Site icon ETHIO12.COM

በችግሩ ወቅት ያስጠጋውን የጓደኛዉን መኖሪያ ቤት በድብቅ ለመሸጥ …


በስልጤ ዞን ወራቤ ከተማ ተከሳሽ አቡበክር ሱጋቶ እና የቅርብ ጓደኛዉ ቶፊቅ ከድር አብረዉ በጓደኝነት እየኖሩ ቆይተዉ ተከሳሽ መኖሪያ ቤት ስለሌለዉ በቤት ኪራይ መቸገሩን ያስተዋለዉ ጓደኛዉ ከቤተሰቡ ጋር በመኖሪያ ቤቱ በተወሰኑ ክፍሎች እንዲኖር ይፈቅድለታል፡፡

ከዚያም ለግዜዉ ባልታወቀ ሁኔታ ጓደኛዉ ቶፊቅ ከድር ያሲን የደረሰበት ይጠፋል፤ ተከሳሽም ይህን አጋጣሚ እንደ መልካም እድል በመዉሰድ የጓደኛዉን ቶፊቅ ከድር ያሲንን መኖሪያ ቤት ለመሸጥ በከተማዉ ከሚገኙ የቤት ደላሎች አንድ ሚሊዮን ብር ይስማማል፡፡

በመቀጠል ግለሰቡ ወራቤ ከተማ አስተዳደር 02 ቀበሌ ጽ/ቤት በመሄድ ራሱን ቶፊቅ ከድር ያሲን እንደሆነ በመቅረብ አጭበርብሮ የቀበሌ መታወቂያ አስወጥቶ ድርድር ላይ ሳለ የስልጤ ዞን ፖሊስ መምሪያ የሙስና እና ሙስና ነክ ወንጀሎች ምርመራ ዳይሬክትሬት ጥቆማ ይደርሰዋል፡፡

ከዞኑ ዓቃቤ ህግ የወንጀል ክስ የቀረበለት የስልጤ ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤትም በመዝገብ ቁጥር 20153 ሲያከራክር ቆይቶ በቀን 14/04/2015 የሙስና ወንጀል ችሎት ተከሳሽን በከባድ ማታለል ወንጀል ጥፋተኛ ብታል፡፡

በዚህም ተከሳሽ የአራት ዓመት ከአምስት ወር ጽኑ እስራት እና አንድ ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጣ መወሰኑን የዞኑን ፍትህ መምሪያ ዋቢ አድርጎ የስልጢ ወረዳ ኮሚኒኬሽን ዘግቧል፡፡

Exit mobile version