Site icon ETHIO12.COM

ለወልቃይት ጠገዴ ሴቲት ሁመራ አንድ ሚሊዮን የጉልበት ሰራተኛ ይፈለጋል፤ ከአንድ ነጥን አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ሰሊጥ ይጠበቃል

“ከየትኛውም የኢትዮጵያ ክልል አስተማማኝ ሰላም ያለው እዚህ ነው። ለሰራተኞች እንደ ቤተሰብ ዝግጅት አድርገናል። ኑ” ሲሉ የተሰሙት አምስት መቶና ሶስት መቶ ሄክታር ሰሊጥና ማሽላ ያመረቱ ባለሃብቶች ናቸው። የዞኑ ግብርና ቢሮ ሃላፊ እንዳሉት አንድ ሚሊዮን አንድ መቶ ሃምሳ ሁለት ሺህ ኩንታል የሰሊጥ ምርት ስለሚጠበቅ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የሰራተኛ ሃይል ያስፈልጋል።

የዞኑ አርባ በመቶ በሰሊጥ ምርት መሸፈኑን ያመለከቱት የዞኑ የግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ አወቀ መብራቱ ” ሰሊጥ ሲሰበሰብ በቂ የሰው ሃይልና ጥንቃቄ ስለሚሻ ይህን ባገናዘበ መልኩ አጨዳ ለመጀመር ዝግጅት ተደርጓል” ብለዋል። ከዝግጅቱ መካከልም ሰራተኞችን መቀበል ነው። ከአጎራባች ዞኖች ጋር በጋር እየተሰራ እንደሆነም አመልክተዋል።

በአማራ ቴሌቪዥን ቀርበው የተናገሩት ባለሃብቶች ዞናቸው እጅግ ሰላማዊ በመሆኑ አጨዳ ለመጀመር ለሰራተኞች ማረፊያ፣ ቀለብ፣ ትራንስፖርትና መድሃኒት ማዘጋጀታቸውን አመልክተዋል። ” ሰርተን፣ ጥሩ ምርት አግኝተን፣ ራሳችንን ጠቅመን፣ ለመንግስት የሚጠብቅብንን ከፍለን አብረን መሻሻል አላማችን ነውና መጥታችሁ ሰርታችሁ እናንተም ተጠቀሙ። እንደ ቤተሰብ ለንቀበላችሁ ዝግጁ ነን” ሲሉ ጥሪያቸውን በሚዘናጠፈውና ታይቶ በማያለቅው ማሳ ውስጥ ሆነው ጥሪ አሰምተዋል።

2014 ዓ ም የምርት ዘመን በተመሳሳይ ለሰራተኞች ቅጥር ማስታወቂያ ሲነገር የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪና 360ዎች በመቀባበል ” አትመዝገቡ፣ አትሂዱ፣ ወታደር አድርገው ሊማግዷችሁ ነው” በሚል በተደጋጋሚ ቅስቀሳ ማካሄዳቸው በወቅቱ ከፍተኛ ቅሬታ ያስነሳ፣ በታሪክም የማይረሳ ጠላትነት እንደሆነ ጠቅሰው አስተያየት ሲሰጡ እንደነበር ይታወሳል።

አሁን ላይ የመንግስት ተቃዋሚ ሚዲያ እየመራ ያለው ጌታቸው ሽፈራው በወቅቱ “ኢትዮ 360 በጦርነቱ ምክንያት መሬት ጦሙን አደረ ሲል ከርሞ፣ አሁን ለሰብል ስብሰባ የሰራተኛ ቅጥር ሲወጣ የህወሓትን አጀንዳ እያራገበ በህዝብ ላይ ሌላ ጦርነት ከፍቷል” በሚል ከትቦ ነበር። ጌታቸው ሽፈራው በራሱ የማህበራዊ ገጽ ሳይቀር ባሰራጨው ሰፊ አስተያየት 360ዎች “በአንድ ዞን ሚሊዮን የስራ እድል ሲፈጠር እንዲስተጓጎል እየሰሩ ነው።  አርሶ አደር ሰብል እንዳይሰበስብ ቅስቀሳ ማድረግ በህዝብ ላይ ጦርነት መክፈት ነው። ሚሊዮን ወጣት ስራ እንዳይሰራ መቀስቀስ ወንጀል ነው። ያፈጠጠ የህዝብ ጠላትነት ነው” ሲል አክርሮ ማስረጃ በማስደገፍ ተቃውሞውን ገልጾ እንደነበር ይታወሳል።

ይህ እስከታተመ ድረስ በግልጽ የተሰማ የተቃውሞ ቅስቀሳ ባይኖርም ” ጎንደር ዓይናቸውን በሰሊጥ መሬት ላይ በተከሉ፣ ለሃጫቸውን በቦሎቄ ፍሬ ላይ በሚያዝረበረቡ፣ ወልቃይትን እንደ ድሬደዋ መስተዳድር ራስ ገዝ አድርገው ከዐማራ ሊለዩ በሚታትሩ ተውሳኮች የታጠረች፣ የተመረዘች፣ ጎንደር አሜሪካ ተቀምጠው ሳይደክሙ የሸዋና የጎጃም፣ የወሎና የጎንደር ፋኖዎችን በፍርፋሪ ዶላር ከፋፍለው 4 ኪሎ ለመግባት ቋምጠው በተጎለቱ ድልብ የተማሩ መሃይሞች ተጠርንፋ ያለችና እነዚህ ሾተላዮች ሊወገዱላት የሚገባት ናት” ሲል Zemedkun Bekele (ዘመዴ) በቴሌግራም ገጹ ስለጎንደር መያዝ መስማቱን ጠቅሶ ማረጋገጫ ሳይሰጥ ጽሁፍ አሰርጭቷል።

ይኸው የአማራ ትግልን ከሚመሩት ወገን የአንዱ ወገን እንደሆነ የሚገልጸው Zemedkun Bekele (ዘመዴ) ሰሞኑንን በተከታታይ “ጎንደር ባንዳ ሆነ” በሚል ሲጽፍና የጎንደርን ዝምታ ከሰሊጥ ጋር በማያያዝ ወልቃይት ራስ ገዝ እንድትሆን የሚደራደሩ ዓይነት አድርጎ ስሏቸዋል።

ወልቃይት ጠገዴ ሲቲትሁመራ የሰላም ቀጠና መሆኑንን ጠቅሰው ኮሎኔል ደመቀ ሲናገሩ ” ከመከላከያ ጋር እጅ ለጅ ሆነን እየሰራን ነው” ማለታቸውን ተከትሎ ትችት ተሰንዝሮባቸው እንደነበር ይታወሳል። ከከፍተኛ ሰቆቃ እንደተላቀቁ የሚናገሩት የውልቃይት ጠገዴ ሲቲት ሁመራ ነዋሪዎች ራሳቸውን አደራጅተው በጥብቅ ስነስርዓት ሌትና ቀን አካባቢያቸውን እንደሚጠብቁ፣ መከላከያም ያለአንዳች ስጋት የራሱን ስራ እንደሚሰራ ኮሎኔሉን የጠቀሳቸው የጀርመን ድምጽ ከወራት በፊት ማስታወቁ አይዘነጋም።

በዞኑ ከአስራ ሁለት በላይ የተላያዩ አዝርዕቶች የሚበቅሉ ሲሆን በዘንድሮው ዓመት ከሰሊጥ በተጨማሪ ከፍተኛ የማሽላ ምርት እንደሚጠበቅ ሃላፊው አስታውቀዋል። ወልቃይት ጠገዴ ሴቲት ሁመራ በአማራ ክልል እጅግ ሰፊ፣ ምቹና ለም የሆነ መሬት ያካለለ አካባቢ ነው።


Exit mobile version