Site icon ETHIO12.COM

ጊዜያዊ ጥቅም በሚያሾረው የጣና ዳር ፖለቲካ

ከአራት ዓመት በፊት ለውጡን ተከትሎ የአማራን ሕዝብ የለውጥ ፍላጎት ለማሳካት በብዙዎች ግፊትና ፍላጎት ዶ/ር አምባቸው በፌደራል መንግሥት የነበረውን የሚኒስተርነት ለቆ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሆኖ በክልሉ ምክር ቤት ፊት በመቅረብ ቃለ መሃላ ፈጽሞ የተሾመው በዛሬው ቀን ማለትም የካቲት 29/2011 ዓ.ም ነበር።

ሚሊዮኖች በ ዶ/ር አምባቸው የአመራር ዘመን ክልሉ ውስጥ ለውጥ ይመጣል እንዲሁም በክልሉ ውስጥም ሆነ ከክልሉ ውጭ የሚኖረው የአማራ ህዝብ የሚያነሳቸው ጥያቄዎች በሂደት ይፈታሉ የሚለው ተስፋ በአጭሩ ተቀጨ። ዶ/ር አምባቸው በኃላፊነት የቆየው 106 ቀን ወይም 3 ወር ከ 16 ቀን ሲሆን የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ዘበኞች ከዚህ በላይ አይደለም በኃላፊነት በሕይወት እንዳይቀጥል ሕይዎቱን በግፍ ነጠቁት። በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ጠባቂዎች ጠንሳሽነትና መሪነት በወያኔያዊ የአማራ ብሔርተኝነት የጋለ ድጋፍ ሰኔ 15/2011 ዓ.ም በጠራራ ፀሐይ በስራ ቦታው ላይ እያለ “እባካችሁ ተውኝ ለልጆቼ እንኳን ልትረፍላቸው” ብሎ እየለመነ ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ የግፍ ሰለባ ሆነ። ያወረዱበትና ያርከፈከፉበት የጥይት ናዳ ስላልበቃቸው ደረጃ ለደረጃ ጎተቱት። መደመርን በአማራ ክልል ገደልነው ቀናነስነው ብለውም ተሳለቁበት። ግፈኞች ከወንድማማችነት ይልቅ ጠላትነትን ምርጫቸው ያደረጉ ናቸውና በፈፀሙት ግፍ ከመፀፀት ይልቅ ዛሬም ለሌላ ግፍ እያደቡ ነው።

በዶ/ር አምባቸው ላይ የፈፀሙትን ክህደት የፈፀሙበትን ግፍ በዶ/ር አብይ ላይ የመድገም ምኞት እንዳላቸው በጓዳ ያይደለ በአደባባይ እንደ ጋዳፊ ይጎተታል እንጎተዋለን እያሉ ደጋግመው ሲገልፁ ታይተዋል።ጥፋትን በጥፋት ለመሸፈን የሚደረገው መወራጨት እስከምን ድረስ ይቀጥላል የሚለውን ወደፊት ጊዜ ያሳየናል።

ሰኔ 15 ወደ ዶ/ር አምባቸው የተሳበው ቃታና የተርከፈከፈው ጥይት መደመር ላይ ነው።አዎ አምባቸው ላይ ሳይሆን መደመር ላይ። የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ጠባቂዎች ጠላታቸው አምባቸው ሳይሆን መደመር ነው። የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መቃብር ጠባቂዎች የኢትዮጵያ ብሔሮች ወንድማማችነት፣ ፍትህ እኩልነትና ዲሞክራሲ ደመኛ ጠላቶቻቸው ናቸው ።

ብዙዎች የሰኔ 15 ጥቁር ቀን የተፈጠረው ጊዜያዊ ጥቅም በሚያሾረው የጣና ዳር ፖለቲካ ይመስላቸዋል። ጉዳዩ ግን ፈፅሞ እንደዛ አይደለም። አለመሆኑን የሚያረጋግጥልን ሰኔ 15 በድንገት ደርሶ የተከሰተ ሳይሆን የመስመር ጎራ እየለየ የሞት አዋጅ እየነገረ የተፈጠረ መሆኑ ነው። የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ጠባቂዎች በአንድ በኩል የመደመር አቀንቃኞች ደግሞ በሌላ በኩል ቆመው ቀድመው መታየታቸውን በሁለቱ መስመሮች ዙሪያ በቂ ግንዛቤ የነበረውና ያለው አካል የሚስተው አይደለም።

ሰኔ 15 እንዲፈጠር የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መቃብር ጠባቂዎች መደመር በአማራ ክልል ከጅምሩ እንዲቀጭ የታቀደ የተጠና ያልተቋረጠ የሚዲያ ዘመቻ በመክፈት የመደመር መንገድን የደገፉትን ወይም ሊደግፉ ይችላሉ ያሏቸውን በሙሉ በብአዴንነት በመፈረጅ ከፍተኛ ዘመቻ አካሂደዋል። በአንፃሩ የመደመር አቀንቃኞች ሕዝቡ ለ27 ዓመት ታፍኖ የኖረና ግፍ የደረሰበት በመሆኑ ብሶቱንም ሆነ ጥያቄውን በነፃነት እንደፈለገ እንዲገልፅ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብቱ ይረጋገጥ ዘንድ በመፍቀዳቸው ሁሉም ብሶቱን ሲገልጥ ለአማራ ሕዝብ መጠቃት ብአዴን ዋና ጠላትና ተላላኪ ተደርጎ በመወሰዱና የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ጠባቂ ብአዴናዊያን የመደመር አቀንቃኞችን አስቀድመው ብአዴንነትን ሊያስቀጥሉ የቆረጡ ብአዴናዊያን በማስመሰል ቁስሉን በመነካካትና የሕልውና ስጋት በማሳየት ሕዝቡን በቀላሉ ለመያዝና የመደመር አቀንቃኞችን ቅቡልነት በመንጠቅ የሰኔ 15 ን ጥቁር ቀን ለመፍጠር የሚያስችል የማድረግ አቅም ፈጥሮላቸዋል።

ዶ/ር አምባቸውን ያስገደለው ከክልሉ ውጭ ስለሚኖረው አማራ እያሰብን እንታገል ወንድሞቻችን ከሌሎች ብሔሮች ጋር በእኩልነትና በፍትሃዊነት አብረው በመከባበር በሰላም የሚኖሩበትን መንገድ እንምረጥ በማለቱ ነው። ዶ/ር አምባቸው በግፍ የተገደለው ወንድማማችነትን በማስቀደሙ ነው። ከኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ጋር በመገናኘት ስለ አማራና ኦሮሞ ሕዝብ የእርስ በርስ ግንኙነትና ወንድማማችነት መጠናከርና ስለ ዘላቂ ሰላምና አብሮነት ተደምረው ስለመከሩ ነው።

የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ጠባቂዎች በረከት ስምኦን ኦሮማራን ያልተቀደሰ ጋብቻ ብሎ ከገለፀበት በላይ በመሄድ የሁለቱን ግንኙነትና አንድነት ለማጣጣል የራስን የተቃርኖ ትርክቶችን ለመፍጠር የተሄደበት ርቀት የሚያሳየን፣ መደመርን ስር እንዳይኖረው የማድረግ የታቀደ ዘመቻ ስለመሆኑ እንጅ ከክልሉ ውጭ ስላለው አማራ ሕልውና ስለመቆርቆር አለመሆኑን ነው። እነዚህ በአማራ ክልል በኩል ያሉ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ጠባቂዎች ከሌሎቹ ለየት የሚያደርጋቸው የእኛ የሚሉትንም እንደጠላት ማየታቸው ነው።

ከክልሉ ውጭ ስለሚኖረው አማራ ሕልውና ግድ የማይላቸው የእኛ የሚሉት ሕዝብ ከሚኖርበት ክልል መንግስት ጋር እንደጠላት መተያየትን የመረጡና የእኛ የሚሉት ሕዝብ በብዛት ከማይኖርበት የክልል አመራር ሃይል ጋር ደግሞ ስትሬቴጂክ አጋር ነን የሚሉ መሆናቸው አንዱ ማሳያ ነው።
እነዚህን ለሁሉም ጠላት የሆኑ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ አቀንቃኞችን መታገል ሰውነት ወንድማማችነት ሰላምንና አብሮነት ፍትህ እንዲነግስ ከሚፈልግ ሁሉ የሚጠበቅ ነው።

ጠላትነት ይጥፋ፤ ወንድማማችነት ይለምልም!

Thomas jajaw opinion

Exit mobile version