ETHIO12.COM

ኢትዮጵያ ቅርጿን ልትይዝ ዳር ላይ – ትጥቅ ማስፈታትና ኤርትራ የዲሞክራሲን ጉዳይ እንድታስብበት መመከሯ

በተለይ ኤርትራ ከኢትዮጵያ በኩል ያገኘችውን አዲስ የትግል አጋርነት በደስታ ነው የተቀበለችው፤ ምክንያቱም ይህ አጋርነት ገና ማሸነፍ በሚጠበቅባት የቀድሞ ጠላቷ – ህወሓት – ላይ የሚከፈት ጦርነት በመሆኑ ነው። …… ለጠ/ሚ/ሩ መጥፎ ዜና የሚሆነው የሚያደርጓቸው ጥረቶች የሚያመጡት ውጤት አናሳ የመሆኑ ጉዳይ ነው። ምክንቱም ህወሓት 6ሚሊዮንና አናሳ የሆነውን የትግራይ ተወላጅ የሚወክል ድርጅት ቢሆንም ለ27 ዓመታት በሥልጣን ላይ በቆየባቸው አምባገነናዊ ዓመታት ከሌሎች ክልሎች ጋር የፈጠረውና ሥር የሰደደ ጥቅማዊ ወዳጅነት እንዲሁም ከ61 ጄኔራሎች መካከል 57ቱ የትግራይ ተወላጅ መሆናቸው የኢትዮጵያ ድንበር ጠባቂ ኦፊሰሮች ሁለት ሦስተኛው እንዲሁ ትግሬዎች ከመሆናቸው ጋር ተዳምሮ የዓቢይን ሥራ ቀላል እንዳይሆን ከሚያደርጉት ዋንኞቹ ናቸው

ብሮንዊን ብሩቶን

ሰሞኑንን በኢትዮጵያ ሰማይ ስር አዳዲስ ጉዳዮች ብቅ ማለት ጀምረዋል። በተለይ ከትህነግ ጋር የሰላም አማራጭ ስምምነት ከተደረሰ በሁዋላ ላይ በላይ የሚሰሙ ዜናዎች “ኢትዮጵያን ለማፍረስ ይሰራል” የሚባለው መንግስትና ግብሩ የተለያዩ መሆናቸውም በገቢር እየታየ ነው።

ለውጡ ይፋ ሲሆን ከወረቀት፣ ብዕርና ቢሮ ውጪ ይሄ ነው የሚባል የጸጥታ ተቋማት ያልነበረው መንግስት አሁን ላይ የገነባው የጸጥታ ተቁማት የፈረጠመ፣ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም፣ ሌሎች አገራትንም ያስገረመ፣ ከሁሉም በላይ በአንድ መረብ ስር የተቀናጁ መሆናቸውን ተከትሎ የሚነፍሰው አዲስ ዜና “ኢትዮጵያ ቅርጿን ልትይዝ ዳር ላይ ደርሳለች” የሚያሰኝ መሆኑንን ገለልተኛ ወገኖች ይገልጻሉ።

ሕዝብ የመንግስትን የውስጥ ጣጣ በቅጡ የማወቅ ዕድል ባይኖረውም፣ ለአገሩና ለአንድነቱ ካለው ቀናዊ ፍቅር በመነሳት ” በየክልሉ የተደራጁ የሰራዊት ሃይሎች ይፍረሱ” ሲል ነበር። የዘር ፖለቲካም ምንም ስላልረባ ተሽቀንጥሮ እንዲጣል ይወተውት ነበር። ህዝብ በቀናነት ይህን ሲል አብሮ ከመኖርና ሰላምን ከማስፈን እንዲሁም የቀድሞው ፍቅር እንደሚበልጥ በመረዳት እንጂ ከሌላ ፍላጎት አልነበረም።



በተመሳሳይ ለውጡ ተወልዶ ገና እትብቱ ሳይቆረጥ “ህገመንግስቱን ቀዳችሁ ጣሉ” የሚል ጥሪ ያቀረቡ ነበሩ። ከነዚህ ሃይሎች መካከል አንዱ ከረሃብተኞች ጉሮሮ ዘርፈው ከአገር የኮበለሉት መሆናቸውን ቢቢሲ በመረጃ ያጋለጣቸው ሻለቃ ዳዊት ይገኙበታል።

በሰማኒያዎቹ ዓመት የሚገኙት ሻለቃ ዳዊት ለውጡን ደግፈው አዲስ አበባ ከገቡ በሁዋላ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ እንዳላገኙዋቸው፣ በለውጡ ሂደት ውስጥ አባል ለመሆን ፍላጎት ቢኖራቸውም ባሰቡት መልኩ ቤተመንግስቱ ስላልተከፍተላቸው በቅሬታ ወዲያው ወደ ተቃዋሚነት መዞራቸውን በውቅቱ ለመንግስት ቅርብ መሆናቸውን የሚገልጹ ማስታወቃቸው ይታወሳል።

የ”ከሃዲው” ዳዊት የሌብነት መረጃ

ዳዊት በተለያዩ ጊዜያት በራሱ አንደበት እንደተናገረው በ1980 የተደረገውን መፈንቅለ መንግሥት ካከሸፉት ተባባሪዎቹ አንዱ ቁምላቸው ደጀኔ በድብቅ ከአገር ወጥቶ አሜሪካ ጥገኝነት በጠየቀበት ጊዜ ዳዊት ቤት ተቀምጦ እንደነበርና እንደረዳው አስረድቷል። የዚህ ሁሉ ገድል ባለቤት ነው እንግዲህ ዛሬ “አገር ካልመራሁ” በሚል የዘረፈውን እየረጨ በሚዲያ በተለይም ባለሃብቶች ስፖንሰር በሚያደርጉት የመረጃ ቴሌቪዥን የርስ በርስ እልቂት ክተተ የሚያውጀው።

በወቅቱ ትህነግ አኩርፎ ” አሃዳዊ መንግስት ሊመሰረትብህ ነው” በሚል ብልጽግና ላይ ከፍተኛ የፕሮፓጋንዳ ሚሳይል ሲከፍት፣ ሻለቃ ዳዊትና ያሰባሰቧቸው ” ህገመንግስቱ ይቀደድ፣ የሽግግር መንግስት ይቋቋም” በሚል ይቀሰቅሱ እንደነበር፣ ይህ የሽግግር መንግስት ቅስቀሳ በአገር ቤት ትህነግ መቀለ ሆኖ ድል ባለ ድግስ ያደራጃቸው የፌደራል ሃይሎች፣ አዲስ አበባ የተቀመጡ የሚታወቁ ‘ ቅምር’ ፖለቲከኞች ተናበው የሚያደርጉት አጀንዳ እንደነበር ዘፈኑ የገባቸው ጎን ለጎን ” ጥሪ አይቀበልም” በሚል ይቃወሙት ነበር።

በአማራ ክልል ህዝብ ሰላሙ እንዲታወክ ፣ ማህበራዊ ዕርፍት እንዲያጣና ለውጡ እንዳይረጋ በፈጠራ፣ በመናበብ፣ በትሥሥር ሲደፋና ሲረጭ የነበረው ቅስቀሳ ሲግም፣ ጃዋር የሚመራው የኦሮሚያ እንቅስቃሴ አበበ። ጃዋር ” መንግስት ነኝ” እስከማለት በደረሰበትና ራሱን ” ከተነካሁ ኦሮሚያ ትናጋለች” በሚል የተጽዕኖ ዙፋን ያስቀመጠው ጃዋር ” የአንድነት ሃይሎች ከዱኝ” ሲል እስር ቤት ሄዳ ለጠየቀችው የዩቲብ ሰራተኛ ( ይህን የጃዋር ቅሬታ እስር ቤት ሄዳ እንደነገራት ለሶስት ወዳጆቿ ከአንድ መጽሄት አዘጋጅ ጋር ሆና መናገሯን ማስተባበል አይቻልም) አስፈላጊ ሲሆን ዝርዝሩ ይቀርባል።

ከትህነግ የዲጂታል ወያኔ መጥንሰሻ ጋን ውስጥ የሴራ ጥንስስ እየተጋቱ፣ ላይ ላዩን ተቃዋሚ፣ ውስጥ ውስጡን ቅምጥ ሆነው በቅብብልና ” በሳቢና ገፊ” ስልት ኢትዮጵያን አሳሯን ሲያሳዩዋት የከረሙ ሃይሎች በክልል ፓርቲዎችና በፌደራል መንግስት ውስጥም እጃቸው በስፋት ስላለ ያሳደሩት ተጽዕኖ ዛሬ ላይ ካልተረሳ በስተቀር ታሪክ የሚረሳው አይደለም።

በሚያስገርም ተዓምር በባዶ የጸጥታ ሃይል ይህን ሁሉ ጉድ ያልፈው የኢትዮጵያ ህዝብ፣ ዛሬ ላይ ሳይፈስር መገኘቱ ለሚገባቸው ሁሉ የምስጋናቸው መጀመሪያ በሆነ ነበር። ራሳቸው አሲረው፣ ራሳቸው ገድለው፣ ራሳቸው ሰቅለው፣ ራሳቸው አፍነው፣ ራሳቸው አግተው፣ ራሳቸው ወግረው፣ ራሳቸው አፈናቅለው፣ ራሳቸው ዘርፈውና ንብረት አቃጥለው በቅጽበት የራሳቸውን ተግባሮች በሚዲያ በማሰራጨት ህዝብ ” ቁጣ” በሚባለው አቅልን የሚያስት ስሜት ውስጥ እንዲገባ ምን ያልተፈነቀለ ድንጋይ አለ? ካልተረሳ በስተቀር በኢትዮጵያ ምድር ምን ያልሆነ አለ? ከክፉ ድርጊቶችና የጭካኔ ተጋባራት ከሚባሉት ውስጥ ምን ያልተፈጸመ አለ? አሁንም ካልተረሳ በስተቀር!!

ጥጋብ አይነ ልቡናውን የደፈነበት ትህነግ የዛሬን አያድርገውና ለመካሪና ለአስታራቂ አልመች ብሎ፣ “ወግዱልኝ” በማለት ሽምግልናን አቃሎ በትዕቢት አቡሸማኔ ሰገር። በታወረ ፖለቲካው የሞላቸውን ህጻናትና አዋቂዎች አሰማርቶ አገር አንተበ። ሃብት አወደመ። ህዝብ ጨረሰ አስጨረሰ። ምንም የማያገባቸውን ሰላዋዊ ዜጎች ቤታቸው ድረስ ሄዶ በወረራ ገደለ፣ ዘርፈ፣ ደፈረ፣ ተቋማትን አወደመ። ይህ እብሪቱ ህዝብን አስቆጣ። ህዝብ “እምቢ” ብሎ ከዳር እስከዳር ተነሳ። እንዳይሆን ሆኖ ነተበ። የጋለበበት አቡሸማኔ የተሰኘው እብሪቱ ወላለቀ። ሃፍረቱን ተቀብሎ ዛሬ ” ለምን አስገደልከን፣ ከሃጂ ነህ” በሚል ማንቁርቱን የተያዘ የደም ባለዕዳ ሆነ። እዚህ ላይ ትግራይ ውስጥም ህግ በማስከበርና ወረራውን በመቀልበስ ታላቅ ዘመቻ ውስጥ ተሳታፊ የነበሩ የሰሩት ክፉ ተግባር እንዳለ አይካድም።

ዛሬ ትህነግ ሲተነፍስና ያ ሁሉ ቅዠቱ ሲተን፣ አዲሱ ስልት የሆነው እነ ዳዊት የሚጠነሡት የመጨረሻ ሙከራ በሃይማኖት ስም የተከፈተው የማጫረሰ ዕቅድ ነበር። “አዋቂ” የሚባሉት ሳይቀሩ አቅላቸውን ጥለው ተተኳሽ ጥይት ሊሆኑ ጥቁር እየለበሱ ምስኪኑንን ወጣት ወደ ሞት ሊነዱት ወጡ። ቀንና ሰዓት እየቆጠሩ መርዝ የሚረጩ የሴራ ብልቃጦችም አዋራቸውንና ጋራባቸውን እያራገፉ ” ግደል ተጋደል” ዘፈኑ። እየፈረሙ “ተነስ” ሲሉ በማህበራዊ ገጾቻቸው ተጣሩ። በዝሙትና አረቄ ሰፈር የሚታወቁት ሳይቀሩ ” እኔ …” እያሉ የእልቂት ቅስቀሳና አቀጣጣይ ሆኑ። “ቤተመንግስት ውረር፣ የጋላን መንግስት አስወግድ” ብለው አዲስ አበባን በደም ሊያጨቀዩ የተነሱ ሁሉ በዘመቻቸው ላይ በረዶ ሲዘንብ ተበሳጩ። አንዱና ዋናው ሻለቃ ዳዊት አውስትራሊያ ሄደው ያቀረበው የተስፋ መቁረጥ ምልክት የሆነው ንግግራቸው ምስክር ነው። መቋሚያ ይዞ ሃጤያትን በሚናዘዙበት እድሜያቸው ህዝብ ለማባለት ቀደም ሲል በኤርትራ የቀይ ኮከብ ዘመቻ ወቅት ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ መትጋታቸውን ሰዎች ለምን በዛ ስብሰባ ላይ እንደማይጠይቋቸው ለዚህ ጸሃፊ ግልጽ አይደለም። እሳቸው እድሜ በሚያስከትለው መጃጃት ቢዘነጉም በመፈንቅለ መንግስት ስም ያለቁት ጀነራሎች እንዴት ለሻዕቢያና ወያኔ ስልጣን መያዝ አመቺ ሁኔታ እንዲፈጠር ሆን ተብሎ ተብሎ እንዲከሽፍ ተደርጎ የተዘጋጀና እሳቸው የመሩት ስለመሆኑ ይህ ትውልድ አይረሳውም። ምስክሮችም አጋልጠዋል። እሳቸውም ጎልጉልን ያንብቡ ለኢሳት ሱዳን ድረስ እየሄዱ መፈንቅለ መንግስቱን ይከታተሉና ግንኙነት ያደርጉ እንደነበር ለሲሳይ አጌና በሰጡ ቃለ ምልልስ አልሸሸጉም።

እንግዲህ አስቡት ግንቦት 8 ቀን 1981 እንዲከሽፍ ተደርጎ የተከወነው መፈንቅለ መንግስት የበላቸው አስከሬናቸው እንደውሻ አስመራ አደባባይ የተጎተተው ጀነራል ደምሴ ቡልቶን ጨምሮ 1/ ሜ/ጀ ኃይሉ ገ/ሚካኤል – የምድር ጦር አዛዥ፣ 2/ ሜ/ጀ አለማየሁ ደስታ -የምድር ጦር ምክትል አዛዥ 3/ ሜ/ጀ ወርቁ ዘውዴ – የፖሊስ ሰራዊት ጠቅላይ አዛዥ፣ 4/ ሜ/ጀ ዘውዴ ገ/የስ – የ603ኛ ኮር ዋና አዛዥ፣ 5/ ብ/ጀ ሰለሞን በጋሻው – የአየር ኃይል ምክትል አዛዥ፣ 6/ ብ/ጀ ደሳለኝ አበበ – የጦር ኃይሎች አካዳሚ ዋና አዛዥ፣ 7/ ብ/ጀ ተስፉ ደስታ – የአየር ኃይል ዘመቻ መምሪያ ኃላፊ፣ 8/ ብ/ጀ እንግዳ ወ/አምላክ -የ606ኛ ኮር ዋና አዛዥ፣ 9/ ብ/ጀ ገናናው መንግስቱ – የ6ኛ አየር ምድብ ዋና አዛዥ፣10/ ብ/ጀ ነጋሽ ወ/የስ – የ608ኛ ኮር ዋና አዛዥ፣ 11/ ብ/ጀ እርቅይሁን ባይሣ -የ607ኛ ኮር ዋና አዛዥ 12/ ብ/ጀ ተስፋዬ ትርፌ – የዘመቻ መምሪያ መኮንን፣ ነብስ ይማር። የአገራችን ሚዲያዎች እንዲህ ያለውን ጉዳይ መርምሮ እርቃን ማውጣት ሲገባቸው የተጠመዱት በተቃራኒው መሆኑ ምንአልባትም በአንድ ወቅት ተጠያቂ የሚያደርጋቸው ይሆናል የሚል ዕምነት አለኝ። ኢትዮጵያ እንዚህ ጀነራሎች ባጣች ማግስት የገንጣይና አስገንጣይ ወረበሎች እጅ ወደቀች። ከዚህ ስብራትና ቁጭት ይልቅ የዚህ ስብራትና ቁጭት ተዋንያኖችን የሚያደንቅና እነሱ ስር ተደራጅቶ አገር የሚያተራምስ መንገድ ተመረጠ።

ለሁሉም ግን “አገር ሊያፈርስ ነው” የሚባለው የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ መንግስት ከነ ሙሉ ጥፋቱና ግብስብሱ ውዳሴ የሚገባቸውን ተግባራት መከወን የቻለው በዚህ ሁሉ ጣጣ ውስጥ ሆኖ ነው። ዛሬ ባዶ የነበረው የኢትዮጵያ የጸጥታ ተቋም ፈርጣማ መሆኑንን ተከትሎ፣ እብሪተኛው ትህነግ ወደፊት በትግራይ ህዝብ የሚደርስበት ዕጣው እንዳለ ሆኖ ለጊዜው ” አርፌ እቀመጣለሁ፣ ማሩኝ፣ ጨዋ ክልል እሆናለሁ” ማለቱን ተከትሎ በየክልሉ ያሉ ታጣቂዎች እንደሚከስሙ መሰማቱ በግል ኢትዮጵያ ሰላሟን የማስፋት ዳርዳርታ፣ እንደ አገርም ቅርጿን የመመለስ ውዝዋዜ እያሳየች እንደሆነ ይሰማኛል።

ከመከላከያና ከተራ ፖሊስ በስተቀር ሁሉም አካላት መሳሪያ እንዲያወርዱ የተጀመረው ስራ ለኢትዮጵያ ሰላምን ለሚመኙ ወገኖች ሁሉ መልካም ዜና መሆን ሲገባው በተቃራኒ ሁሉም ክልል ሳይሆን የተወሰኑቱ የራሳቸውን ታላቅ ሃይል መገንባት አለባቸው የሚለው ጩኸት መዳረሻውን መረዳይ ያዳግታል። በተገነባው ዘመናዊ የአገር መከላከያ ስር የሚገባው ገብቶ፣ ሌላው ወደ መደበኛ ህይወቱ እንዲመለስ ማድረግ ነውር የሆነበት አግባብ መከላከያን ከመናቅ፣ ከመጥላት ወይም ካለማመን ስለመሆኑ ደፍረውም አይገልጹምና ልለፈው።

አገር ለማጥፋት እንደሚሰሩ የሚታሙት አብይ አህመድ ” አገር መበተን ካስፈለገን ለምን እንዲህ ያሉ ታላላቅ ተቅማትን እንገነባለን?” እንዳሉት ምላሹን መስጠት ያለበት ሰክኖ የሚከታተለው ዝምተኛው አብዛኛ ክፍል ነው። እውነት ግን አገር መበተን አጀንዳው የሆነ መሪ ለምን ጦር ሜዳ ዘመተ? ለመን ታላቅ አየር ሃይል ገነባ? ለመንድን ነው ባህር ሃይል የገነባው? ለምንድን ነው የዘመነ የደህንነትና የመከላከያ እንዲሁም የፖሊስ ሃይል በአጭር ጊዜ ያበቃው? ለምንስ ነው የህዳሴ ግድብን ለማስፈጸም የተጋው? … ብዙ ጥያቄዎች አሉ። መመርመሩ መልስ ይሰጣል። ሁሉ ሳይሆን ሲቀር ህዝብን በሚመገበው ምግብ ለመቅጣትና ለአመጽ ለማነሳሳት የተጀመረው ዘመቻና የአሻጥር ኢኮኖሚ …. አክሉበት።

ታጣቂዎችን ትጥቅ የማስፈታቱ አጀንዳ በፓርቲ ውሳኔ ያገኘና ሁሉም ክልሎች የተስማሙበት ለመሆኑ ሰሞኑንን የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ይፋ አድርገዋል። ህግ ማስከበር ስራ ላይ በቀጣይ እንደሚሰሩም ተናግረዋል። ከነፍጥና ጦርነት ምንም የሚገኝ ነገር እንደሌለ ” በተግባር አይተነዋል” ሲሉም የታጣቂዎችን ችግር አስምረዋል። ተረኛው የሰሞኑ ተሰዳቢ እሳቸው እንደሆኑ ጥርጥር ባይኖረኝም አፈጻጸሙን የሚያስቆም ሃይል እንደሌለ ምልክቶች አሉ። መከላከያም ለዚህ ውሳኔ የማይገዙትን እንደለመደው ማስተንፈስ እንደማይከብደው ስራውን የሚሰሩት ሲናገሩ እየሰማንም ነው።

ትጥቅ ማስፈታቱ ብቻ ሳይሆን ጎን ለጉን በኤርትራም የዴሞክራሲ አተገባበር ግድ እንደሚል መንግስት ምክር መስጠቱ ተሰምቷል። ባለኝ መረጃ ኤርትራ በዚህ መልኩ ተዘግታ ለትቀጥል አትችልም። ኢትዮጵያ ቀደም ሲል በመለስ ዜናዊ ሴራ እንዳታጣ የተደረገችው አፋር ምድር ላይ የሚገኘውን የአሰብ ወደብ የመጠቀም መብቷ፣ ከዛ ሲያልፍም የባለቤትነት ጉዳይ ማንሳት የምትችልበት ቁመና ላይ መቃረቧ በኤርትራ በኩል ስጋት እንደሆነ ይታወቃል።

የኢትዮጵያ መንግስት ወታደራዊ ሃይል መጎልበት፣ ከትህነግ ጋር የተደረሰው ስምንነትና የውስጥ መረጋጋቱ ኢሳያስን እንዳሳሰባቸው በርካቶች ያምናሉ። በረባውም ባልረባውም ጉዳይ ” ይህ ህገ መንግስት እንደማይጠቅም ለወያኔ መሪዎች ነገሪያቸው ነበር” በሚል በተቆርቋሪነት የሚናገሩት የኤርትራ ፕረኢዚዳንት፣ ትህነግን ከጅምሩ አምጠው እንደወለዱትና ፋፋ እየቀለቡ አዲስ አበባ እንዳደረሱት ለሚያውቁ ንግግራቸው ” ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ” አይነት ነው።

ላለፉት አራት አስርት ዓመታት ስልጣንን ያለ ምርጫ በብቸኝነት የያዙት ኢሳያስ፣ አሁን ላይ የቀድሞው አካሄዳቸው ብዙም እንደማይጠቅማቸው እየተሰማ ነው። ኢትዮጵያ ከሱዳን ጋር አሁን የደረሰችበት ወዳጅነት፣ የውስጥ ፖለቲካው መስከንና አድመውባት ከነበሩት አሜሪካና አውሮፓ አገራት ጋር ዳግም ወደቀድሞው ወዳጅነት መመለሷ ኢሳያስን ባይስደስትም ስጋታቸውን እንዳጎላው ማሳያው ከትህነግ ጋር የተደረገውን ስምምነት መንቀፋቸው ነው።

በአትላንቲክ ካውንስል የአፍሪካ ማዕከል ምክትል ዳይሬክተር የሆኑት ብሮንዊን ብሩቶን በለውጡ ሰሞን  Ethiopia and Eritrea Have a Common Enemy ህወሃት የኢትዮጵያና የኤርትራ የጋራ ስጋት መሆኑን ነው። ስጋት የሚሆነበትን ምክንያት በመዘርዘር የቀረበውን ይህንን መነበብ የሚገባውን ትንታኔ ጎልጉል፤ የድረገጽ ጋዜጣ ወደ አማርኛ መልሶ እንደሚከተለው አቅርቦታል። ትርጉሙ ቀጥተኛና ተዛማጅ የትርጉም ስልትን የተከተለ መሆኑ እንዲታወቅልን እንፈልጋለን።

ጸሃፊይዋ ያቀረቡትን አመክንዮ ባማስታወስ አሁን ላይ ትህነግ የሻዕቢያ ስጋት ካልሆነ ስለምን ከኢትዮጵያ ጋር ግልጽ የንግድና የወደብ ስራ ስምምነት አይደርጉም የሚል ጉዳይ እየተነሳ ነው። አሰብን ኩሬ ያደረገው የኢሳያስ ፖሊሲ አሁን ባለበት መልኩ ሊቀጥል እነድማይችል የሚናገሩ ባለሙያዎች 120 ሚሊዮን ህዝብ ያላት አገር መሪ ስታገኝ የተቆለፈባትን ቁልፍ ታስከፍታለች በሚል ቀደም ሲል አስተያየት ሲሰጡ የነበሩ እንዳሉት አሁን ላይ ያ ጊዜ የደረሰ ይመስላል።

ለዚህ ይመስላል ሁልጊዜ ኢትዮጵያን የሚወጉ ተቃዋሚዎችን በመሸሸግና በማስታጠቅ ስትራቴጂ የኖሩት ፕረዚዳንት ኢሳያስ በተለይ ከአማራ ክልል ጋር ልዩ ወዳጅነት ለመፍጠር ደፋ ቀና ሲሉ የሚታዩት። ይህ የነበረው ልምድ የሚያስረዳን ዕውነት ሲሆን ዛሬ ላይ እሱም የከሸፈ መሆኑ እየተሰማ ነው።

እጅግ ተዋዶና ተዛምዶ የሚኖረው የኢትዮጵያና የኤርትራ ህዝብ የክፉ ፖለቲካ ሰለባ ሆነው የኖሩት በጠላትነት፣ በጨቋኛና ተጨቋኝ ትርክት እንዳልሆን በቅርቡ በሩ ሲከፈት የታየው የህዝብ ስሜትና ዕምባ ምስክር ነው። ይህን ግንኙነት ማሳደግ አንድ ነገር ሆኖ ሳለ መልሶ እንዲደበዝዝ ሆኗል። የትህነግ ክፋትና ሴራ ለተጀመረው ወዳጅነት መላዘብ ምክንያት ቢሆንም አሁን ላይ ያ ስጋት ከሌለ ወደ ቀጣይ ኢኮኖሚያዊ መተሳሰር ማምራት ያልተፈለገበት ምክንያት ወይም እንቅፋቱ አይገባኝም።

በዚሁ መነሻ አካባቢዬንና ቅርብ ናቸው የምላቸውን ወገኖች ሳወያይ ያገኘሁት ነጥብ ” ዛሬ ላይ እንደቀድሞው ሳይሆን አብይ ሊኢሳያስ አስፈላጊ ናቸው” የሚለው ትንተና ውሃ እያነሳልኝ ነው። ቀደም ሲል ገና በልጅነቱ ሊበላ የነበረው ለውጥ ሲውተረተር ኢሳያስ ለአብይ አስፈላጊ ነበሩ። አሁን ባለው ወቅታዊ የፖለቲካ ስሌት የአስፈላጊነቱ ቀመር ተቀይሯል።

በዚህ ምክንያት ይመስላል ኤርትራ የአስተሳሰብ ለውጥን እንድትመለከት፣ በተራ የኮንትሮባንድ አስተላላፊነት የተሰማሩም እጃቸውን እንዲሰበስቡ መንግስት ምክር ሰጥቷል። በማህበራዊ ሚዲያ በሚፈጠር ጫጫታ መንግስት የዛለ ለሚመስላቸው ” አየር ጨብጦ አሁን ያለውን መንግሥት ከሥልጣን ልቀቁ አይሆንም” ሲሉ ከተቀነባበረውና ከሚናበበው የሴራ ሰፈር የተሰጠን አጀንዳ ጠቅለል አድርገው የመለሱት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ሶስት ከፍተኛ የሚባሉ የጦር መርከብ ባለቤት የሆነ፣ ከዝመነው የአየር ሃይል ጋር የተሳለጠ የባህር ሃይል አዘጋጅተው የህንድ ውቅያኖስ ላይ ብቻ ሳይሆን በቀይ ባህርም የኢትዮጵያን አቅም መትከል ፍላጎታቸው በቅርቡ ዕውን እንደሚሆን በብዙ ምክንያቶች እንዳምን ተገድጃለሁ።

” የመናደርገውን የሚያውቁት ጠላቶቻችን ናቸው” የሚሉት አብይ አህመድ እንዲህ ያለ ራዕይና እምነት ይዘው ሳለ “አፍራሽ፣ አገር አጥፊ” ተብለው የሚፈረጁበት አግባብ የማይገባኝና ሳስበው የሚያጥወለውለኝ ለዚህ ነው። ሌሎችም ብዙ ምክንያቶች አሉ። ዞሮ ዞሮ አሁን ነገሮች መስመር እየያዙ፣ ኢርቶጵያም ቅርጿን ልትይዝ እየተንደረደረች እንደሆነ ይሰማኛል። ሟርት አብቅቶ ጨዋ የፖለቲካ ከሚናፍቁ ዜጎች መካከል አንዱ ነኝ፤

ሰበልው ወርቅ ሃይሉ አዲስ አበባ

ዝግጅት ክፍሉ – ጽሁፉ መጠነኛ የአርትዎት ስራ ከመደረጉ በቀር ሙሉ አሳቡ የጸሃፊዋ ነው።

Exit mobile version