ETHIO12.COM

ኢትዮጵያ መቶ የኢንደስትሪ ፓርኮችን ልትገነባ ነው

የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በመጪዎቹ ዓመታት ከ100 በላይ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ለመገንባት ማቀዱን አስታወቀ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍፁም ከተማ ለኢፒድ እንዳስታወቁት ፤ የኢንዱስትሪ ፓርኮች የሥራ ዕድል በመፍጠር፣ የእውቀትና የልምድ ሽግግር በማድረግ የውጭ ምንዛሬ ገቢ በማስገኘት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው።

«ኮርፖሬሽኑ በመጪዎቹ አመታት ከ100 በላይ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በመላ ሀገሪቱ የመገንባት እቅድ በማውጣት የኢንደስትሪላይዜሽን ሂደቱን ለማሳለጥ እና ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ አስተዋጽኦ ለማድረግ አቅዷል» ብለዋል።

«ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን አሁን ላይ ከአዋጭነት ጥናት ጀምሮ እስከ ተግባር ድረስ ያሉትን ፕሮጀክቶች ለማስፋፋት እና ለመደገፍ ፍላጎት አለው። በዚህም ባንኮች የአዋጭነት ጥናቶችን እንዲሁም ሌሎች ዘዴዎችን መሠረት በማድረግ ብድር የማግኘት መንገዶችን ማዘጋጀት ይኖርባቸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ኮርፖሬሽኑ የመንግሥት እና የግሉ ዘርፍ ፕሮጀክቶችን ውጤታማነት የበለጠ ለማገዝ የኢንዱስትሪ ፕሮጀክት አገልግሎቶችን የማማከር፣ የመመርመር እንዲሁም የማሠልጠን ሥራዎችን በማስፋፋት ላይ በትኩረት እየሠራ ይገኛል» ብለዋል፡፡

እንደ አቶ ፍጹም ገለጻ፣ በአዲስ መልክ በኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ሥር መቋቋሙ የኢንዱስትሪ ልማትን ለማመቻቸት ዕድል የሚፈጥር ሲሆን፤ ባለፉት 40 ዓመታት ይህ የኢንዱስትሪ ልማት አገልግሎት 600 የሚሆኑ ውጤታማ የአዋጭነት ጥናቶችን ለመንግሥት እና ለግሉ ሴክተር ማበርከት ችሏል። በተቃራኒው ደግሞ በአመራር እና በአሠራር ችግር ምክንያት የተቋረጡ ፕሮጀክቶችም ነበሩ ሲሉ ተናግረዋል።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ተወዳዳሪ የኢንዱስትሪ ፕሮጀክቶች አገልግሎት እንዲኖር የሠራ ሲሆን ይህን ለማሳካትም ኮርፖሬሽኑ ከባለድርሻ አካላት እና ከግል አማካሪ ድርጅቶች ጋር በትብብር ሠርቷል ብለዋል።

ኮርፖሬሽኑ በመላ ሀገሪቱ 13 የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በማስተዳደር ላይ እንደሚገኝም አቶ ፍጹም አስታውሰዋል።


Exit mobile version