Site icon ETHIO12.COM

ዐቃቤ ሕግ በእነ ሙሉ ሐጎስ ላይ አቅርቦት የነበረው ክስ በችሎት ተሰማ

በኢፌዲሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ዘርፍ የኢኮኖሚ ወንጀል ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ሕግ ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ ስማርት ሳምሰንግ ጋላክሲ ሞባይሎችን እና የሞባይል ቻርጀሮችን በህገ-ወጥ መንገድ ወደ አገር ውስጥ በማስገባት የኮንትሮባንድ ወንጀል ፈፅመዋል ባላቸው ሙሉ ሐጎስ እና ክብሮም ገብረ-ሚካኤል የመሰረተው ክስ በችሎት ተነቧል፡፡

ጉዳዩን የተመለከተው የፌደራሉ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 5ኛ ወንጀል ችሎት ተከሳሾች ቀርበው የተከሰሱበትን ክስ ካዳመጡ በኋላ የክስ መቃወሚያ ያቀረቡ ሲሆን ዐቃቤ ህግም በክስ መቃወሚያቸው ላይ መልስ ለመስጠት ለህዳር 26 ቀን 2015 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

ተከሳሾች ተገቢውን የጉምሩክ ሥነ-ሥርዓት ሳይፈፀምባቸው ወደ አገር ውስጥ የገቡ መሆናቸውን እያወቁ ወይም ማወቅ ሲገባቸው 1ኛ ተከሳሽ የዋጋ ግምታቸው 10 ሚሊዮን 847 ሺ ብር የሚያወጡ 715 ስማርት ሳምሰንግ ጋላክሲ ሞባይሎች እና 815 የሞባይል ቻርጀሮችን ከሞያሌ አጓጉዞ ወደ አዲስ አበባ ከተማ በማስገባት በ2ኛ ተከሳሽ የመኖሪያ ቤት ውስጥ በተደረገ ብርበራ በቤታቸው ውስጥ እና ግቢ ላይ ቆሞ በነበረ መኪና ንብረቶቹን አስቀምጠው የተያዙ በመሆኑ በፈፀሙት በህገ-ወጥ መንገድ ወደ አገር ውስጥ የገባን ዕቃ ማጓጓዝና ይዞ መገኘት የኮንትሮባንድ ወንጀል ዐቃቤ ህግ ክስ እንደመሰረተባቸው ከዚህ ቀደም ባጋራነው መረጃ መግለጻችን ይታወሳል፡፡

የዚህን መዝገብ የክርክር ሂደት ተከታትለን መረጃ የምናጋራችሁ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

Ministry of justice

Exit mobile version