Site icon ETHIO12.COM

አዲስ አበባ – ባለፉት 6 ወራት ከ1ሺህ 300 በላይ የትዳር ፍቺ ተመዘገበ

ባለፉት 6 ወራት ከ1ሺህ 300 በላይ የትዳር ፍቺዎች ተመዝግበዋል – የአዲስ አበባ ከተማ ወሳኝ ኩነት ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ


በአዲስ አበባ ከተማ ባለፉት 6 ወራት 1ሺህ342 ፍቺዎች እና 14ሺህ 136 ጋብቻዎች መመዝገባቸውን የአዲስ አበባ ከተማ ወሳኝ ኩነት ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ አስታወቀ።

በአዲስ አበባ ከተማ ወሳኝ ኩነት ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ የወሳኝ ኩነት ምዝገባና ማስረጃ አገልግሎት ዳይሬክተር የሆኑት ወ/ሮ ቤቴልሔም ታደሰ ከኢቢሲ ሳይበር ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደተናገሩት፣ እነዚህ መረጃዎች የሚያመላክቱት በመስሪያ ቤቱ በህጋዊ መንገድ የተመዘገቡትን ብቻ ነው።

ዳይሬክተሯ እንደሚሉት፣ በተለያዩ ቦታዎች በህጋዊም ሆነ በባህላዊ መልኩ ፍቺ እና ጋብቻ ይከናወናል፤ ነገር ግን ወደ ወሳኝ ኩነት ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ መተው የሚመዘገቡት አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ናቸው።

ዘንድሮ በ6 ወራት ብቻ የተመዘገበው የፍቺ ቁጥር ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጻር ተቀራራቢ ሲሆን፤ በ2014 በጀት ዓመት 1 ሺህ 623 የፍቺ ምዝገባዎች መደረጋቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።

በአዲስ አበባ ከ2012 እስከ 2014 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ ብቻ 16 ሺህ 35 ፍቺዎች እንደተካሄዱ የወሳኝ ኩነት ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ መረጃ ያሳያል።

ትዳር በበርካታ ምክንያቶች ሊፈርስ እንደሚችል ጥናቶች የሚያመለክቱ ሲሆን ለአብነትም የኢኮኖሚ ድቀት፣ ቅናት እና አለመተማመን ወዘተ ይጠቀሳሉ።

ታዲያ የትዳሮች በፍቺ መጠናቀቅ በርካታ የማህበራዊ ቀውሶች መንስኤ እንደሆነም ይጠቀሳል።

በተለይም ትዳር በሚፈርስበት ጊዜ በትዳሩ ውስጥ የተፈሩ ህጻናት ከባድ የሆነ የስነ-ልቦና ቀውስ የሚገጥማቸው ሲሆን፤ የሁለቱንም ወላጆቻቸውን ክትትል እና እንክብካቤ ማግኘት ስለማይችሉም በቀጣይ ህይወታቸው ላይ አሉታዊ ተጽእኖን ያሳድራል።

በሰለሞን ከበደ ENA

Exit mobile version