮነት መፍጠር አይቻልም፡፡
በአሁኑ ወቅት፣ቢያንስ በነባራዊው ሐቅ የዐማራ ሕዝብና የህወሓትን ግንኙነት በወዳጅነትና በመፈቃቀር የተመሠረተ ነው ብሎ ለመናገር የሚደፍር ሰው የለም፡፡ ጥያቄው ግን ይህ አለመተማመንና መጠራጠር፣ አሁን የተከሰተ ነው ወይስ ታሪካዊ አመጣጥም አለው? የሚለው ነው፡፡

መረጃዎች እንደሚያሳዩት ከሆነ፣ በአንድ በኩል በህወሓትና በትግራይ ሊህቃን፣ በሌላ በኩል ደግሞ በዐማራ ሕዝብ መካከል መጠራጠርና ጥላቻ የተከሰተው አሁን ብቻ ሳይሆን፣ ረዘም ካሉ ጊዚያት ጀምሮ ሲከሰት የኖረ እውነታ ነው፡፡ ለዚህም እውነታ ማሳያዎቹ፡-

 ስለ ዐማራ ጥላቻ በህወሓት (ተሓሕት) ማኒፌስቶ
 ቢያንስ ከ40 ዓመታት ወዲህ ያለው የትግራይ ሕዝብ በጸረ-ዐማራ አመለካከት ተገንብቶ ነው ያደገው፡፡ ህወሓት ለትግራይ ወጣት ስለ ዐማራ በዳይነት፣ የትግራይ ሕዝብ ችግሮች ዋነኛው ምንጭ ዐማራ ነው ብሎታል፡፡ በዚህ ሳይታጠር በማንፌስቶው ያስቀመጠውን ዓላማ ለማሳካት፣ አደገኛና ፀረ-ዐማራ የሆኑ ዘፈኖቹን አዘጋጅቶ በማስደመጥ፣ የትግራይ ወጣት በዐማራ ሕዝብ ላይ ጥላቻውን እንዲያጠናክር አድርጓል፡፡
 አብዛኛዎቹ የትግራይ ብሔርተኞች (ልሂቃን) በዐማራ ላይ ያላቸው ጥላቻ ስር ሰደደ መሆኑ፡፡
 ከአማራ ህዝብ ጋር የምነወራርደው ሂሳብ አለ ( ህወሀት አመራሮች ውሳኔ)፡፡

ታድያ እንዲህ እሰራና እየተናገረ እንዲሁም ሃሳቡን እየተገበረ የመጣው ወያኔና አብዛኛው የተግራይ ኤሊት እንዴት ባለ ሂሳብ ነው የአማራ ህዝብ ወዳጅ ሊሆኑ የሚችሉት ?

  1. ህወሓት እና ጎንደር !

ህወሓትና ጎንደር ሲበዛ አይተማመኑም፤ የጎንደር ሕዝብ ህወሓትን ክፉኛ ይጠላል፡፡ ህወሓትም ጎንደርን በእጅጉ እና በተለየ ሁኔታ ይጠረጥራል፤ይጠላል፡፡ ለዚህም ነው የጎንደር ሕዝብ ህወሓትን ከጅመሩ ጀምሮ የታገለው፡፡ ለዚህ ጥሩ ማሳያው የከፋኝ እና በጎንደር በጌ ምደር ተቀጣጥሎ የነበረው የሽምቅ እንቅስቃሴ ነበር፡፡ ህወሓትም ጎንደርን መበቀልና ማሳደድ የጀመረው ገና በጥዋቱ ነበር፡፡ በዚህ በኩል ተጠቃሽ ከሆኑት የህወሓት ሥራዎች መካከል፣ የጎንደርን ለም መሬቶች መቀማት፣ በደም ካሳነት ከኢጣሊያን ሀገር የተገኘውን ትልቅ ጀኔሬተር ነቅሎ ወደ ትግራይ ማጓጓዙ ወዘተ. ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ጎንደር ላይ ገና በጥዋቱ የተጀመረው የህወሓት በትር፣ እየቀነሰ ከመምጣት ይልቅ፣ ለ27 ዓመታት በልዩ ልዩ ስልቶች እየታገዘ ተጠናክሮ ቀጠለ፡፡ እነዚህ ሁሉ ግፎች ተደማምረው መላ ዐማራ በተለይም ጎንደር የህወሓትን በደል ለመሸከም ከማይችሉበት ደረጃ ደረሱ፡፡ ስለሆነም ዐማራ ከዚህ የመከራ ዘመን ለመላቀቅ አብዮት ማካሄድ ነበራበት፣ ይህን አብዮትም የጎንደር ዐማራ እንዲ ጀምረው ታሪክ ፈቀደለት፤ የጎንደር ዐማራ የዐማራን አብዮት ሐምሌ 5/2008 ዓ.ም. አቀጣጠለው፡፡

አንድ ቀን ኮምፒውተሬን ሥነካካ አንድ መጣጥፍ በቪዲዮ ድምጽ ተደግፎ ሲተረክ ሰማሁ፡፡ የንግግሩ ርዕስ ሳበኝና ማዳመጥና ማንበብ ጀመርኩ፡፡ መጣጥፉ እንዲህ ይላል፤ “የትግራይ ጎሰኞችና ዘረኞች ዐማራን በጣም ይጠላሉ፤ በተለይ ጎንደሬዎችን፣ እንደ ትግራይ ጠላት ነው የሚያስቧቸው” (“Tribalist and Racist Tigrians hate Amhara so much & specially Gonderes and they consider them as Tigray enemies” )፡፡

የዚህን መጣጥፍ ርዕስ አይቶ ማንበብ በራሱ ከባድ ቢሆንም፣ ነገሩን የበለጠ ያከበደብኝ ግን በቪዲዮው የሚሰማው ድምጽ ነበር፡፡ ድምጹ አዲስ አልሆነብኝምና ማነው ስል ከቆየሁ በኋላ አባይ ፀሐዬ (ነብስ ይማር) መሆኑን በእርግጠኝነት ገመትኩ፡፡ እውነቴን ነው የምላችሁ ያንን ንግግር ያደረገው አባይ መሆኑን በከፍተኛ ግምት ሳረጋግጥ በጣም ደነገጥኩ፣ ግራም ተጋባሁ፡፡ ስብሰባው የት ቦታ እንደተካሄደ ማወቅ ባልችልም፣ በወቅቱ አባይ ፀሐዬ ሕዝብ ሰብስቦ እያወያየ እንደነበር ግን ንግግሩ ያስታውቃል፡፡ የንግግሩ ጭብጥም አብዛኛው ዐማራ በተለይም ጎንደሬዎች ህወሓትና የትግራይ ሕዝብ እንዲጠላ እየሠሩ ነው የሚል ነበር፡፡ አባይ ፀሐዬ ተሰብሳቢውን እንዲህ ሲል ይጠይቃል፡- “ጎንደሬዎች
ይሄን የሚያደርጉት ለምን ይመስላችኋል? ሲል ይጠይቃል፡፡ ምላሹን እራሱ እንዲህ ሲል ይሰጣል፡-

አብዛኛው ጎንደሬ የነመላኩ ተፈራ ደጋፊና ተከታይ የነበረና የደርግ ኢሰፓን ሥርዓት ናፋቂ ነው፤ የትግራይ ሕዝብና ህወሓት ደግሞ ይሄንን ጉዳይ ስላከሸፉበት በመበሳጨት የሚወስዱት እርምጃ ነው” ይላል፡፡ በመቀጠልም “እኚህ ጎንደሬዎች ከደርግ ጋር ሁነው ሕዝብ የጨፈጨፉ ናቸው” ሲል ጎንደርን ደጋግሞ ሲወነጅላት ይደመጣል፡፡

አቶ አባይ በመጨረሻም ለተሰብሳቢው ሕዝብ እንዲህ ሲል ይደመጣል፣ “ለእነዚህ ጎንደሬዎች ይሉኝታ አያስፈልግም፤ ልክ ልካቸውን እና እንቅጩን እንንገራቸው ይላል ፡፡ በርግጥ ህወሓት ከጅምሩ ጀምሮ ለዐማራ ሕዝብ በጎ አሳቢ እንዳልሆነና የዚህን ሕዝብ ጥንካሬና አንድነት ማየት የማይሻ ድረጅት እንደሆነ በተደጋጋሚ ጊዜ ነግሮናል ፡፡ ይሄን የቪዲዮ ድምጽ ከመስማቴ በፊትም፣ አቶ አባይ ፀሐዬ በጎንደር ሕዝብ ላይ የሠራውን በደል አውቅ ስለነበር (የደለሎን መሬት ለሱዳን መስጠቱ)፣ ሰውዬው ፀረ-ጎንደር እንቅስቃሴ ውስጥ እንደነበረ ተግንዝቤው ነበር፡፡

እንግዲህ ጉዳዩን ለማረጋገጥ የሚፈልግ ማንኛውም ሰው ቀጥሎ የጠቀስኩትን አድራሻ በመጎብኘት ማረጋገጥ ይችላል፡፡ ምን አልባትም ብዙዎቻችሁ መረጃው ካሁን በፊት ኑሯችሁም ከኔ በፊት አዳምጣችሁት ሊሆን ይችላል፡፡ https://www. youtube. com/watch? v= 6j86mWFJO-0).፡፡ ጉዳዩ ግን አቶ አባይ ፀሐዬ ካሁን በኋላ ለምን ያህል ጊዜ በዚች ምድር ላይ ይኖሩ ይሆን? እሱ በተፈጥሮአዊ ሁኔታም ቢሆን ይችን ምድር ጥሏት ይሄዳል፡፡ የተናገራት ንግግር ግን በዐማራና በትግራይ ሕዝቦች መካከል ዘላቂ ጥላቻን ትቶ እንደሚያልፍ የሚያጠራጠር ጉዳይ አይደለም፡፡ የጎንደር ዐማራም ይሄንን መረጃ በስፋት ማግኘቱ አይቀርም፣ ያን ጊዜ ደግሞ በዚች ምድር ሌላ ታሪክ እናይ ይሆናል፡፡ (ወቅቱን በተመለከተ፤ ጽሁፉ የተወሰደው ዳገት ያበረታው የአማራው ፍኖት፤2010 ከተሰኘው መጽሀፌ ስለሆነ በዚሁ አግባብ ተረዱልኝ) ፡፡

  1. ታድያ ዛሬ ምን አዲስ ነገር ተገኘ?

እንግዲህ ከላይ ለማንሳት እንደሞከርኩት፤ ህወሀትና የአማራ ህዝብ እንዴትና መቸ ትውውቅ እንደጀመሩ፤ በሂደቱ የነበራቸው ግንኙነት እጅግ ያልሰመረ ሁኖ እንደከረመ፤ አብዛኛው የአማራ ህዝብ ለሕወሀት፤ሕወሀትም ለአብዛኛው አማራ በጎ አመለካከት ኖሯቸው እንደማያውቅም ተመላክቷል፡፡ ይልቁንስ ሕህወሀት አማራን በጠላትነት ፈርጆ ለ27 ዐመታ አሳሩን እዳበለው፤አማራ በሕወሀት አገዛዝ ለሁለንተናዊ በደል እንደተጋለጠ እሙን ነው፡፡

አስገራሚው ነገር ሕወሀት በአማራ ህዝብ ላይ ላለፉት 40/50 አመታት የፈጸመው ታሪካዊ ስህተቱና በደሉ ሳይረሳ፤ ላፉት ሁለት አመታት ደግሞ በባሰ መልኩ ለ3ኛ ጊዜ ተደጋገሚ ወረራዎችን በማካሄድ አማራን ለከፋ ሁለንተናዊ በደል መዳረጉ ነው፡፡ እነዚህ ተደራራቢ ግፎቹ ሳይረሱና ዛሬም ተባብሰው እየቀጠሉ ባሉበት ሁኔታ ነው ዛሬ ላይ ወያኔ ከመሬት ብድግ ብሎ ‘‘የአማራ ህዝብ ወዳጅ ሁኛለሁ፤ጠላቴ እና የምፈልገው የብልጽግና መንግስትን ነው” በማለት ሊቀልድበን እየሞከረ ያለው፡፡ ነገሩ ገራሚ ነው፡፡ ሕወሀት ቢያንስ ላፉት 40/50 አመታት በአማራ ህዝብ ላይ ላደረሰው ሁለንተናዊ በደል ይፋዊ ይቅርታ ሳይጠይቅና ተገቢውን ካሳ ሳይከፍል እንዴት የአማራ ህዝብ ወዳጀ ነው ሊል ሞከረ?፤ ሞራሉንስ እንዴት አገኘው?፤ ምን ያክልስ ልባችንን ቢሰልለው ነው? በኛዎቹ …..ምን ያክል ቢተማን ነው?

ለሁሉም ነገሩ ሁሉ ”እኛም አውቀናል ጉድጓድ ምሰናል” እንዳለችው አይጥ ነው፡፡
ለሕወሀት አደናጋሪ ፕሮፓጋንዳ ሰለባ ላለመሆን እንጠንቀቅ፤ የሆነ ካለም ይቅርብህ ወንድማዊ ምክሬ ነው፡፡
ሕወሀት መቸም ቢሆን የአማራ ህዝብ ወዳጅ ሊሆን አይችልም !
ድል ለመከላከያ ሀይላችንና በሱ ስር ለሚመሩ ሁሉም ፀትታ ሀይሎቻን.!!!

Opinion chuchu Alebachew

Exit mobile version