Site icon ETHIO12.COM

የአያንቱ ኑዛዜ – የጭካኔ ጥግ

ሰዎች ይማሩበት አንብባችሁ ሼር አድርጉት

ዛሬ ስራ ቦታ ወደ ምሳ ሰዐት አካባቢ አንዲት እናት ብር ወጪ ለማድረግ ትብብር ፈልጋ ወደ እኔ መጣች!

አያንቱ ትባላለች ከቡራዩ አለፍ ብሎ በሚገኝ አንድ የገጠር ከተማ ላይ የምትኖር ምስኪን እናት ስትሆን የካንሰር ታማሚ የሆነ ልጇን ለማሳከም የካንሰር ህሙማን ማገገሚያ መጥታ በወሬ መሀል የገጠማትን አንድ አሳዛኝ ክስተት ነገረችኝ:-

“ወደ አዲስ አበባ እንደመጣሁ የሪፈር ወረቀቴን ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል አስገብቼ ልጄ ህክምና ጀመረ መድሃኒት ለመግዛት ቦርሳዬን ይዤ ወደ ውጪ በወጣሁበት ቅፅበት አንድ ሰው ወደ እኔ ቀረብ ብሎ ያወራኝ ጀመር ለምን እንደመጣሁ ጠየቀኝ የ12 አመት ልጄ የካንሰር ታማሚ መሆኑንና ከ3ጊዜ በላይ ሰርጀሪ መሰራቱን የመጨረሻ እድሌንም ልሞክር ብዬ ቤቴን ሽጬ መምጣቴን አሁን ላይ አጠገቤ ሆኖ የሚረዳኝ ሰው አለመኖሩንና ልጄ እራሱ ከአልጋ ቢወድቅ የሚያነሳው ረዳት አለመኖሩን ነገርኩት!

እሱም እህቱን ለማስታመም መምጣቱን ነግሮኝ የመድሃኒትና የአልጋ ወጪው እንደከበደውና ተስፋ ቆርጦ ህክምናውን ሊያቋርጥ ሲል ከውጪ የመጡ ፈረንጆች በነፃ ህክምና የሚሰጡበት ተቋም አግኝቶ የእህቱ ጤና መመለሱን ነገረኝ እኔም ወጪውን ስለማልችለው በጊዜ ልጄን አስወጥቼ ያለኝ ተቋም እንዳስገባው ወተወተኝ የልጄ ህመም ይፈውሳል የተባለ ቦታ ሁሉ ለመሄድ ዝግጁ ስለነበርኩ ተቋሙ የት እንደሆነ ጠየቅኩት!

እሱም ዶክተሮቹ ወደ ሀገራቸው ከመመለሳቸው በፊት የማውቃቸው ጓደኞች ስላሉኝ ቶሎ እንዲጨርሱልኝ አደርጋለሁ ብሎኝ ወደ ራስ ደስታ ወሰደኝ!የተወሰነ መንገድ እንደሄድን ሁለት ሰዎች ተቀላቀሉን!በሱ ረዳትነት አልጋ መያዛቸውንና ለምስጋና መምጣታቸውን ነገሩኝ!

መንገዱን ቀጥለን ራስ ደስታ በር ላይ ስንደርስ እንዴ ይሄንማ አውቀዋለሁ ከዚህ በፊት ለደም ምርመራ መጥቻለሁ ስለው አንቺ የገባሽው በዛኛው በር ነው ፈረንጆቹ የሚሰሩት አሁን በምንገባበት በር ነው አለኝ እሺ ብዬ ተከተልኩት ግቢ ውስጥ እንደገባን ግን የማውቃቸው ሰዎች ስላሉ አናግሪያቸው ልምጣ እናንተ እዚህ ጠብቁኝ ብሎ ወደ ውስጥ ገባ!

ትንሽ ቆይቶ “ተፈቅዷል ትምጣ”ብሎ ጓደኞቹ ጋር ደወለ እኔም ደስ ብሎኝ ወደ ውስጥ ልገባ ስል ቦርሳ አያስገቡም እኛ እንጠብቅልሻለን ግቢ አሉኝ እሺ ብዬ ልገባ ስል ዝርዝር አስር ብር ይዘሻል አሉኝ አልያዝኩም ድፍን ሃምሳና መቶ ነው ስላቸው ለካርድ ማውጫ ይሆንሻል አስር ብር ሰጥተውኝ ወደ ውስጥ ገባሁ!

ልጁ ቆሜ እየጠበኩሽ ነው ያለኝ ቦታ ላይ ስደርስ ማንም የለም!ወደ ውስጥ ገብቶ ከሆነ ብዬ ለረጅም ደቂቃ በር ላይ ብጠብቅም ላገኘው አልቻልኩም! ተጠራጥሬ ወደ ውጭ ስወጣ ልጆቹ የሉም!መታለሌ መዘረፌ ገባኝ እሪታዬን አቀለጥኩት፣ሰው ተሰበሰበ እራሴን ስቼ ወደቅኩ

ቦርሳ ውስጥ የልጄ ህልም ነበር በሰዓቱ ቦርሳ ውስጥ የነበረው 10ሺህ ብርና ስልኬ ትዝ አላለኝም፣የልጄ ሪፈርና የህክምና ሲዲዎች ውስጡ ነበሩ ልጄ ከለበሰው ልብስ ውጪ ቅያሪ ልብሶቹ ሳይቀር ቦርሳው ውስጥ ነበሩ!

በመጨረሻም ለቅሶዬን ያዩ የጥቁር አንበሳ ቅን ዶክተሮች ተባብረውኝ የሪፈር ወረቀቱ ኮፒ ተገኘ በሲዲ የነበሩት የህክምና ዶክመንቶችም ኮፒ ተደርገው ተሰጡኝ አሁን ላይ ልጄ የህክምና ክትትሉን እያደረገ ነው”ብላ እያነባች ታሪኳን አወጋችኝ!

እሷ ንግግሯን ስትጨርስ እኔ እራሴን ለመቆጣጠር ብሞክርም አልቻልኩም!የደረሰባት የጭካኔ ጥግ የሰው ልጅ ክፋት ምን ድረስ ይሆን?የሚለው አስለቀሰኝ
©Mame Mussa

Exit mobile version