ETHIO12.COM

የአራጣ መስጅድ መስራቹ ሸህ ቀሪብና ቤተሰቦቻቸውን በአራጣ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ

አራጣ በደቡብ ጎንደር አስተዳደር ዞን ስማዳ ወረዳ የሚገኝ የገጠር መንደር ነው። በተራራ ሰንሰለት በተከበበው በዚህ መንደር ሙስሊምና ክርስቲያኖች ለረጅም ዓመታት በአንድነትና በፍቅር ኑረውበታል።

ፍቅርና አንድነታቸውን ለማሳየትም የአራጣ መስጅድ እና የአራጣ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተመሳሳይ ዲዛይን በአንድ ባለሙያ ከዛሬ 500 ዓመታት በፊት እንዲሰሩ አድርገዋል። ይሄን ለማመስከርም በአካባቢው የሚከበሩት የአራጣ መስጅድ መስራቹ ሸህ ቀሪብ አህመድ እና ቤተሰቦቻቸውን የሚያሳይ ስዕል በአራጣ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተስሎ ይገኛል።

አስገራሚው ነገር ደግሞ ወዲህ ነው። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የስዕል አሳሳል ትውፊት ተጠራጣሪ፣ ከሀዲ፣ ሀጢያተኛ፣ ኢአማኒ ወይም የሀይማኖቱ ተከታይ ያልሆነ ሰው የሚሳልበት ጥበብ አለ። ይሄም በጎን ወይም አንድ ዓይንን ብቻ በማሳየት ነው።

ሙስሊም ቢሆኑም ሸህ ቀሪብ አህመድ እና ተከታዮቻቸው ግን በዚህ ዓይነት መንገድ አልተሳሉም። የተሳሉት ቤተ ክርስቲያን ፃድቃንን፣ ሰማዕትን ወይም የሀይማኖቱ ተከታይ ነገሥታትን በምትስልበት ጥበብ ሁለት ዓይኖቻቸው በጉልህ እንዲታዩ በማድረግ ነው። ይሄም በአራጣ የነበረውን ከፍ ያለ መከባበር እና አንዱ ሀይማኖት ለሌላው ሀይማኖት ተከታይ ይሰጠው የነበረውን እውቅና ያሳያል።

ክብር በመከባበር እና በመፋቀር ዘመናቸውን ላሳመሩ ቀደምት ወላጆቻችን ይሁን!
Via Vist Amhara

Exit mobile version