ETHIO12.COM

የብረት ሌባ “ባለሃብቶች” – ነዳጅ ስር የሚርመጠመጡ ባለስልጣናት

ሰሞኑንን ብቻ ይፋ በሆነ መረጃ ከመቶ ሚሊዮን ብር በላይ “ባለሃብት” ተብዬዎች ኢትዮጵያን በተራ ሌብነት፣ በወራዳ ተግባር፣ ይቅርታ በማያሰጥ ጥፋት አልበዋታል። ይህን ያስታወቀው ደግሞ ደሃው ገበሬ ቆፍሮ ባመረተው ምርት በተገኘ ሃብት የገዛውን ንብረት የተዘርፈው የመግስት ተቋም ነው። እናም ማጅራት መቺነቱ ማስተባበያ የማይቀርበበት ወራዳ፣ ባለፉት ሰላሳ ዓመታት የተፈጠሩ ሞራል አልባዎች የፈጸሙትና ያስፈጸሙት ዝርፊያ ነው።

ዝርፊያው የሚከናወነው ከፍተኛ በሆኑ የኤሌክትሪ ሃይል ተሸካሚ ማማዎች ላይ ነው። ዝርፊያውን የሚፈጽሙት የህዝብን ብርሃን የሚያወድሙ ሞራል አልባ የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ፍልፍሎች ናቸው። ዝርፊያውን ስፖንሰር የሚያደርጉት ” ግብር በአግባቡ ይከፍላሉ” ተብለው በአደባባይ የሚሸለሙ ወራዳ ባለህት ተብዬዎች ናቸው። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ባለስልጣን ዳር ዳር እያለ ዘራፊዎቹ ብረቱን ለበረት አቅላጮች እንደሚያቀርቡ ጠቁሟል። ከዚያ በላይ ግን አልሄደም።

ጎበዝ ስንት ብረት አቅላጭ ፋብሪካ አለንና፣ ምን ያህል ቁጥራቸው ለክትትል ናዳጋች እስኪሆን ሚስጥር መሆን ችለው ይሆን እነዚህን ሞራል አልባ የሌባ ተቀባይና ስፖንሰር አድራጊዎችን መያዝ ያማይቻለው? መልሱ አንድ ነው። አገሪቱን የወረረው ሌባ፣ ሳይማር መለስ ዜናዊ በስለፍ ዲግሪ ያሸከማቸው፣ ዶክተር ባደግ የሚባል የሰርተፊኬት ቸርቻሪ ያደላቸው መሃይማን፣ ዝርፊያውን የብሄር ትግል፣ የዘረኝነት ታርጋ እየለጠፈ ሲያጋድል የሚውል ካድሬ በፈላበት አገር ምን ይጠበቃል የሚለው ነው።

ቢያንስ ቢያንስ መሬቱን ያደላቸው የዛሬው የማዕድን ሚኒስትር ከነሚስቶቻቸው ስም የሚያውቃቸው የቀድሞው የሶቪየት ሰላይና ጋዜጠኛ ” ላሽቀው የተሰሩ፣ ሞራል አላባዎች” ሃብታሞች፣ የልቦናቸው መዛግና የመላሸቃቸው ማረጋገጫ የሚሆነውን ” የደሃውን ብርሃን ማዘርፍ” የተባለ ፕሮጀክት ያደረሰውን የጥፋት መጠን በአንድ አገ ብሄራዊ ሚዲያ መስማት ተስፋ የሚያስቆርጥ ነው። አንድ “ሰው” የተባለ ፍጡር እንዴት የወላጆቹን አይነ ብርሃን እያዘረፈ ሃብት ያከማቻል? ይህ ልቡና ላላቸው ህመም ነው። ዛሬ በአገራችን በልዩ የትርምስ አጀንዳ የተቀረጹ፣ የሌባ ጠባቂ የሆኑ፣ አንዳንዶቹም ስትራቴጂካል የወያኔ አንደበት የሆኑ ሚዲያዎች ፈሉና እንዲህ ያለው አስነዋሪ ማጅራት መቺነት ነገሰ።

ያልተነቀለው ሰንኮፍ “ትህነግ” – ዩሪ ቢስሜኖቭ እንዳለው፣ እኛም እንዳየነው…

ዩሪ ቢስሜኖቭ በቀደመችው ሶቪየት ህብረት ኬጂቢን ሲያገለግል የነበረ፣ በጋዜጠኛናት የሰራ ሰው ነው። አሱ አንደሚለው አንድን አገር አንበርክኮ ለመግዛት ትውልድን ማላሸቅ፣ ትውልዱን አላሽቆ አውነትን እንዳይቀበል ማድረግ፣ በተቋማት ውስጥ የላሸቁትን በመመደብ ማንኮታኮት መበተን፣ ኢኮኖሚውን ማናጋት፣ ቀውስ መፍጠር፣ በቀውስ ወስጥ ማህበራዊ እረፍት መንሳት፣ ይህ ሁሉ ከሆነ በሁዋላ ኖርማላይዜሽን ወይም አረጋጊ መስሎ ወደ ቤተመንግስት መሮጥ።

” በኤሌክትሪክ የብረት ማማዎች ላይ በተፈጸመ ስርቆት የ100 ሚሊዮን ብር ኪሳራ እንዳጋጠመው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታወቀ በ2014 ዓ.ም ብቻ ከኤሌክትሪክ የብረት ማማዎች ላይ በተሰረቀ 756 ቶን ብረት የ100 ሚሊዮን ብር ኪሳራ እንዳጋጠመው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታወቀ። በተቋሙ የምስራቅ ሪጅን ዳይሬክተር አቶ ጋሻው እንድሪያስ እንደገለጹት፥ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በሚያስተዳድራቸው የከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር ተሸካሚ የብረት ምሰሶዎች ላይ ተደጋጋሚ ስርቆት እየተፈፀመ ነው። በ2014 ዓ.ም ብቻ 24 የሚደርሱ ከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊያ የብረት ማማዎች ሙሉ ለሙሉ ተቆርጠው የወደቁ ሲሆን የብረትና የኮንዳክተር ዘረፋ እንደተፈጸመባቸው እና በቁጥር 30 ሺህ 257 የሚሆኑ የተለያዩ የታወር ብረቶች ደግሞ በቁማቸው ካሉ ማማዎች ተፈትተው ” ተቁሙ መዘረፉን ሲገልጽ ያለው ነው። ሙሉውን ዜና እዚህ ላይ ያንብቡ

“ሰሞኑን ‘የ፰ ወር ሕጻንና ጨቅላ ወንዶች የሚደፈሩባት ትግራይ’ ሲሉ የሄርሜላ እናት ፕሮፌሰር ሐረገወይን አሰፋ በኢሳት የሰጡትን ቃለምልልስ ሰምቶ የማይደነግጥ ከሰው ያልተፈጠረ ብቻ ነው” ሲሉ አስተያየታቸውን እንደሰጡት ሁሉ፣ የብረሃን ማስተላለፊያ እያስፈረሱ፣ በህዝብ ገንዘብ ተበድረው ላቆሙት ፋብሪካ ጥሬ ምርት አድርገው ዳግም በማቅለጥ፣ መልሰው ገበያው ላይ በወኪሎቻቸው በመሰወር ሃብት የሚያግበሰብሱ ወረበሎችን እስከመቼ ነው ” ባለሃብት” የምንላቸው? በአብዛኛው ሚዲያውስ የነሱ ቅምጥ ሆኖ የሚኖረው እስከመቼ ነው? እንዴት ብርሃን ይሰረቃል? በብርሃን ወይም ኤሌክትሪክ ችግር እስከመቼ ምስኪን እናት ፍሬዋን ሳታይ ትሞታለች? ህክምና ይስተጓጎላል? የስንቱ ኩላሊት ይፈለንዳል? እናም መንግስት ሆይ የቤተመንግስትህን አጥር ነቃቅለውና አስነቅለው ሳያቀልጡልህ ወስን። ተቋሙ ፍንጭ ሰጥትቷል ወርደህ ስራ።አለያ ያቋቋምከው አዲሱ ወረበላ ሚዲያ ላንተ ሳይሆን ለሚተኩህ አዝማች ያወርድላቸዋል።

የብረቱን ሰምተን ሳንጨርስ ነዳጅ ስር የሚርመጠመጡ ባለስልጣናት መኖራቸውን ሰማን። ይህ መረጃ ይፋ ሲሆን ” ባለፉት አምስት ወራት የታለመ የነዳጅ ድጎማ ተግባራዊ በመደረጉ 29 ቢሊዮን ብር ወጪ ማዳን መቻሉን የነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣን ገለጸ። በእነዚህ ወራትም መንግስት ለህዝብ ትራንስፖርት ተሽከርካሪዎች ለነዳጅ ድጎማ ሶስት ቢሊዮን ብር ወጪ ሆኗል” ሲሉ የባለስልጣኑ የነዳጅ ውጤቶች የገበያ ጥናት ዳይሬክተር አቶ ለሜሳ ቱሉ መግለጫ ሰጥተዋል።

ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ እንባ ጠባቂ ተቋም የነዳጅ ድጎማው ለሌብነት መጋለጡን በጥናት ይፋ አድርጓል። የባልስልጣኑን መረጃ ያተመው አዲስ ዘመን የነዳጅ ድጎማው ከታለመለት አላማ ውጭ ለሌብነት መጋለጡን፣ ኮንትሮባንድና ብክነትም በስፋት እየተስተዋለበት መሆኑን በጥናት ማረጋገጡን የኢትዮጵያ ህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ዋቢ አድርጎ አምልክቷል።

የኸው የተቋሙ ገጽ የፊስ ቡክ ዜና በተለያዩ ሚዲያዎች አናቱ እየተቀያየረ ቢቀርብም ቁሉፉ ጉዳይ ያልፉት 30 ዓመታት አብዮታዊ ዴሞክራሲ አልሞና አቅዶ በማገሸብ ያመረታቸው የአገሪቱ እንግዴ ልጆች ስጋ ከሌለው ህዝብ አጥንት ላይ እየጋጡ መሆኑን ነው። ሌብነቱ ቀዳዳ ባገኘበት ሁሉ እየገባ እንደ ዘንዶ አገሪቱን እያነካከታት እንደሆነ ሌላው ማሳያ ነው።

የእህቱን ልጅ አፍኖ ካሳ የሚጠይቅ የከሸፈ ትውልድ፣ ሰው ገሎ፣ ሰቅሎ፣ በድንጋይ እየወገረ ቪዲዮ የሚቀርጽና ይህንኑ ህሊናን የሚፈትን ቪዲዮ በማህበራዊ ገጽ የሚቀባበል ማሰብ የተሳነው ትውልድ፣ በተወለድበት ማህበረሰብ የዘር ገመድ እየሳበ በደም የሚነግድ፣ “ሂሳቡን እኔ አወራርዳለሁ እናንት ሙቱ” የሚል ሞራል አልባ የተሰገሰገባት ኢትዮጵያ፣ በሃይማኖት ስም በአደባባይ ህዝብ የሚታለብበት፣ ማንም እየተነሳ ራሱን እየቀባ ህዝብ በትንቢት ህዝቧ የሚዋከብባት፣ የታቦት ስም እየተጠራ ህዝብ ወደ ሞት እንዲነጉድ እያማተቡ ፊሽካ የሚነፉባት፣ ላዩትም ላላዩትም የአላህን ስም እየጠሩ ውቃው በለው የሚባልባት ኢትዮጵያ፣ ከውጭ ሆነው ለራት ዓመት ሳያቋርጡ ሙሾና ስድብ የሚያመሩርቱ ጉዶችን የቻለች ኢትዮጵያ ትሻገር ዘንዳ ምን ይደረግ?

“አላሽቀውናል። የላሸቁ ተቋማት ተለጣጥፈው አንዲላሽቁ ተደርገው በተሰሩ እራፊ አዕምሮ ባላቸው ተመርተዋል። የጸጥታ ተቋሞቻችን ፈርሰዋል።መከላከያችን አንዲወድም ተደርጓል። ኢኮኖሚው አንዲሰበር ሆኗል። በሃይማኖት ተቋማት ሳይቀር የላሸቁ ገብተው አነትበውናል። በየስፍራው ሞትን በየአይነቱ፣ ስደትን በየፈርጁ፣ ሃዘንን በፈረቃ አከናንበውናል። በስተመጨረሻ ዩሪ አንዳለው ኖርማላይዝ ወይም አረጋጊ ሆነው ለመምጣት ከገዟቸውና ከራሳቸው ሚዲያዎች ጋር ሆነው በደም ጀልባ ጉዞ መጀመራቸውን አየወተወቱ ነበር። “የአይጥ ምስክር ዲንቢጥ አንዲሉ” አራጅና አሳራጅ ከእርድ ከተረፉት በላይ “ እመኑን” ብለውንም ነበር። ኢትዮጵያ በምርጦቿ ጸሎት፣ በውድ ልጆቿ ደም፣ በቀደመው ማተቧ ተሻግራለች። ግን ላሽቀውና ደንቁረው በባዶ ህሊና የተመረቱት እንግዴ ልጆቿ ዛሬም እየወጓት ነው። ብርሃን በማጥፋት፣ ደሟን በመጠጣት!! ከስር እንባ ጠባቂ ጠቅሶ አዲስ ዘመን የዘገበው ነው።

በኢትዮጵያ የህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም የታለመው የነዳጅ ድጎማ አተገባበርና በአፈፃፀም ሂደት ላይ ያጋጠሙ ችግሮችን የዳሰሰ የጥናት ውጤት ይፋ ሆኗል።

የኢትዮጵያ የህዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ዋና ዕንባ ጠባቂ ዶክተር እንዳለ ሃይሌ እንደገለፁት የጥናቱ ዓላማ ህብረተሰቡ ከታለመለት የነዳጅ ድጎማ አሰራር ተጠቃሚ መሆኑን ለማረጋገጥና በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመለየትና ቀጣይ የመፍትሔ እርምጃ ለመውሰድ እንዲቻል ነው ብለዋል።

የነዳጅ ድጎማው የመንግስትን ወጪ ለመቀነስ፣ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ፣ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ፣ በነዳጅ ላይ የሚስተዋለውን ኮንትሮባንድ ንግድና ብክነትን ለማስወገድ ያለመ መሆኑንም አስታውሰዋል። ይሁን እንጅ የታለመለት የነዳጅ ድጎማ አተገባበር ሰፊ ክፍተቶችና ችግሮች የሚስተዋሉበት መሆኑን ጥናቱ አመልክቷል።

በተለይ የነዳጅ ማደያዎችና ችርቻሪዎች አካባቢ ሌብነትና ህገ ወጥነት እንዲሁም የኮንትሮባንድና ብክነት በስፋት የሚስተዋል መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህም አልፎ ድጎማው ከህብረተሰቡ ይልቅ አሽከርካሪዎች ባልተፈለገ መልኩ እየተጠቀሙበት እንደሆነ ጥናቱ ማመላከቱን ገልጸው ድጎማ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎች መደበኛ አገልግሎት መስጠት ትተው በኮንትራት ስራ ላይ መሰማራታቸውንም ተናግረዋል። የነዳጅ ድጎማ ተጠቃሚ ሆነው የ90 ብር ታሪፍ እስከ 200 ብር እንዲሁም የ300 ብር ታሪፍ እስከ 600 ብር እያስከፈሉ መሆኑን ጥናቱ አሳይቷል ነው ያሉት።

ለዚህ ደግሞ በትራንስፖርት ስምሪት አካባቢ የተቀናጀ ስምሪትና ቁጥጥር ያለመኖር፣ የንግድና የትራንስፖርት ዘርፉን የሚመሩ የስራ ሃላፊዎችና ሙያተኞች ሃላፊነታቸውን በአግባቡ ያለመወጣትና ቅንጅታዊ አሰራር ደካማ መሆን ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል።

ችግሮቹን ለመፍታት የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ አሰራር ማጠናከር፣ ድጎማውን የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን በ’ጂፒ ኤስ’ ቴክኖሎጂ መቆጣጠር እንደሚገባ ገልጸዋል። ችግሮቹን በዘላቂነት ለመቅረፍ የታለመለት የነዳጅ ድጎማ ዓላማን መሰረት ያደረገ አሰራርና የፖሊሲ ማዕቀፍ ማዘጋጀት እንደሚገባም ጠቁመዋል።

አተገባበሩ ወጥና ውጤታማ እንዲሆን ከፌዴራል ጀምሮ ክልሎች፣ የከተማ መስተዳድሮች፣ ዞኖችና ወረዳዎች ጨምሮ አዋጁን በባለቤትነት መፈጸም እንዳለባቸው አመላክተዋል። የታለመለት የነዳጅ ድጎማ ተግባራዊ ከተደረገ ወዲህ በየወሩ ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ መንግስት ለነዳጅ ያወጣ የነበረውን ወጪ ማዳን መቻሉ ተገልጿል።

Exit mobile version