ETHIO12.COM

በሺዎች የሚቆጠሩ የት ህነግ አመራሮችና ተዋጊዎች የተቀበሩበት የጅምላ መቃብር ተገኘ

“አሸባሪው ህወሃት ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም በመከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝ አባላት ላይ አሰቃቂ የክህደት ጥቃት በመፈጸም በኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ላይ ከፍተኛ አደጋ ደቅኖ መቆየቱ ይታወሳል” ይላል የ ኦቢኤን ዘገባ

የሽብር ቡድኑ በወቅቱ በርካታ የሰሜን እዝ አባላትን ጨፍጭፏል፤ በርካቶችን ደግሞ አካላዊና ስነ-ልቦናዊ ጉዳት እንዲደርስባቸው አድርጓል፡፡ መንግስት ጥቃቱን ተከትሎ በወሰደው ህግ የማስከበርና የህልውና ዘመቻ በኢትዮጵያ ላይ የተደቀነውን የህልውና አደጋ መቀልበስ የቻለ ሲሆን፤ የተናጥል የተኩስ አቁም በማወጅም ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት በተግባር አሳይቷል፡፡

ነገር ግን አሸባሪው ህወሃት ህጻናትን አስገድዶ በጦርነት በማሰለፍ ጭምር በአማራና አፋር ክልልች ተደጋጋሚ ወረራ በመፈጸም የትግራይ ህዝብን በጦርነት አዙሪት ውስጥ ልጆቹን እንዲያጣ ሲያደርግ ቆይቷል፤ አሁንም ከዚህ አኩይ ተግባሩ አልተመለሰም፡፡

በመከላከያ ሰራዊት መስዋእትነት ከህወሃት እየተላቀቁ በሚገኙት አካባቢዎች የአሸባሪው ህወሃት ድብቅ ገመና መጋለጡን ቀጥሏል። የሽብር ቡድኑ ቁንጮ አመራሮች አስገድደው በጦርነት ላሰለፏቸው ታጣቂዎች እንኳ ምንም አይነት ርህራሄ እንደሌላቸው በጨርጨር የተገኘው ጅምላ መቃብር ለዚህ ማሳያ ነው፡፡

1 / 10

ከጨርጨር ከተማ በስተምስራቅ በኩል በሺዎች የሚቆጠሩ የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎችና የጦር አመራሮች የጅምላ መቃብር ስፍራ የተገኘ ሲሆን፤ ይህም የሽብር ቡድኑ ቁንጮ አመራሮች በትግራይ ህዝብ ደም በስልጣን ለመቆየት የማይፈነቅሉት ድንጋይ እንደሌለ ያሳያል፡

የጅምላ መቃብር ስፍራው መለያ ኮድ የተሠጠው ሲሆን በአንዳንዱ መቃብር ከ3 እስከ 5 አስከሬን በጋራ ተቀብሮበታል። የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎቹን የቀበራቸው እንደ ኃላፊነታቸው እና ማዕረግ ደረጃቸው መሆኑ ደግሞ በመቃብሩ ላይ ባሉት ምልክቶች መረዳት ይቻላል።

ተዋጊ የሚባለውን ኃይል በአንድ መቃብር ውስጥ ከ3 አስከ 5 እስከሬን እንዲሁም ለብቻቸው ኮድ ተሠጥቷቸው የተገኙ የመቃብር ስፍራዎች ደግሞ የአመራሮች መሆኑ ታውቋል። ከዚህ በተጨማሪም የሞቱ የሽብር ቡድኑ ከፍተኛ አመራሮች በአንድ ዋሻ ውስጥ አስክሬናቸው በሬሳ ሳጥን ውስጥ ተቀምጦ ተገኝቷል።

በዋሻ ውስጥ በሬሳ ሳጥን የተገኙት አስከሬኖች በልዩ ሁኔታ የተቀመጡ በመሆኑ ውጊያውን ሲመሩ የነበሩ የሽብር ቡድኑ አመራሮች እንደነበሩ ለማወቅ ተችሏል።

በአጠቃላይ በጨርጨር የተገኘው የጅምላ መቃብር ስፍራ በሶስት የተከፈለ ሲሆን፤ የመጀመሪያው የቡድኑ ታጣቂዎች የተቀበሩበት ነው፡፡ ቀሪዎቹ ሁለቱ ደግሞ የሽብር ቡድኑ መካከለኛ አመራሮች እና ጦርነቱን ሲመሩ የነበሩ ከፍተኛ አመራሮች የተቀበሩበት ስፍራ ነው፡፡

Exit mobile version