ETHIO12.COM

ማን ነው ቀውስ የሚጠምቅልን? ከቀውሱ ብሁዋላስ? አዲስ አበባ መርዝ ታቅፋለች

ትርምሱ እንጂ ከትርምሱ በሁዋላ ምን፣ እንዴትና፣ በነማን አማካይነት ማረጋጋቱ እንደሚከናወን በውል ሳይቀመጥ በገፊና ጎታች ትርክት ተናበው የሚንጡን ቅርንጫፋቸው ውጭ፣ ስራቸው ደግሞ አዲስ አበባ ነው። አዲስ አበባ መርዝ ታቅፋ መሽቶ ይነጋባታል። ኮንትሮባንዲስቶች ብር ያጥባሉ። የፍራንኮ ቫሉታ እድልን በመጠቀም ኢትዮጵያን የሚያልቡት ” የነጻነት ቀን አክባሪዎች” እና ወዳጆቻቸው ሁመራን እያሳረሱ ነው። አዲስ አበባ ሆነው ወደብ እያስተዳደሩ ነው። አዲስ አበባ ምስኪኖች የሚጸልዩላትን ያህል ዋና ዋና ሌቦች ደግሞ እያለቧት መልሰው መርዝ ያስረጫሉ። ያልገባቸው መርዛቸውን ይጠጡላቸዋል። ይህ ሁሉ የሚታወቅ ነው። ተቆርጦ እንዳይጣል አገር መርጋት አለባት። እንዳይቆረጡ አገር እንዲረጋ አይፈለግም። ህዝብ ቁጣ ውስጥ እንዲገባና በቁጣ አስቦ በስሜት እንዲመራ፣ በምሬትና ብስጭት የዓላማቸው አስፈጻሚ እንዲሆን የሚደረገው እንዲህ ባሉ ማጅራት መቺዎች ነው።

እንደ ተከታታይ ፊልም በኢትዮጵያ ምድር ቀውስ መጥመቅ የተለመደ ሆኗል። ድፍን አምስት ዓመት ንጹሃን ዜጎች በሚያውቁትም፣ በማያውቁትም ምንጭ ነውጥና ቀውስ እየተጠመቀላቸው ፍዳቸውን እየገፉ ነው። በጅምላ ሞተዋል። ተሰደዋል። ወድመዋል። ፈርሰዋል። ይህ ሁሉ አላረካ ያላቸው አሁንም ቀውስ እያጋጋሙ ነው። የሆነው ብቻ ሳይሆን እንዲሆን የተፈለገው ግራ የሚጋባና እንቅልፍ የሚነሳ ሆኖ ሳለ እሳቱን ማንቀርቀብ የመረጡ በርክተዋል።

ልብ ላለው በሰከነ አንደበት የአማራ ክልል መሪ ዶክተር ይልቃል ከፋለ ” ማን ነው ይህን ሁሉ የሚያደርገው? ለምን በምርጫ እንድንቀጣ አያደርጉም?” ሲሉ ያቀረቡትን ጥያቄ ቀላል የሚመስለን ካለን ስተናል። ዛሬ በማህበራዊ ሚዲያ ገቢ ያበዱ፣ በማህበራዊ ሚዲያ ተከታይ ያሰባሰቡ ወገኖች፣ ወገናቸው ላይ ምን አጭሰውና ምን ተቀብለው በዚህ ደረጃ እንደጨከኑ ማሰብ ጣዕረ ሞትን የመቧቀስ ያህል ከባድ ነው። እንደውም ለመረዳት ሁሉ የሚያዳግት የግሽበታችን ሁሉ ድምር ነው።

” መንገድ ዝጉ፣ ንብረት አቃጥሉ፣ ሱቅና አገልግሎት መስጫዎችን ከርችሙ፣ ምግብ ቤትና ተራ ቂጣ መሸጫ መደብሮችን አታሰሩ…” የሚለውና በማህበራዊ ሚዲያ ቀጭን ትዕዛዝ የሚያሰራጨው ማን ነው? የሚፈለገውስ ምንድን ነው? ማንስ ነው ዕውቅና የሰጣቸው? የት ነው ማዘዣ ጣቢያው? መሪዎቹስ እነማን ናቸው? የነማን ወኪሎች ይሆኑ? ኦሮሞው፣ ሶማሌው፣ ቤኒሻንጉሉ? አፋሩ? ጋምቤላው? ወላሞው፣ ጋሞው፣ ዶርዜው፣ ሲዳማው፣ ሃረሪው፣ አማራው ዳር እስከዳር … ያውቃቸዋል? አውቆስ ተቀብሏቸዋል? ካልሆነስ እንዴትና እነማን ኢትዮጵያን ከነውጡና ሁከቱ በሁዋላ ያረጋጋታል?

ዛሬ በአገራችን ነጻ መሆን፣ ያመኑበትን ዓላማ ማራመድ፣ መልካምን ጉዳይ መልካም ማለት ወንጀል ነው። በጀታቸው፣ አጀንዳ አሸካሚያቸውና የሚልካቸውን ለማስደሰት ሲሉ ነጻ አሳብ አራማጆች፣ ወይም ለማራመድ የሚሞክሩትን፣ ወይም ለም የሚል ጥያቄ የሚያነሱ ወገኖችን መደብደብ ተለምዷል። ቤተሰብ፣ የግል ህይወት፣ ሚስት፣ ልጅ፣ ዘመድ አዝማድ ሳይቀር በነጻ አሳብ ስም ማዋረድ፣ መፈረጅ፣ ማበሻቀጥ … ለመስማት በሚከብድ ደረጃ የቁም ግድያ መፈጸም ባህል ሆኗል። የሚያሳዝነው እንደዚህ ዓይነቶቹን ሚዛን አላባ የሚዲያ ውስጥ አሳራጆችን ስፖንሰር የሚያደርጉ፣ የሚከተሉና የነሱን የዕርድ ትዕዛዝ የሚያሰራጩ ወገኖቻችን በሽታ የጠና መሆኑ ነው። አንዳንዶቹ የደም ፖለቲካ ውስጥ ገብተው የሚርመጥመጡት እጅግ የሚከበሩና በክርስቶስ ስም የተሸፈኑ ስፖንሰር አድራጊዎች መሆናቸው በታሪክም በትውልድም ዘንድ ይዘከር ዘንድ ቀኑ ሲደርስ ይፋ የሚሆን ነው። አሜሪካ ሚስጢር የለምና!!

የአማራ ህዝብም ሆነ ሌሎች ኢትዮጵያዊያን በርካታ ችግሮች አሉዋቸው። መንግስትም በሁለት ቢላ የሚያርዱትን ተላላኪ ካድሬዎቹን ጨምሮ በሽታው ብዙ ነው። ሌብነቱና ግልሙትናው እጅግ የሚያሳፍር ደረጃ ላይ መድረሱ ክርክር የሚቀርበበት አይደለም። የምናውቃቸው እልፍኝ አስከልካዮች ዝርፊያ ላይ ተሰማርተው አይተናል። ይህም ጊዜውን ጠብቆ ይፋ የሚሆን ነው። ይህን ያልኩት መንግስትን ለመከላከል አስቤ ይህን ጽሁፍ አለማዘጋጀቴን ለማስታወቅ ነው።

ይህን ጽሁፍ ለመጻፍ የውሰንኩት ወ/ሮ ዝናሽ ታያቸው በቀዳማዊ ነታቸው ጽህፈት ቤት አማካይነት ጎንደር የዳቦ ማምረቻ መመረቃቸውን ተከትሎ ሰባት ሰዓት በላይ በፈጀ የዩቲዩብ ፕሮፓጋንዲስት ሲሰደቡ የሰማሁ ዕለት ነበር። እጅግ ልብና ህሊናን በሚፈትን ጠጣር አነጋገር ወይዘሮዋን ሲያደማ የነበረው ሃብታሙ አያሌው ነበር። የዳቦ ቤቱን መመረቅ መቃወም ከምን ስሜት እንደመነጨ ባይገባኝም ሴትየዋን በዛ ደረጃ መስደብ ምን ማለት ነው?


እንትን ምስጥን እበላለሁ ብሎ ሲነሳ …

…. አሁን ላይ በኢትዮጵያ ምስጥ መንግስት ነው ያለው። ምስጥ መንግስት ደግሞ 120 ሚሊዮን ህዝብ ይዞ በነቀዝ አይበላም። በታሪክም ነቀዝ ምስጥን በልቶ አያውቅም። ነቀዝና ምስጥ ከጽሃፊው አሳብና ገለጻ ይተወሰዱ የእብጠት እሳቤዎች ናቸው


ዝናሽ ታያቸው ፖለቲከኛ አይደሉም። የካድሬ አይነት አቋምም ሆነ ጮሌነት አይታይባቸውም። ትምህርት ቤቶች ሲመርቁና በእንግድነት በሚገኙበት ቦታ ሲናገሩ ላድመጠ ጥሩ እናት፣ ሰው መሆናቸውን ከመረዳት በላይ ለሌላ ጉዳይ የሚጋብዙ አይደሉም። “ሁሉም ያልፋል” ብለው በራንድ ጉባኤ ላይ ሲናገሩ እንደሰማሁዋቸው በቤተመንግስት ህይወትም ደስተኛ አይመስሉም። ጠቅላይ ሚኒስትሩን መቃወም፣ መጥላት ወይም አለምደገፍ፣ ፓርቲያቸውን መታገል ሲቻል ሚስታቸውንና ልጆቻቸውን ሰባት ሰዓት ሙሉ መስደብ በቃል ሊገለጽ የማይችል የልቡና ዕውርነት ነው። ከዛም ሲያልፍ ለሃብታሙ ሚስትና ልጆች ልብ ካላቸው ውርደት ነው። ወደ መነሻዬ ልመለስ?

አማራ ክልልን ለማተራመስ የቋመጠው ማን ነው? አሁን የተጀመረው አካሄድ እውን ለምስኪኑ የአማራ ህዝብ ይጠቅመዋል? አማራና ትግሬን አስታርቆ አብሮ መኖሩ ቀላል ሆኖ ሳለ አልፎ ሌላ ሰፈር ገብቶ ነፍጥ ማንሳት ክልሉን ሊያደቅ እንጂ እንዴት ሊያበልጽገው ይችላል?

ሰሞኑን አዲስ አበባ ውስጥ ” የነጻነት ቀን” ሲሉ ያከበሩትን የኤርትራ ጠቅላይ ግዛት ተወላጆች ስመለከት የተሰማኝን ስሜት ለአፍታ ላጋራ። እነዚይ “ነጻ ወጣን” ብለው አዲስ አበባ ላይ የሚደንሱት የኤርትራ ጠቅላይ ግዛት ተወላጆች “ጨቋኝ፣ ቅኝ የያዘች፣ የባርነት ቀንበር የጣለችብን…” በሚሏት ኢትዮጵያ ውስጥ ነው። ቅኝ የያዘውና ወራሪ ሆኖ የተሳለው ደግሞ የኢትዮጵያ ህዝብ ነው። ” ወራሪ ” በተባለ ህዝብ ከተማና ሃብት ” ነጻ ወጣን” እያሉ ይዘፍኑብናል። በግል እንደዚህ አይነት እብለትና የድንቁርና መንፈስ በየትኛውም ዘመን ይታያል የሚል ዕምነት የለኝም። የሚገርመው የዩቲዩብ ገቢና ድርጎ የጋረዳቸው ይህንኑ ዳንስ ሲያሰራጩ ነበር። ይህ እያሰራጩ ሌሎችን በብሄራዊ ስሜት ኮስማናነት ይከሳሉ። ሞራለ ቢሶች።

በምኖርበት ከተማም በተመሳሳይ የፈርደበት የነጻነት ቀን ሲከበር አይቻለሁ። የሰማኒያና የሰባ ዓመት አዛውንቶች ሳይቀር የስደት ማዕረጋቸውን ተከናንበው ” የነጻነት ቀን” ብለው ” እንኳን አብጻኩም” እያሉ ሲቦርቁ ሳይ ” እነዚህ ሰዎች የነጻነትን ፍሬ ያውቁታል?” ስል ጠየኩ። ለመሆኑ የኤርትራ ወድሞቻችን ኢትዮጵያ ውስጥ ሌሎች በሚማሩበት ትምህርት ቤት አትማሩ ተብለዋል? አትነግዱ፣ አትስሩ፣ አትበደሩ፣ አትግዙ፣ አትሽጡ ተብለው ያውቃሉ? ብድር ተከልክለው ያውቃሉ? ከየትኛው የኢትዮጵያ ህዝብ በታች እንዲኖሩ ተደርገዋል? ይህ የኢትዮጵያ አምላክ ይፍረደው ከማለት ውጭ ምን ይባላል? ከህጻን እስከ ሽማግሌ ጥርግ ብሎ ስደት የወጣባት፣ በኡጋንዳ፣ ሲዳን፣ ኬርንያ … አሁንም ስለፍ ላይ ያሉ ዜጎች ያሉዋት አገር ለይትኛው የነጻነት ፍሬ ኢትዮጵያ ላይ ሆነው ኢትዮጵያን ” ወራሪ” አድርገው በዓል እንደሚከብሩ መሳይ መኮንን እንደለመደው አሜሪካ ጎረቤታችን ያለውም ተንታኝ ቢጠይቀው እመክረዋለሁ።

ይህን ያልኩት ያለምክንያት አይደለም። የቀደሙትን አባቶቻችንን ወራሪ በሚል ፈርጆ በተሳሳተና በተጋነነ ታሪክ ሲወጉንና ሲያስወጉን ከነበሩ የሻዕቢያ ቁማርተኞች ጋር ኩሩውን የአማራ ህዝብ መስፋት ምን ለማግኘት ነው? ላለፉት አራት አስርት ዓመታት ምርጫ፣ ህገመንግስት፣ የተለይ አሳብ፣ የሃይማኖት ነጻነት፣ ነጻ ኢኮኖሚ፣ ኢንቨስትመንት … ከማይታየበት የሻዕቢያ መሪዎች የአማራ ህዝብ ምን እንዲያገኝ ተፈልጎ ነው መጣበቁ የተፈለገው? ከሻዕቢያ ጋር ተጣብቆ ኮንትሮባንድ ማጧጧፍ ለምስኪኑ አማራ ምን ይፈይደዋል። በዚህ ጉዳይ ላይ ወደፊት እመለስበታለሁ። የኮንትሮባንዱ ጉዳይና ዶላር አጠባው እንዴት እንደሚሰራ እተርካለሁ። እዚህ ላይ ሻዕቢያና ሻዕቢያን የማይቀበለውን የኤርትራ ህዝብ ነጣጥዬ እነደምመለከት ልብ ይባልልኝ።

ልክ እንደ ፈጣሪው ሻዕቢያ መርዘኛ የሆነው ትህነግ የሚባል ድርጅት የትግራይና የአማራ ህዝብን እሳትና ጭድ ከማድረጉ ውጭ በሁለቱ ህዝብ መካከል ይህ ነው የሚባል የተጻፈና የተሰነደ ጠላትነት እንደሌለ አዋቂዎች መስክረዋል። ትህነግ ዛሬ ላይ በድዱ የሚሄድ በአቋምም ሆነ በአሳብ ያረጀ ድርጅት በመሆኑ ተሻግሮ ማለፍ ያስፈልጋል ባይ ነኝ። ካለፈው መከራ፣ እልቂት፣ ውድመትና ስደት የሚማሩ ዜጎች ስለምን ቁጭ ብለው ስለ ዕርቅ አያወሩም? አማራና ትግሬ መካከል በቀለኞች የረጩትን መርዝ በመጥረግ ሁለቱ ህዝብ ግንባር ቢፈጥር ምን ሊፈጠር እንደሚችል ማስላት ከባድ አይደለምና ሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዩርጊስ የሚባለውን የሻቢያ አገልጋይ አምኖ ከመተራመስ ቀላሉን መነግድ መከተል ይበጃል።

ትግነግን በባንዳነትና ከሃጂነት የፈረጀ ጀግና ህዝብ ለድብቅ የኮንትሮባንድ አስተሳሰብ እጁን እንዲሰጥ ሌት ተቀን የሚሰብኩ ፍልፈሎች፣ ሆዳቸውን አማራው ላይ ጭነውበታል። በዚህ ከርሳቸው ሳቢያ ትናንት ብልጽግና ደጅ ሲንደባለሉና ሲለምኑ በገሃድ እንዳላየናቸው ዛሬ የሻለቃ ዳዊት ተከፋዮች ሆነው መርዝ አከፋፋይ ሆነዋል። መርዙም የሚቀዳው ከየት እንደሆነ ይታወቃል። መርዝ መርጨት ያስፈለገውም ኢትዮጵያ ከረጋች እግፏ ወዴትና እንደሚዘረጋና እጇ በግፍ የተነጠቁባትን ንብረቶቿን የባህር በር ጨምሮ ለመሰብሰብ እንደሚዘረጋ ግልጽ በመሆኑ ነው። ትህነግ ህዳሴ ግድብን ሊያጨናግፍ ከግብጽ ጋር እንደሚሰራ የዛሬው ጌታቸው ረዳ ነግሮን እንደነበረው፣ ሻለቃ ዳዊት የሰራው ወንጀል ሳይንስ፣ ዛሬ በሰማኒያ አምስት ዓመቱ ተቀጥሮ አማራን ከኦሮሞ ጋር ሊያጫርስ አዋጅ አውጇል። ይህ አዋጅ መነሻውም መድረሻውም ጡንቻዋ እየፈረጠመ የመጣውን ኢትዮጵያን በደም አጥቦ ለመፍረካከስ ብቻ ነው።

ዳዊት ሌባ ነው። የዘርፈው ረሃብ ከጠበሳቸው ወገኖች ነው። ተመሳጥሮ የዘርፈው ደግሞ አሁን ከሚላላከለት አካል ጋር ነው። ዳዊት የኢትዮጵያን ምርጥ ጀነራሎች ሆን ተብሎ እንዲከሽፍ ታስቦ በተሰራ መፈንቅለ መንግስት ስም መሪ ሆኖ አስጨርሷል። አስመራ ላይ ጀግኖቻችን አስከሬናቸው በውርደት እንዲጎተት፣ አዲስ አበባ መከላከያ ቢሮ በየስራቻው የውሻ ሞት እንዲሞቱ አስደርጓል። ይህ ወንጀለኛ አዲስ አበባ ሲገባ አስሮ ለፍርድ ማቅርብ የሚገባው ቢሆንም ቤተ መንግስት ዳግም ገብቶ ጨዋትውን ለመጫወት የደፈረ የትልቅ ቀላል ነው። ይህ ሰው ነው እንግዲህ የአማራ ተቆርቋሪ ሆኖ ሁለቱን ህዝብ ደም ሊራጭ በሚዲያና በሰርጎ ገቦች፣ እንዲሁም በሚከፈላቸው መርሰነሪዎች በከፍተኛ ትጋት እየሰራ ያለው።

እጁ ቤተክርስቲያን ዘልቆ ግብቷል። እምነት ተቋማትን መጠቅም ግድ እንደሆነ በገሃድ ያስታወቀው ዳዊት፣ በእስክንድር ነጋ አማካይነት የአማራው ትግል መሪ መሆኑ በይፋ ሲነገር ኢትዮጵያን ማን እየናጣት እንደሆነ ለመረዳት የዳዊትን ዱካ መከተለ በቂ ነው። ሜሪ ላንድ በተደረገ ስብሰባ ኤርሚያስ ለገሰ ከ360 እንዲሰናበት ሲወሰን (የተስብሳቢዎቹን ስም መዘርዘር ለጊዜው አስፈላጊ አይደለም) ስንት ጊዜ አስመራ እንደተመላለሰ ያጫወታቸው አንድ “ትልቅ ሰው” እንደነገሩኝ ከሆነ ዳዊት አጅንዳ የሚሰፈርለት ከዛው ነው። ዳዊት ከዛ የሚሰፈርለትን አጀንዳ ነው እነ እስክንድር ላይ የሚጭነው። ታዲያ እስክንድርም ሆነ ሌሎቹ ተቀላቢ ሚዲያዎች በምን መስፈርት ኢትዮጵያዊ ይሆናሉ? በሚል ጥያቄ ሲያቀርቡ የነበሩ በሃሰት ሲሰደቡና ሲወነጀሉ በሞራቸው ጥፋት እንደነበር ራሱ እስክንድር “ኢትዮጵያ” የሚለውን ጭንብል ሲገፈ ገሃድ ሆኗል። እንደውም “ብሄርተኛ ነህ” ሲባል እያምታታን መልስ ሲሰጥ የነበረው እስክንድር በግል “የአማራ ትግል መሪ ነኝ” ማለቱ አሰላለፉን አጥርቶታል። ካሁን በሁዋላ ” ተያዝኩ፣ ተመታሁ፣ ተተኮሰብኝ” የሚል ሮሮ ማሰማትም አይቻልምና መልካም የትግል ጊዜ ይሁንለት።

ስለ ወቅታዊው መንግስት ከላይ እንዳልኩት ብዙ ጥፋቶች ያሉብት፣ ከምንም በላይ ሁለት ቦታ የሚጫወቱ የህሊና ድሆች፣ ደምና ሃብት የማይበቃቸው አውሬዎችን መታገል ለነገ የማይባል እንደሆነ አምናለሁ። በምንም የሂሳብ ስሌት ከረሃብተኞች ጉሮሮ የዘርፈ ወራዳ፣ በአገር ክህደትና ንጹሃን ደም ሊወነጀልና ሊፈርበት የሚገባ ተላላኪ ወንጀለኛን ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አልቄ አላይም። ጭራሽ ሊታሰብ አይገባም። ይህ በነ ጀነራል ደምሴ ቡልቶ ደምና አስከሬን የተጫወተ ሰላይ የሚመራውን ትግል መደገፍም እነዛን ወርቅ የኢትዮጵያ ልጆች ዳግም ቀስቅሶ መጭፍጨፍ፣ አስከሬናቸውን መጎተት፣ ይህንንም በገድል በምስል ማሰራጨትና ደማችውን የመጠጣት ያህል ነው። ይህን ወንጀለኛ መከተልና በክፚም ቢሆን ማገልገል የሚያስብ ትውልድ ሲነሳ የልጅ ልጅ የሚያፍርበት ገድል ማስመዝገብም ይሆናል። ልጅ የልጅ ልጅ፣ ዘመድ አዝማድ የሚያፍርባችሁ ከመሆንም አታልፉም። አዲስ የሚስብ ትውልድ እየተሰራ ነው። የነቀዘው የትህነግን ዕውቀት ይነጥፋል። ኢትዮጵያን ብብዙ መከራ አልፋለች። ወደቀች ስትባል የሚያነሷት አታጣም። ዛሬም እስከ እምነት ቤት ዘልቆ የሚወዘወዘው የጥፋት ነዶ ይቆረጣል። ኢትዮጵያ ትሻገራለች። ዶክተር ከፋለ “እንደቃለን ሌላ ውጤት አናገኝበትም” ሲሉ የገለጹት የትርምስ ጥሪ ባለቤቶቹ ራሳቸውን ገልጸዋልና ” ማን ናቸው” ለሚለው ምላሽ ቀርቧል።

ትርምሱ እንጂ ከትርምሱ በሁዋላ ምን፣ እንዴትና፣ በነማን አማካይነት ማረጋጋቱ እንደሚከናወን በውል ሳይቀመጥ በገፊና ጎታች ትርክት ተናበው የሚንጡን ቅርንጫፋቸው ውጭ፣ ስራቸው ደግሞ አዲስ አበባ ነው። አዲስ አበባ መርዝ ታቅፋ መሽቶ ይነጋባታል። ኮንትሮባንዲስቶች ብር ያጥባሉ። የፍራንኮ ቫሉታ እድልን በመጠቀም ኢትዮጵያን የሚያልቡት ” የነጻነት ቀን አክባሪዎች” እና ወዳጆቻቸው ሁመራን እያሳረሱ ነው። አዲስ አበባ ሆነው ወደብ እያስተዳደሩ ነው። አዲስ አበባ ምስኪኖች የሚጸልዩላትን ያህል ዋና ዋና ሌቦች ደግሞ እያለቧት መልሰው መርዝ ያስረጫሉ። ያልገባቸው መርዛቸውን ይጠጡላቸዋል። ይህ ሁሉ የሚታወቅ ነው። ተቆርጦ እንዳይጣል አገር መርጋት አለባት። እንዳይቆረጡ አገር እንዲረጋ አይፈለግም። ህዝብ ቁጣ ውስጥ እንዲገባና በቁጣ አስቦ በስሜት እንዲመራ፣ በምሬትና ብስጭት የዓላማቸው አስፈጻሚ እንዲሆን የሚደረገው እንዲህ ባሉ ማጅራት መቺዎች ነው።

ለውጥ ከመጣ ጀምሮ የጥፋት ጥንስስ እዛም እዚህም ሲጠነስስ የነበረው ትህነግ የፈረሰው በህዝብ የተባበረ ክንድና በውድ የመከላከያ ሰራዊታችን ደምና አጥንት ነው። ፋኖ፣ ሚሊሻ ልዩ ሃይል ሁሉ ዋጋ ከፍለዋል። አሁን ላይ ኢትዮጵያ የገነባችው ዘመናዊ ጦር እንዲፈርስ የብሄርና የጎሳ ቅባት እየተቀባ ያለው ለምን ይሆን ብሎ መጥየቅ ዋናውን የኢትዮጵያን ጠላት ለመንቀል ዳግም ህብረት ይፈጥራልና ዜጎች እናስብ። ዋና የኢትዮጵያ ጠላት ማን እንደሆነ እንለይ። ማን ጠላት እያስለጠነ እንደሚደፋብን እንወቅ። በአገር ቀልድ የለምና!! ለማንኛው አባይ ሴራውን ሁሉ በጣጥሶ መብራት፣ ውበት፣ ደሴት፣ ሆኗል። አሳም እያመረተ ነው። ከሴራ ይልቅ አሳ ብሉ!!

ሰለሞን ዳዊት ከዲሲ

አዘጋጁ = ይህ ጽሁፍ የሚ ያንጸባርቀው የጸሃፊውን አሳብ ብቻ ነው። መልስ ወይም ተጨማሪ አስተያየት ለምትልኩልን አናስተናግዳለን

Exit mobile version