ETHIO12.COM

የትግራይ ሕዝብ ከትህነግ ምን አተርፈ? መላሹ የትግራይ ሕዝብ ብቻ ነው

ስልሳ ሺህ የትግራይ ወጣቶች እንደተገበሩበት የተነገረለት የጫካ ትግል፣ ትህነግን ቤተመንግስት ከቶት በዛው ተካካሰ። የ”ልጆቻችን” ጥያቄ ሞታቸው “የተሰው ጅግኖች፣ በማዕታት” ስም ተተክቶ ” ትግሬ መንግስት ሆነ” በሚለው ምላሽ ታትሞ፣ ከለቅሶ ይልቅ በዜማ፣ በዕልልታ ተወደሰ። ትህነግ በዚያው ውዳሴ ውስጥ ሆኖ፣ “ጦርነት ባህሉ፣ ቁርሱና ምሳው የሆነ ህዝብ” ሲል ማንም አካል ሊገዳደረው እንደማይችል አሳመነን። እናም በትግራይ ጦርነት ከተነሳ ማደባየት፣ መደምሰስ፣ መማረክ፣… እንጂ መማረክ፣ መደምሰ፣ መሞት የሚባሉት የጦር ሜዳ ህጎች ትህነግ ላስተማረን የማይታሰብ ሆነ።

በባድመ ጦርነት ትህነግ ” የደርግ” ሲል ለአገራቸው የተዋደቁትን በሙሉ ለማኝ ካደረገበት ቀስቅሶ፣ መላውን አገር አነሳስቶ መቶ ሺህ ሰራዊት ካስበላ በሁዋላ ድርድር ተቀምጦ ” የተዋጋሁባቸው አካባቢዎች የእናንተ ነው” ሲል ይግባኝ በሌለው ፊርማ በትግራይ ህዝብ ስም የሚምለው ድርጅት አስረከበ። የትግራይን ልጆች ጨምሮ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ወገኖቻችን እንደ ፈንዲሻ ፈንጂ ላይ እየጋለቡ ላለቁበት ጦርነት ምላሹ ” አስረክቦ ቁጭ” ሆነ። ያን ጊዜ እንደ አንድ ትግራዋይ አንብቻለሁ።

ትህነግ ይህን የፈረመው በራሱ መሪ ነውና ማንንም ሊከስ፣ ሊያንጠለጥል፣ ተጠያቂ ሊያደርግ አይችልም። እናም በትግራይ ህዝብ ስም ያላወራረደው የደም ዕዳ አለበት። የመቶ ሺህ ሰው ጓዳ የሃዘን እንባ እየጮከበት ነው። ባድመን አስረክቦ መጥቶ አዲስ አበባ ላይ ” ባድመ በፍርድ ቤት ተወሰነልን” በሚል ድፍን አዲስ አበባን በቱሻ ሲያስጨፍር አቶ ስዩም ነብሳቸውን ይማረውና ጥቁር ክራባት አድርገው የተናገሩትን ስናስታውስ ሁሌም እንድናለቅስና እንድንሸማቀቅ ያደረገን ትህነግ የሚባለው ድርጅት ቅጥፈቱ የት ድረስ እንደሆነ ስለሚያሳየን ነው። እንደ እኔ ላሉ የትግራይ ተወላጆች ይህ ትልቁ ማንቂያ በሆነን ነበር። ግን አልሆነም። በሆነ አፍዝ አደንግዝ ይዞን ይሆን?

ሁሉም ይቅር ከለውጡ በሁዋላ ትህነግ ለምን መቀለ ግብቶ ተደበቀ? ቴውድሮስ በርዕዮት ሚዲያው ላይ ቢዘገየም ያነሳው አሳብ ምንም ማስተባበያ ሊቀርብበት አይችልም። ትህነግ ለምንስ ገና በጠዋቱ የጦርነት ከበሮ መምታት ጀመረ? ምንድን ነበር ያልተመቸው? ዛሬ እደራደራለሁ ሲል ምን አትርፎ ነው? ይህን ከጅምሩ እስከ መጨረሻው መመርመር የትግራይ ህዝብ ፈንታ ነው። የኔም ጭምር።

ትህነግ ወደ መቀለ ሲሸሽ፣ በትግራይ መብራት ነበር። ውሃ እንደ አቂሚቲ ነበር። ልጆች ይማሩ ነበር። ተቋማት ይሰሩ ነበር። ስልክና ኢንተርኔት ነበር። አየር፣ መኪና ሁሉም አይነት እንቅስቃሴ ነበር። ላለፉት ሁለት ዓመታት ምንም አልነበረም። ለምን? ምን ነበር የዚህ ሁሉ ጣጣ ምክንያቱ? ይህ ሁሉ ከሆነ በሁዋላ ምን ተገኘ?

ጦርነቱ ከተጀመረ በሁዋላ፣ አንደኛ፣ ሁለተኛ፣ ሶስተኛ … ትህነግ የት ድረስ ሄዶ ወንጀል ፈጸመ? ለምን እዛ ድረስ ሄደ? እዛ ድረስ ሄዶ ሲመለስ ከዘርፈውና ካወደመ ውጪ ምን አተረፈ? ለትግራይ ህዝብና ለራሷ ለትግራይ ምን ልዩ በረከት አስገኘ?

በመጨረሻው ጦርነት ምን ሆነና ትህነግ “ሁሉንም እቀበላለሁ” ብሎ ፈረመ? ዛሬ ሲፈርም ምን ልዩ ነገር ተደርጎለት፣ ወይም በፊት ያልነበረ ምን ተሰጥቶት? ወይም አለቁ ለሚባሉት የትግራይ ልጆች ደም ማካካሽ የሚሆን ምን አግኝቶ? ይህን መመርመር የትግራይ ህዝብ ፈንታ ነው።

ለመሆኑ ባይቶና እንዳለው፣ ኦባ ሳንጆ እንዳሉት ተደመሮ ሳይሆን ራሱ ትህነና ወላድ በምታውቀው ያለቁት የትግራይ ልጆች “ለምን ሞቱ” ለሚለው ጥያቄ ዛሬ ላይ ተንፍሶ እጁን የሰጠው ትህነግ ምን መልስ ይኖረዋል? ይህን ጥያቄ የትግራይ ህዝብ ረጋ ብለህ ጠይቅ? ሌላው ትህነግ ከአፋር፣ አማራና ኤርትራ ጋር ጠላት ሆኖ የትግራይን ህዝብ ወዳጅ አልባ አድርጎ የዘለቀበት መንገድ ምን ኪሳራ አደረሰ? እስኪ ይህንንም የትግራይ ህዝብ ያጢነው። ለግዜው ኢትዮ ኢንሳይደር የትግራይ ተፈናቃዮች አተር ክክ፣ ስንዴ ዘይት ምናምን የዓለም ምግብ ድርጅት ማህተብ ባለበት ጆንያ እየተሰጠ መሆኑን ጽፏል። ይህ ነው የጦርነቱ ውጤት?

ክክ እየተሰፈረ መውሰድ? ዱቄት እየተለካ፣ ዘይት እየተመተረ … ትህነግ ይህን ለማድረግ ነበር ውጊያ የገባው? አርፈው የሚኖሩ የትግራይ ምስኪኖች ተፈናቅለው እርዳታ ጠባቂ እንዲሆኑ ማድረግና፣ ” እርዳታው በቂ አይደለም” በሚል መግለጫ ለመስጠት ነው ትህነግ ቋምጦ የነበረው? የትግራይ ህዝብ ሳይፈናቀል፣ በትግራይ ህዝብ ስም ሌሎች ሳይፈናቀሉ፣ አስቀድሞ መስማማት አይቻልም ነበር?

ትግራይን ጨለማ ማድረግ፣ ህዝቡን ማስራብና ማዋረድ፣ በሚሰቃዩ የትግራይ ልጆች ምስልና ቪዲዮ መነገድ….. ነበር የሚፈልገው? በፊት የትግራይ ህዝብ የተነፈገው፣ ዛሬ ይህ ሁሉ ደርሶበት ያገኘው ጥቅም ምንድን ነው? ይህን ጥያቄ ማስላትና መመለስ ካልተቻለ እንደ ሰው “ማሰብ” የሚባለው፣ ” በምክንያት ማሰብ” የሚሉት አስተዋይነት ጥያቄ ውስጥ ይገባል። እውነት ለመናገር ዛሬ ላይ የትህነግ መሪዎችና ደጋፊዎች ትግራይ ህዝብ ፊት ቆመው ለማውራት ሞራል የላቸውም። ማሳብ ሞታለችና እርም አውጥቶ መቀመጥ ነው።

ለትግራይ ህዝብ አንድ ትህነግ ብቻ አማራጭ ሆኖ፣ አንድ ትህነግ ብቻ መሲህ ሆኖ፣ አንድ ትህነግ ብቻ መፍትሄ ሆኖ የሚኖረው እስከ መቼ ነው? ማሰብ የሚሉት የህሊና አስኳል ለመሞቱ ማረጋገጫው ይህ ነው።

እርግጥ ነው ሃብታሞች ተፈጥረዋል። እነማን ናቸው? ይታወቃሉ። የሌብነት መንደር በትግራይ አለ። ባለቤቶቹ ግልጽ ናቸው። በውጭ አገር ብዙ ልጆች አሉ የነማን ልጆች እንደሆኑ ግልጽ ነው። የነማን ሚስቶችና ቤተሰቦች እንደሆኑ ድብቅ የለውም። የሞተው፣ አመድ የለበሰው፣ ጨለማ ውስጥ የቀረው… ምስኪን የትግራይ ህዝብ እያንዳንዱ ቤት ድንኳን ተተክሏል። ካድሬዎቻችን ዛሬም ይህ ሁሉ ደርሶ አላፈሩም… እና እስከመዜ በዚህ እንቀጥል?

“ኢትዮ ኢንሳይደር ክክ እየተለካ መሰጠቱን በአይኑ አይቶ ያቀረበውን ዜና ሳይ ከበሸቁት አንዱ ነኝ” በሚል ከአውሮፓ ነዋሪ የተሰጠንን አስተያየት አሳጥረን አቅርበነዋል። ተናጋሪው በሌላ ጉዳይ በስፋት እመለሳለሁ ብለዋል። “ጎረቤት አልባ ካደረግን የትህነግ ፖለቲካ ለመዳን ማሰብ አለብን” ሲሉም አክለዋል። የኢትዮ ኢንሳይደር ዜና ከታች ያለው ነው።

በትግራይ ክልል በነበረው ጦርነት ምክንያት ከቀያቸው ተፈናቅለው በመቐለ የተለያዩ አከባቢዎች የተጠለሉ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ የክልሉ ነዋሪዎች እንዳሉ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ለእነዚህ ተፈናቃዮች ከሚቀርበው የእለት ደራሽ እርዳታ በተጨማሪ በመቐለ እና በሌሎች ከተሞች ላሉ ነዋሪዎችም እርዳታ በመከፋፈል ላይ ይገኛል፡፡

በግብረ ሰናይ ድርጅቶች አማካኝነት የሚመጣው ይህ እርዳታ እንደ መቐለ ባሉ ከተሞች እየተከፋፈለ የሚገኘው በትግራይ ክልል አስተዳደር ነው፡፡ በመቐለ ዓዲ ሓቂ ክፍለ ከተማ ይህንኑ አካሄድ በተከተለ መልኩ ትላንት ቅዳሜ ታህሳስ 22 አመሻሽ ላይ እርዳታ ሲከፋፈል ነበር፡፡

ለከተማይቱ ነዋሪዎች የሚቀርበው እርዳታ የሚሰላው በአንድ ግለሰብ ልክ ሲሆን ክፍፍሉ በሚደረግበት ጊዜ አንድ ቤተሰብ በስሩ ባሉት የሰዎች ቁጥር ብዛት እየተሰፈረ ድርሻው ይሰጠዋል፡፡ ለአንድ ሰው የሚደርሰው የእርዳታ መጠን 15 ኪሎ ግራም ስንዴ፣ አንድ ኪሎ ከግማሽ አተር ክክ እና ግማሽ ሊትር ዘይት ነው፡፡ ለከተማይቱ ነዋሪዎች የሚከፋፈለውን የእርዳታ እህል የያዙት የማዳበሪያ ከረጢቶች የዓለም የምግብ ፕሮግራም (WFP) መለያ የታተመባቸው ናቸው፡፡ (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

Exit mobile version