Site icon ETHIO12.COM

“ውሳኔውን በመርህ ደረጃ የተቃወመ አላየሁም” ቹቹ አለባቸው

እስካሁን ባለኝ ትዝብት ማናቸውም ኃይል በመርህ ደረጃ የመንግስትን ውሳኔ ሲቃወም አላየሁም። ይህ ትልቅ ፀጋ ነው። እኔም ውሳኔውን በመርህ ደረጃ ከተቀበሉት ወገን ነኝ። ልብ ላለው አመራር እንዲህ አይነት ውሳኔ ቢያንስ በመርህ ደረጃ ተቀባይነት ያገኘበትን ምክንያት በሚገባ መርምሮ የስራ መመሪያ ያደርገዋል።

ጥሪ ለአማራ ክልል አመራር!

Chuchu Alebachew ነጻ አሳብ

የማዕከላዊ መንግሥት የሁሉንም የክልሎች ልዩ ኃይሎች አደረጃጀት በማፍረስ ወደ ፌዴራል እና መለስተኛ የክልል የፀጥታ ተቋማት እንዲካተቱ ወስኖ እንቅስቃሴ ውስጥ መግባቱ እውን ሁኗል።

የአማራ ክልል ኮር አመራር ደግሞ የዚህ ውሳኔ አካል ነው። የብልጽግና ሥራ አስፈፃሚን ውሳኔ በማስፈፀም በኩልም ትልቁ ኃላፊነት ሆኖ የወደቀው የክልሉ ኮር አመራር ላይ ነው። በተለይም የሰመረ የሕዝብ ግንኙነት ስራ በመስራት የልዩ ኃይል አባላትንና የአማራን ህዝብ በማሳመን በኩል።

የፌደራሉ መንግሥት ከደጋፊነት በዘለለ ስምሪት የወሰደባቸው አካባቢዎች ስለመኖሩ ይሰማል። ይሄንን አጀንዳ በሰመረ መልኩ በማስፈጸም በኩል ግን ዋነኛው ኃይል የአማራ አመራር ስለመሆኑ ነው መረጃዎች የሚያሳዩት።

እስካሁን ባለኝ ትዝብት ማናቸውም ኃይል በመርህ ደረጃ የመንግስትን ውሳኔ ሲቃወም አላየሁም። ይህ ትልቅ ፀጋ ነው። እኔም ውሳኔውን በመርህ ደረጃ ከተቀበሉት ወገን ነኝ። ልብ ላለው አመራር እንዲህ አይነት ውሳኔ ቢያንስ በመርህ ደረጃ ተቀባይነት ያገኘበትን ምክንያት በሚገባ መርምሮ የስራ መመሪያ ያደርገዋል።

ይሁን እንጅ ምንም እንኳን በሌሎቹ ክልሎች ያለው ሁኔታ እንዴት እየሄደ እንደሆነ መረጃ ባይኖረኝም (የለገሰና ሰላማዊት መረጃ ተጨማሪ ማመሳከሪያ የሚጠይቅ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ) በአማራ ክልል አንፃር ግን ድርጊቱ የፀጥታ ውጥረት እየገጠመው ስለመሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ። በተወሰነ ደረጃ መንግስትም እውነታውን እየገለጠው ነው።

አሁን ጥያቄው ይሄ አገራዊ እና በመርህ ደረጃ ተቀባይነት ያገኘ አጀንዳ ወደገቢር ሲገባ አማራ ክልል ላይ ለምን ሳንካ ገጠመው የሚል ነው። መፈተሽ ያለበት ጥያቄ ይህ ነው።

በእኔ እምነት አጀንዳውን (የልዩ ኃይልን መበተን) ውሳኔ ለመቀበል የተቸገረው ከአማራ ልዩ ኃይል አባላት የበለጠ የአማራ ሕዝብ ነው። እዚህም ላይ ለምን የሚል ጥያቄ ማንሳት አስፈላጊ ነው።

ለሁሉም የአማራ ልዩ ኃይልም ሆነ የአማራ ሕዝብ ይሄንን ወቅታዊ አጀንዳ ለመቀበል የተቸገሩት ጠመንጃ ነካሽ ሆኖ የመቀጠል ሱስ ስላለባቸው አይደለም፤ ይልቁንስ ገና ያልተመለሱ ጥያቄዎችና የህልውና ስጋት አለብን ብለው ስለሚያምኑ እንጅ። በተለይም አማራን በጠላትነት የፈረጀውና ሒሳብ እንደሚያወራርድበት ያቀደው ሕወሓት እንደገና ወታደራዊ መንግሥት መስርቶ በተጠናከረበት ወቅት የአማራ ልዩ ኃይል ይበተን የሚለውን አጀንዳ ለመቀበል የአማራ ሕዝብና ልዩ ኃይሉ አጀንዳውን ተቀብለው ለመተግበር መቸገራቸው ሊደንቀን አይገባም።

የአማራ ሕዝብ እነዚህ መሰል ጥያቄዎቹ ከተመለሱለትና ‘የህልውና ሰጋት የለብኝም’ ብሎ ካመነ ክላሽና ምንሸር ተሸክሞ ውሎ የሚያድርበት ምክንያት የለውም።

ይሄንን እውነታ አይደለም የአማራ ልዩ ሀይል የአማራ ፋኖ ጭምር እንደሚጋራው እምነቴ የፀና ነው።

ስለዚህ አሁን ላይ የተያዘውን አገራዊ አጀንዳ አማራ መሬት ላይ ለመተግበር ሳንካ እየገጠመው ያለው ከላይ ባነሳሁዋቸው ምክንያቶች በመሆኑ፣ አጀንዳው በሰመረ መልኩ ሊተገበር ከተፈለገ ለእነዚህ ጥያቄዎች በቂ ማብራርያና ምላሽ በመስጠት ሊሆን ይገባል እላለሁ።

መፍትሔ:-

1. የፌደራሉ መንግስት፣

ስለሂደቱ ታማኝነት ያለው ግልፅ መረጃ ቢሰጥ ይመከራል። አጀንዳው እውነትም በሁሉም ክልሎች በእኩልነት እየተተገበረ ሰለመሆኑ የሚታይ መረጃ ማቅረብ ቢችል ጠቃሚ ይመስለኛል። በዚህ ረገድ ከፖለቲከኞች ይልቅ የመከላከያ ወታደራዊ ካውንስል ኃላፊነቱን ወስዶ እንደፌዴራል የፀጥታ ተቋም ማብራሪያ ቢሰጥ ይመከራል።

በሌላ በኩል በፖለቲካ አመራሩ በኩል፥ የወሰንና ማንነት ጥያቄዎች ሊፈቱበት ስለታሰበው መንገድ ግልፅ መረጃ መስጠት እጅግ ጠቃሚ ነዉ ብየ አምናለሁ።

ነገሮችን በትዕግስት መያዝ። ነገር ከልኩ ላያልፍ መቸኮል አያስፈልግም። በውይይት የማይፈታ ነገር የለም። ስለሆነሞ በተለይም የኃይል አማራጮች እንዳይኖሩ ብርቱ ጥንቃቄ ቢደረግ መልካም ነው።

2. የአማራ ክልል አመራር:-

ወደታች ወርዶ የልዩ ኃይል አባላትንና ሕዝቡን ማወያየት ይገባል። ይሄንን ያክል ግዙፍ አጀንዳ በወረዳና ዞን አመራር ለማስፈጸም መሞከር የፖለቲካውን ጡዘት ያለማስተዋል ጉድለት አድርጌ እወስደዋለሁ። በካድሬ የሚፈታ ትጥቅ ስለመኖሩ ማመን ይቸግራል። የነገሩን ሥረ-ምክንያት ልብ ብሎ ማጤን ይመከራል። በዚህ ረገድ የኮር አመራሩን የቅርብ አመራር ማረጋገጥ ይጠይቃል። የመውጫ ስትራቴጂያዊ መላዎችን ከመዘየድ አልፎ የውሳኔ ሀሳቡን ከጊዜው ሁኔታ አንፃር ዳግም እንዲፈተሽ በጎ ጫና ማሳደርም ብልህነት ነው።

በሌላ በኩል ልዩ ኃይሉ ይበተን ሲባል የወሰን ጥያቄዎችና የአማራ ህዝብ ያደረበት የህልውና ስጋት እንዴት ሊመከት እንደታሰበ በቂ መረጃ መስጠት ይገባል።

እነዚህ ጥያቄዎች ላይ ግልፀኝነት ካልተፈጠረ ልዩ ኃይሉም ሆነ ሕዝቡ ግራ ቢጋቡና አገራዊ አጀንዳውን ለመቀበል ቢቸገሩ አያስገርምም። እነዚህን ብዥታዎች የማጥራት ጉዳይ የኮር አመራሩ ሥራ ነው።

መቼም፣ ይህን ጉዳይ ለማጥራት ኃላፊነቱን ለወረዳና ለዞን ካድሪ ማውረድ የ “ትኩስ ድንች” ፖለቲካን ከማስታወስ የዘለለ ፋይዳ የለውም። እናም የክልሉ አመራር በዋናነት ኮር አመራሩ የበዛ ኃላፊነት አለበት።

3. ለአማራ ሕዝብ በአጠቃላይ!

ፋኖሞ ሆነ ወጣቱ በምንም ታዓምር ከመከላከያ ጋር ሰጣ ገባና ግጭት ውስጥ መግባት የለበትም። ወደዚህ ኃይልን ወደቀላቀሉ ድርጊቶች ከሚያመሩ ማናቸውም ድርጊቶች መራቅ አለብን። ሰራዊቱ የፖለቲካ አመራሩን ውሳኔ ነው የሚያስፈፅም። ስለሆነም ይሄንን የሕዝብ ልጅ ላለማስቀየም የቻልነውን ያክል ሁሉ እንጣር።

በትላንትናው ዕለት ደቡባዊ የጎንደር ቀጠና በደብረ ታቦር ላይ የነበረው መፋጠጥ በአዋቂዎች ብልህነት ነገሩ መርገብ በ’ጀ እንጂ ሁኔታዎች መልካቸውን ሊቀይሩ እንደነበር እግር ጥሎኝ ታዝቤለሁ። በዚህ አጋጣሚ የማማው ደብረታቦር ብልሆችና የመከላከያ ሰራዊቱ አባላት ምስጋናየ ይድረሳችሁ። ይህ ተሞክሮ በሁሉም የክልሉ ከተሞች ሊሰፋ ይገባል። እኛም እናግዛቸው።

የአማራ ወጣት ደግሞ ትዕግስትና አሰተውሎት ይኑራችሁ። በትግላችሁ የመጣ ለውጥ ነውና በሰላማዊ ትግላችሁ ይታረማል። የአማራ ሕዝብ ጥያቄ ሕጋዊና ሰላማዊ በሆነ መንገድ ምላሽ እንዲያገኝ ከመታገል ውጭ ሌላ አማራጮችን ለመከተል አንሞክር። ሌላ አማራጮችን መከተል ሕጋዊና ተገቢነት ያላቸው ጥያቄዎችን እንዲዳፈኑ/እንዲታፈኑ ሊያደርግ ይችላል። ስለዚህ ትግላችሁ ሁሉ ሰላማዊ፣ ሕጋዊና ስክነት የተሞላበት ሊሆን ይገባል።

4. የአማራ ጉልሃን-ልሂቃን (በተለየ)

አሁን ባለው ሁኔታ አጀንዳው ከልዩ ኃይል አባላት ወጥቶ የሕዝብ የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው። ስለዚህ ክልሉ ወደአደገኛ የጦርነት አውድማ ከመግባቱ በፊት ዳፋዉ ለአገርና ለቀጠናው እንዳይተርፍ ወደ ሕዝቡ ወርዶ ማስተማር፣ የአማራን ሕዝብ እውነተኛ ጥያቄዎች መንግሥት እንዲመልስ፣ ግልፅ ያልሆኑ ጉዳዮችን ግልፅ እንዲያደርግ በማድረግ በኩል ግንባር ቀደም ሆኖ ስላማዊ ትግል በማድረግ ሚናችንን ልንወጣ ይገባል። ልሂቃን በዚህ መሰል የጭንቅ ጊዜ ለመቶ ዓመት አልመው ማሰብና መንቀሳቀሱ የግድ የሚሆነው ከቀደሙት አባቶቻችን

ብልህነት መውረስ ሲቻል ነው። መስከን፣ ማሰላሰል፣ መተንተን፣ መተግበር የዘመኑ ሰላማዊ የትግል መንፈስ ነው።

ሰላም ለኢትዮጵያና ሕዝቦቿ

Exit mobile version