Site icon ETHIO12.COM

በምስል የተደገፈ ጥቆማ ለEBC የደረሰ በማስመሰል ጉቦ የተቀበሉ ተቀጡ

በምስል የተደገፈ ጥቆማ ለEBC የደረሰ በማስመሰል ከውሀ አምራች ባለቤት 500 ሺ ብር ጉቦ የተቀበሉት በላቸው ጀቤሳ እና አለማየሁ ቂጥሶ በእስራት ተቀጡ

የኢትዮጲያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የኦሮምኛ ዝግጅት ክፍል ሀላፊ በላቸው ጀቤሳ እና 2ኛ ተከሳሽ አለማየሁ ቂጥሶ የሙስና ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣውን አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀጽ 10 (1) እና 2 ን ተላልፈው በፈጸሙት የሙስና ወንጀል በኢ.ፌ.ድ.ሪ ፍትህ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ዘርፍ የሙስና ወንጀል ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ህግ መጋቢት 9 ቀን 2014 ዓ/ም በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የልደታ ምድብ 4ተኛ የሙስና ወንጀል ችሎት ክስ መስርቶባቸው ነበር፡፡

የዐቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስታው ተከሳሾች የሸገር ውሀ ባለቤት ዶ/ር ሀሰን መሀመድ ጋር 2ኛ ተከሳሽ ስልክ በመደወል በአዳማ ከተማ ከአንድ ሱቅ የገዛው የታሸገየሸገር ውሀ ሶፍት መሰል ባዕድ ነገር ቆሻሻ እንዳገኘበት ለኢትዮጵያ ብሮድካስት ኮርፖሬሽ ጥቆማ መስጠቱን ገልጾ በቴሌቪዥን ጣቢያው የኦሮምኛ ዝግጅት ክፍል ኃላፊ የሆኑትን 1ኛ ተከሳሽን አናግሩት በማለት የኃላፊውን ስልክ ቁጥር ለባለሀብቱ ይሰጠዋል፡፡ባለሀባቱም በተባለው ስልክ በመደወል 1ኛ ተከሳሽን በአካል ሲያገኘው በምስል የተደገፈ ጥቆማው ለክፍሉ እንደደረሰው ለባለሀብቱ በመግለጽ ጉዳዩ በሚዲያው እንዳይተላለፍ ከፈለጋችሁ 500 ሺ ብር ጉቦ እንዲከፍሉ በመደራደር በሌላ ቀን ተከሳሾች ከባለሀብቱ እጅ 100 ሺህ ብር በጥሬ ገንዘብ እንዲሁም ቀሪ 400 ሺህ ብር ደግሞ በ3 ቼኮች ተቀብለው 1ኛ ተከሳሽ መኪና ውስጥ እንዳሉ ባለሃብቱ አስቀድሞ ለፖሊስ በሰጠው ጥቆማ መሰረት የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን አባላት ክትትል ሲያደርጉ ቆይተው እጅ ከፍንጅ በቁጥጥር ስር በማዋላቸው ዐቃቤ ህግ ክስ መስርቶ በሰው እና በሰነድ ማስረጃዎች የተባለውን ድርጊት ተከሳሾች መፈጸማቸውን በበቂ ሁኔታ አረጋግጧል።

በዚሁም መሰረት ፍርድ ቤቱ ሐምሌ 4 ቀን 2014 ዓ/ም በዋለው ችሎት ዐቃቤ ህግ ባቀረበባቸው ከባድ የጉቦ መቀበል የሙስና ወንጀል ተከሳሾችች እንዲከላከሉ ብይን በሰጠው መሰረት ተከሳሾች የዐቃቤ ህግ ክስ እና ማስረጃ ለማስተባበል የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍርድ ቤቱ አቅርበው ተከራክረዋል።

ክርክሩን የመራው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የልደታ ምድብ 4ተኛ የሙስና ወንጀል ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር ተመልክቶ በሰጠው የጥፋተኝነት ፍርድ ምንም እንኳን ዐቃቤ ህግ ተከሳሾች 500 ሺ ብር ጉቦ ተቀብለዋል በማለት በከባድ የሙስና ወንጀል አንቀጽ የከሰሰ ቢሆንም ተከሳሾቹ በቁጥጥር ስር ሲውሉ የ400 ሺህ ብር ቼክ መቀበላቸውን በሚመለከት ቼኩ ላይ የተጻፈው የክፍያ ጊዜ ያለፈበት እና ለክፍያ ቢቀርብም ጥቅም ላይ የማይውል ነው በማለት ተከሳሾቹ በጉቦ ከተቀበሉት የ 500 ሺ ብር ውስጥ ያገኙት ጥቅም በጥሬ ገንዘብ የተቀበሉት 100 ሺህ ብር ብቻ ነው በማለት ዐቃቤ ህግ ክስ ከመሰረተበት የሙስና ወንጀል አዋጅ ቁጥር 881/2008 አንቀጽ 10 ንኡስ አንቀጽ 1 እና 2 ውስጥ በ ንኡስ 1 ስር ብቻ ጥፋተኛ በማለት ተከሳሾች እያንዳንዳቸው በ 1 ዓመት ከ 6 ወር ጽኑ እስራት እንዲቀጡ በመወሰን 2ኛ ተከሳሽ የተጣለበት የእስራት ቅጣት በፈተና ጊዜ እንዲገደብለት ወስኗል፡፡

ዐቃቤ ህግ በውሳኔው ላይ ይግባኝ የሚጠይቅ ሲሆን የክርክር ሂደቱን ተከታተልን መረጃ የምናደርሳችሁ ይሆናል፡፡

EBC

Exit mobile version